January 27, 2018
ከአቻምየለህ ታምሩ
የመርሳ ውሎ. . .
ወሎ ከዳር እስከ ዳር እየተቃጠለ ይገኛል። አማራ ለማጥቃት የሰለጠኑ የትግራይ ወታደሮች በመርሳ ያገኙትን አማራ ሁሉ ሲጨፈጭፉ ውለዋል። መርሳ ከወልድያ ወደ ደሴ በሚወስደው መንገድ ከወልድያ ሰላሳ ኪሎ ሜትር አካባቢ የምትገኝ ከተማ ናት። እስካሁን በደረሰኝ መረጃ መሰረት በዛሬው እለት መርሳ ውስጥ 13 ንጹሐን አማሮች በትግራይ ወታደሮች ጥይት ተጨፍጭፈዋል።
የመርሳ ሕዝብ አደባባይ የወጣው ወልቃይት የአማራ ነው፤ ራያ አንድ ነው፤የወያኔ ፋሽስታዊ አገዛዝ በቃን፤ በወልድያ እና ቆቦ የፈሰሰው የአማራ ደም የእኛም ደም ነው፤ ሕዝብን በጠላትነት ፈርጆ እንደ ወራሪ ጠላት በመከላከያ የሚጨፈጭፍ ፋሽስት እንጂ መንግሥት አይደለም የሚል መፈክር በመያዝ ነበር። ወሎ ውስጥ ከተካሄዱት ሕዝባዊ ተጋድሎዎች የመርሳው የሚለየው የከተማው ፖሊሶች ከሕዝቡ ጎን በመቆም አጋርነታቸውን መግለጣቸው ነው። ሌሎችም ፖሊሶች የመርሳ ፖሊሶችን ፈለግ እንዲከተሉ ሕዝቡ ጥሪውን አስተላልፏል።
ዛሬ ቅዳሜ ጧት አደባባይ ከወጡ የከተማይቱ ነዋሪዎች መካከል የመጀመሪያው ሶስቱ ንጹሐን የተገደሉት ፖሊሶችን ለግድያ ለማሰማራት ከቤቱ የወጣው ከሀብሩ ወረዳ ፍርድ ቤት ኃላፊ በተተኮሰ ጥይት ነው። የተቆጣው ሕዝብ በወሰደው ራስን የመከላከል እርምጃ የሀብሩን ወረዳ ፍርድ ቤት አቃጥሎ ሶስት ሰዎችን በገደለውን የፍርድ ቤት አስወግደውታል።
ከዚህ በተጨማሪ ሕዝቡ የትግራይ ወታደሮች የመሸጉባቸውን የሀብሩ ወረዳና የከተማው ፖሊስ ጣቢያዎች፣ የአገዛዙ የግድያ ተቋማትንና ሕዝብን የሚያስገድሉ ደህንነቶች የሚደበቁባቸውን መኖሪያ ቤቶችን በመለየት አውድሟል። የወያኔ ሰላዮች በቢኖነት የሚጠሙበት የመርሳ ከተማ ማዘጋጃ ቤት ክፍል መስታወቶችዎ ወድመዋል፤ ከፊል የህንጻው ክፍልም ጋይቷል።
ከዚህ በተጨማሪ ተጋዳዩ ሕዝብ በከተማው በግፍ ታጉረው የነበሩ ግፉዓንን እስረኞች በሙሉ አስለቅቋል። ባሁኑ ሰዓት መርሳ በመከላከያ ሰራዊት ስም በሚጠሩ የትግራይ ወታደሮችና የከተማውን የፖሊስ ልብስ በለበሱ አጋዚዎች ተከባለች።
በተያያዘ ዜና በዛሬው እለት በቆቦ ታስቦ የነበረው እነ አለምነው መኮነን የጠሩት ስብሰባ ሳይካሄድ ቀርቷል። በስብሰባው አዳራሽ የተገኙ ሰዎች ሕዝቡን ጭምር የተሳተፈበት ስብሰባ ነው መካሄድ ያለብን፤ ለዚህም አዳራሹ ስለማይበቃ ስቴዲዬም እንሰብሰብ በሚል በአንድ ድምጻ በማሰማታቸው የአዳራሹ ስብሰባ ወደ ስቴዲያም እንዲዛወር ተደርጎ ነበር ግን። ሆኖም ግን ስታዲየም የታደመው ተሰብሳቢ አማራን በተሳደበው በባለጌው አለምነው መኮነን የሚመራ ስብሰባ አንሰበሰብም በማለቱ ሊካሄድ የታቀደው ስብሰባ በረብሻ ተበትኗል። በዚህም ጀግናው የቆቦ ሕዝብ ታሪክ ሰርቷል። በቆቦ ሕዝብ የተዋረደው ነውረኛው አለምነውም ከግብረ አበሩ ከያለው አባተ ጋር በመሆኑ በትግራይ ወታደሮች ታጅቦ ከቆቦ ወደ መቀሌ ሄዷል!