January 30, 2018
ባህር ዳር ወደ ፍቅር
በቅርቡ ቴዲ አፍሮ ባህር ዳር ላይ ፈተና ገጥሞት ነበር፡፡” ጃ ያስተሰርልን” ዝፈን ተብሎ፡፡ በ17መርፌ እንዲል፡፡ ለውጥ መቼ መጣ እነዲል፡፡ ንግስና በዘረ ነው ስለዚህ አዲስ ንጉስ እንጂ… ሊልላቸው ፈልገው ነበር፡፡ ቴዲሾ ግን አንዲት መልስ ብቻ ነበረችው፡፡ ሁሉንም በፍቅር እናሸንፋለን ፡፡ የምትል፡፡ አንዳንድ አክቲቪስቶች ግን ተቃውመውታል፡፡ “ከመቼ ወዲህ ነው ሴጣን በፍቅር የተሸነፈው “ ብለው፡፡ ነው እንዴ…. ነገርየዋ ካልተካረርን አንፋታም አይነት ነው፡፡ ቴዲ ጥበቡን ይጨምርልህ!
ቤተሰብ ወደ ፍቅር
ለመፋታት ቅድሚያ መጋባት ያስፈልጋል፡፡ ለመጋባት ደግሞ ቀድሞውኑ ሁለት የተለያየን አካላት መሆናችንን ማክበር አለብን፡፡ ከዚያ “እሱ አንድ ያደረገውን …. “ ብለን ብንፎክር ያስኬዳል፡፡ አንድ መንግስት የራስን ዕድል በራስ ለመወሰን መጀመሪያ የግለሰብ መብትን ያለገደብ ያክብር፡፡ ዲሞክራሲን ያለ ገደብ ከሕዝቡ ለሕዝቡ በህዝቡ ያክብር፡፡ ከዚያ ማንም በሌላው አይፈርድም፡፡ መብቱ ተከብሮለታልና፡፡ ለይስሙላና በማጭበርበር ሳይሆን ማንም የማንንም መላጣ እማይነካ ጨዋ ስልጡንና ሥርዓትና ባህል ያለው ሕዝብ እንዳለን አንዘንጋ፡፡ ይህ ህዝብ ለዕድገታችን ቅራኔዎች ያሉትን የቡድን መብት ከግለሰብ መብት እኩል ማክበርንም ያውቅበታል፡፡ ብቻ ቅድሚያ የግለሰብ መብት ይከበርልንማ፡፡ “ከሩቅ ዘመድ የቅረብ ጎረቤት” እንጂ “ዘር ከልጓም ይስባል” የሚለው አይቀድመውምና፡፡ “ሀ ራስህን አድን” ብሏል ያራዳ ልጅ፡፡ ፍሬንዶች በግል እየወጣችሁ ከፒፕሉ ጋር “ተዛረቡ”፡፡ ከዚያ አዳሜ ነቄ ነው፤ ነጥሎ ከምቹን አስሊዋ ላይ ማሳረፍ ይችልበታል፡፡ ይህ ነው እንግዲህ በቅድሚያ የራስን እድል በራስ መወሰን ሲባል፡፡ ቡድኑ ያከብርልኛል ብለህ ግነ እንዳትጠገረር ጀለስ፡፡
ሕዝብ ወደ ፍቅር
ማንም ሕዝብ “በራሱ ጉዳይ ራሱ ወሰነ” ማለት ቀላል ነገር አይደለም፡፡ ትልቅ የመብት ማስከበር ስርዓት ተከናወነ ማለት ነው፡፡ ይህ መብት ግን የቡድንን መብት ሊያስገኝ እንዳይችል ልናውቅ ግድ ይለናል፡፡ ክሪሚያ ውስጥ በድምፅ ተበልጠው ከዩክሬይን የተለዩ እንዳሉና ድምፃቸውን አጥፍተው እንደሚኖሩ አንርሳ፡፡ ያቺ “የግለሰብ መብት” በድንገተኛው የዩክሬንና ሩሲያ ግጭት እንደቁማር ተበላች፡፡ ግና ቀድማ በዩክሬን ሳለች ተከብራለት ቢሆን ኖሮ ቀድሞውኑ ራሱ፤“የራሱን እድል የመወሰን መብት” ያለው አካል አባል በሆነ ነበር፡፡ በፍቅሩ ጊዜ፡፡
የሪፈረንደም ሪፌሪዎች(ዳኞች)
