31 December 2017

ነአምን አሸናፊ

ከገዥው ፓርቲ ኢሕአዴግ ጋር እየተደረገ ባለው ድርድር ምክንያት በኢትዮጵያውያን ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢዴፓ) አመራሮች ዘንድ የተፈጠረውን አለመግባባት የመረመረው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ፣ አዲሱ አመራር የተመረጠበት መንገድ የፓርቲውን መተዳደሪያ ደንብ መሠረት ያላደረገ በመሆኑ እንደማይቀበለው አስታወቀ፡፡ የምርጫ ቦርድ ጽሕፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ ወንድሙ ጎላ ይህንን ቢሉም፣ አዲስ የተመረጠው አመራር ውሳኔው ሆን ተብሎ ኢዴፓን የማፍረስ ዓላማ ያለው ነው በማለት ተቃውሞ አሰምቷል፡፡

የፓርቲው መሥራችና የብሔራዊ ምክር ቤት አባል አቶ ልደቱ አያሌው ሐሙስ ታኅሳስ 19 ቀን 2010 .. በፓርቲው ዋና ጽሕፈት ቤት በተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ እንዳስታወቁት፣ ቦርዱ ከዚህ ቀደም አዲሱ አመራር እንዲያስተካክል ያዘዛቸውን አምስት ነጥቦች ወደ ጎን በመተው አዲስ ጥያቄ አምጥቷል፡፡

ምርጫ ቦርድ ለአዲሱ አመራር ያቀረባቸው ጥያቄዎች ለቦርዱ የቀረበውን ደብዳቤ ፕሬዚዳንቱ መሆን ሲገባቸው ለምን ዋና ጸሐፊው ጻፉ? እንዲሁም የብሔራዊ ምክር ቤቱ ስብሰባ የትና መቼ መጠራት እንዳለበት የሚወስነው ማን ነው? የሚሉ ናቸው፡፡

ይህን ጥያቄ የተቃወሙት አቶ ልደቱ፣ ‹‹ቦርዱ ለመረጥነው ሊቀመንበር ዕውቅና አልሰጥም ብሏል፡፡ ስለዚህ በሊቀመንበሩ ፊርማ ደብዳቤ ቢሄድ እንደማይቀበለው አስቀድሞ የሚታወቅ ነበር፡፡ በመሆኑም በዋና ጸሐፊው አማካይነት ደብዳቤው ወጥቷል፡፡ ነገር ግን ይህ አሠራር በፓርቲው ሕገ ደንብ መሠረት ሕጋዊ አሠራር ነው፤›› በማለት አስረድተዋል፡፡

የፓርቲው መተዳደሪያ ደንብ አንቀጽ 24 የፓርቲውን ዋና ጸሐፊ ሥልጣንና ተግባራት የሚዘረዝር ሲሆን፣ በዚሁ አንቀጽ ንዑስ አንቀጽ 2 ላይ ‹‹ዋና ጸሐፊው የጽሐፈት ቤቱን የደብዳቤ ልውውጦች ያከናውናል፡፡ የጽሕፈት ቤቱ ሰነዶች ሁሉ በሥርዓት መያዛቸውንና መጠበቃቸውን ያረጋግጣል፤›› ይላል፡፡

ሆኖም የቦርዱ ምክትል ኃላፊ፣ ‹‹ይህ አንቀጽ ተግባር ላይ የሚውለው የፓርቲው ፕሬዚዳንት በማይኖርበት ጊዜ ነው፡፡ አሁን ግን ፕሬዚዳንቱ አለ፡፡ እንዲያውም እሱ ለቦርዱ ተቃውሞውን እያቀረበ ነው፡፡ ስለዚህ እንዲህ ባለ ሁኔታ የሚቀርቡ ደብዳቤዎችን መቀበል አስቸጋሪ ነው፤›› በማለት ለሪፖርተር ምላሽ ሰጥተዋል፡፡

ከዚህ በተጨማሪ፣ ‹‹እኛ ከፓርቲው ምንም የምንፈልገው ጉዳይ የለም፡፡ እያልን ያለነው የፓርቲውን መተዳደሪያ ደንብ በቅጡ አክብሩ ነው፤›› ብለዋል፡፡

ስብሰባው መቼና የት መደረግ እንዳለበት መወሰን የሚገባው አካል ማን ነው? ለሚለው የቦርዱ ጥያቄ ላይ አስተያየት የሰጡት አቶ ልደቱ፣ ፓርቲው ሁለት ዓይነት የስብሰባ አጠራር ሥርዓት እንዳለው ገልጸዋል፡፡

በዚህም መሠረት መደበኛ በሆነ አሠራር ሥራ አስፈጻሚው የሚጠራቸው ስብሰባዎች ከሆኑ ቦታውንም ጊዜውንም የሚወስነው ሥራ አስፈጻሚው ነው፡፡ ነገር ግን ሥራ አስፈጻሚው ስብሰባ መጥራት የማይችልበት ሁኔታ ከተፈጠረ፣ ብሔራዊ ምክር ቤቱ ጥቅሙን ለማስጠበቅ አንድ ሦስተኛ የሚሆኑ የብሔራዊ ምክር ቤት አባላት  ተፈራርመው ስብሰባ ሊጠሩ ይችላሉ በማለት፣ የፓርቲውን የስብሰባ አሠራር አካሄድ አብራርተዋል፡፡

‹‹ሆኖም ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በፓርቲው ሕገ ደንብ መሠረት ያቀረብናቸውን አማራጮች ሁሉ ወደ ጎን በመተው ለጥቂት ግለሰቦች ወገንተኝነቱን አሳይቷል፤›› በማለት አቶ ልደቱ በምርጫ ቦርድ ላይ የሰላ ትችት ሰንዝረዋል፡፡

ሪፖርተር