ብዙ ጊዜ የራስን ዕድል በራስ መወሰን ወይም (ሪፈረንደም) የሚካሄደው ችግሮች ከተፈጠሩ በኋላ ነው፡፡ ችግሮቹም ሰው ሰራሽ ናቸው፡፡ ችግሮቹን የሚያባበሱአቸው እነዚያው ያቺን ከመለያየት የምትገኝ ትርፍ ለማፈስ የተዘጋጁ አካላት ናቸው- ሪፌሪዎች፡፡ በኤርትራ ከ30ዓመታት ጦርነት በኋላ ማንም በእንባ እየተራጨ የማይለይ አካል አይኖርም፡፡ “….ሀዘንሽ ቅጥ አጣ” ነዋ ነገሩ፡፡ እንጠቅሳለን ፡ – የሎንዶን አደራዳሪው ኸርማን ኮኸን፡፡ ዛሬም አንቀፅ 39ን ተግብሩ ይላል አሉ፡፡ (ተስፋ ኒውስ)በቅድሚያ መላው ስላንተ መጨነቅ እንዲችል ሰላም ያስፈልጋል ለሀገሩ፡፡ ሰላም የህሊና ሰላም ያስፈልገዋል ለግለሰቡ ህሊና፡፡ አንድነትም እንዲኖር ሰላም ያስፈልጋል፡፡ ለመተካከም ሰላም ያስፈልጋል፡፡ ሰላም እንዳይኖር የሚሻው ያው የታወቀ ነው – ዓላማውና ዒላማው፡፡ ትናንሽ መንግስታትና የአንድነት ሐይሎች ናቸው፡፡ መንግስታቱን አግኝቶም ጭዳ የሚያደርጋቸው በፍቅር ሰለባነት የአንድነት ተጓዦቹን ነው፡፡ለዚህ ሁሉ ሪፌሪ ዳኛ የሚሆኑት ጥቅመኛና ስግብግብ ብሎም የፍቅር ጠላቶች ናቸው የሪፈረንደም አጋፋሪዎቹ፡፡ የዳኛ ተጫዋቾች እንዲል አንድ ገጣሚ ወዳጄ፡፡
የራስን ዕድል በፍቅር መወሰን እንዴትነት
ፍቅር ያለ አንድነት፤ አንድነትም ያለ ፍቅር አይኖሩም፡፡ ሰላም የምንለውም የሁለቱን ስምረት ነው፡፡ በዚህ አንፃር አሻግረን ስንመለከት ለፍቅር የግለሰብ መብት መከበር ግዴታ ይሆናል፡፡ ፍቅር ያለ ነፃነት አይገኝም፡፡ነፃነት ያለው ፍቅር ካለንና ከተዋደድን ሰላምም ሆነ አንድነት አለን፡፡ አንድነታችን በፍቅር ላይ ከተገነባ ደግሞ መለያየት አንፈልግም፤ የራስን ዕድል በራስ መወሰን አያስፈልገንም፡፡ ፍቅር ሁሉንም ወስኖልናልና፡፡ ያንንም የራስን ዕድል በፍቅር መወሰን ብንለውሳ፡፡ እኛው እንታረቅ እኛው እንፋቀር፡፡
ማንም በማንም ላይ አይወስንም (ማንዴቴ)
በፖለቲካ ከምንም ነገር በላይ የሕዝብን ይሁንታ ወይም ማንዴት በሕጋዊ መንገድ መቀበል የሥርዓቶች ሁሉ መጀመሪያ ነው፡፡ ፖለቲከኞች ያለ ሕዝባዊ ማንዴት ሕዝብ ላይ ቂጥ ብለው ሕዝብን ሲያሸማቅቁ ይታያሉ፡፡ ዘመናችን የማንዴት አልባ ፖለቲካ ወደ ሽብር ያደገበት ሆኖ በየእጣጫው ይስተዋላል፡፡ “እስላማዊ መንግስት ነኝ” የሚል አካል የሙስሊሞችን ታሪካዊ ቅርሶች እንዴት ሊያጠፋ ይችላል፡፡ በቺቦክ ልጃገረዶችን ያፈነው ለእነዚያው ልጆች ነፃነት የምታገል አካል ነኝ ቢል ማን መብትህ ነው ብሎ ይቀበለዋል፡፡ ያ ህዝብ ትወክለኛለህ ሳይለው እንዴት በራሱ በህዝቡ ላይ መልሶ ጥቃት ይፈፅማል፡፡ የግለሰብን መብት የማያከብር የነፃነት ትግል ነፃነትን የማያውቅ መሆኑን ማወቅ በራሱ ላይ እንድትነሳ ያደርግሃል፡፡ ለዚህ መሰረቱ “ታግለህ አታግለኝ” የሚል ማንዴትን ከሕዝቡ የሚቀበል ሐይል መኖር አለበት፡፡ ያለማንዴት ሕገመንግስት አይደለም አንድ ረቂቅ ህግ ማውጣት ከንቱ ነው፡፡ ሕዝብን የሚያከብር ማንዴቱን ያከብራል፡፡ በተሰጠው ህዝባዊ ማንዴት ሥራውን ይሰራል እንጂ ከማንዴቱ በፊት አዋጅ አያወጣም፡፡
መሪ ግብዝ አይደለም አፍቃሪ ንጂ
“ተናገር በከንፈሬ ተቀመጥ በወንበሬ” ሳይባል መባተት እንደ ሰርቫንቲስ ዶን ኪሆቴ ግብዝነትን ያላብሣል፡፡ ብኩን ያደርጋል፡፡ ስትወዳት ስትወድህ ነው እንጂ አንተ ብቻ መውደድህ ከንቱ ነው፡፡ የራሷን አድል በራሷ ወስና የምታገባህ ሚስት እንጂ እንደጥንቱ ጋብቻ ቤተሰብ የመረጠላትን የምታገባ ሴት ምን ትረባሃለች፡፡ ላትወድህ ላታፈቅርህ ትችላለችና፡፡የልምዣትን ያነቧል፡፡ ሕፃናትም ከማን ጋር ማደግ እንዳለባቸው የሚወስኑበት እድሜ አለ፡፡ ለዚህ ሁሉ ፍቅር ወሳኝ ነው፡፡ አግቢዋም ህፃኑም ፍቅር ወዳላቸው መሰብሰባቸው ተፈጥሮአዊ ነው፡፡ ፍቅር ካለ ሰላም አለ፤ ሰላም ካለ በልዩነት ውስጥ አንድነት አለ፡፡
መደምደሚያ
አይዞን ወገኔ ፤ፍቅር ነው መድኔ
ተባባል ወገኔ፤ ተባበር ወገኔ፡፡
በ”የራስን ዕድል በራስ የመወሰን መብት” ስበብ ፤ ሕዝብ ቢለያይ አንድ ተስፋ አለው፡፡ ያም ተስፋ ቀድሞውኑ ያ ህዝብ የግለሰብ መብቱ የተከበረለት ህዝብ የሆነ እንደሆነ ብቻ ነው፡፡ ያ ከሆነ ምርጫውን ያውቃል፡፡ በድገተኛና ሰውሰራሽ ሁኔታዎች በጥድፊያ በሚደረግ ሪፈረንደም ዋና ምርጫውን እንዳይስት ልቦና ይኖረዋልና፡፡ አምባገነኖች ግን የራሰን ዕድል በራስ መወሰንን ተጠቅመው ሕገወጥ መለያየት ቢፈጥሩ እንኳን አሁንም ሌላ አንድ ተስፋ አለን፡፡ ልብ እንበል፡፡ ያለስልት በመታገል ሣይሆን፤ ከተለያዩ በኋላም ቢሆን፤ በፍቅር በመተሳሳብ ያን የተለዩበትን ሀገር መልሶ በአንድ የተባበረ ሀገርነት መመስረት ይቻላል፡፡ ይህ በዓለም ዓቀፍ ደረጃ ያለ ሕጋዊ የተባበረ መንግስት ምሰረታ ቅርፅ ነው፡፡ የተባበረች አሜሪካ መንግስታትም የዚሁ ዓይነት ትግል ውጤት ናት፡፡ ሊያውም የእሷ ፍጹም የተለያዩ ሀገር ዜጎችን አሰባስባ የምትኖር የታባበረች ሀገር፡፡ ስለተባበረችም የተከበረች፡፡ ለዚህ ደግሞ ዋናው ዋስትና የሕግ የበላይነት መከበር ነው፡፡ ሕግ በእኩል በሚከበርበት፤ ፍትሕ ርትዕ ባለበት፤ ዜጎች በግል ሆነ በቡድን መለያየትን ሳይሆን የአንድነትን ፍሬ ነው ማጣጣም የሚሹት፡፡ አንድነት እና ሕብረት የፍቅር መግለጫዎች ናቸው፡፡ ለዚህም ነው ለእኛ ለኢትዮጵያውያን ክቡር ዶ/ር ጥላሁን እንዳቀነቀነው “መለያየት ሞት” የሚሆነው፡፡ አንለያይም ሳይሆን እንተባበራለን፡፡ ተስፋ አንቆርጥም እንገናኛለን፡፡
የራሣችንን ዕድል በፍቅር በመወሰን የዘረኞችን ሴራ እናከሽፋል!
ዛሬም ነገም – አብረን ነን!!!