በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን።
“የወንድምህ ደም ከምድር ወደ እኔ ይጮኃል ”
፩. ቃየልን ለግድያ ያበቃው፤ ምንድነው? እራስ ወደድነት ፤ ቅናት ፤ ቁጣ ፤ ጥላቻ ፤ ንዴትና ምቀኝነት ናቸው።
“ለምንስ ተናደድክ? ለምንስ ፊትህ ጠቆረ? መልካም ብታደርግ ተቀባይነትን አታገኘምን? መልካም ባታደርግ ግን ኃጢአት በድጅህ እያደባች ነው”
ይህ ኃይለ ቃል መጀመሪያ የቃየል አስተሳሰብ መበላሸቱን ነው የሚያረጋግጠው ። የስው ልጅ መጀመርያ ልቡ (አስተሳሰቡ) ነው የሚታየው። ንግግሩ ወይንም ተግባሩ አይደለም።“እግዚአብሔርሰ ልበ ይሬኢ ወሰብሰ ገጸ ይሬኢ” “ሰው ፊትን ያያል እግዚአብሔር ግን ልብን (አስተሳሰብን) ይመለከታል” ስንቶቻችን ዛሬ በልባችን አስበን እኔነትን አንግሠን ቅናትን ፣ ቁጣን ፣ ጥላቻን ፣ ምቀኝነትን አንግበን ፣ የወንድሞቻችንን ሚስቶች ፣ የእህቶቻንን ባሎች የተመኘን ፣ የቀማን? ወንድማችንን ፣ እህታችንን አንድ ጊዜ የአጠቃን፤ እራሳችንን ደጋግመን የምናጠቃ? በቁጣ ፣ በጥላቻ ፣ በንዴት ፣ በምቀኝነት በመነሳሳት ወንድሞቻችንን ፣ እህቶቻችንን የገደልን፤ እራሳችንን ግን ደጋግመን የምንገድል አይደለንም እንዴ’? መንግሥትም የዚሁ ኅብረተሰብ ውጤት በመሆኑ ሌላ ሊሆን አይችልም።
፪. ቃየል አቤልን ለመግደል የተጠቀመበት ስልት ምን ነበር? በማታለል ፣ በመዋሸትና በማስመሰል ነበር። “እስቲ ና ወደ መስክ እንውጣ አለው በመስክም ሳሉ ወንድሙ አቤልን አጠቃው ገደለውም”። ይህ የመጀመሪያው ነፍሰ ገዳይ ነው። “እስኪ ና ወደ መስክ እንውጣ” ዐይን ባወጣ ማታለል በወንድሙ ላይ እና በጻድቅ ሰው ላይ የተፈጸመ አረመኔያዊ ድርጊት ነው። የሰው ልጅ ከአራዊት የባሰ መሆኑን ያረጋግጣል። ዛሬስ በሀገራችን በማታለል ፣በመዋሽት ፣ በማስመስል «ዲሞክራሲ አስፈንኩልህ ፤ በነፃነት የማምለክ ፣ የመናገርና የመጻፍ የተፈጥሮ መብትህን አስከብርኩልህ» እያለ፣ በወልድያ አምልኮታቸውን በሚፈጽሙበት ወቅት በደም የተጥመቁ የአቤል እድል ፈንታ የገጠማቸውን ስማእታተ-ወልድያን እናስባቸዋለን፤ ለዘለዓለም ታሪክ ሲያስትውሳቸውም ይኖራል። ቃየላዊ ተግባር የፈጸመውንና የሚፈጽመውን መንግሥት በእግዚአብሔር ስም እናውግዛለን። ከእንደዚህ ያለው እኩይ ተግባር እንዲርቅና እንዲያቆም በእግዚአብሔር ስም እናስጠነቅቃለን። በውስጥና በውጭ የአላችሁ ከሕዝብ ጎን ቆመናል የምትሉ ወታደሮች ፣ አርበኞች ፣ ምሁራን ፣ የሀገር ሽማግሌዎችና የፖለቲካ ሰዎች፣ ከቃየላዊ ባሕርይና ግብር የተላቀቃችሁ እንድትሆኑ በእግዚአብሔር ስም አደራ እንላለን።
፫/ ከግድያ በኋላ እግዚአብሔርስ ለገዳዩ ምን አለው? ገዳዩስ ምን መልስ ሰጠ?
“እግዚአብሔር ቃየልን ወንድምህ አቤል የት ነው ? አለው። ቃየልም አላውቅም ፤ እኔ የወንድሜ ጠባቂ ነኝን? ሲል መለሰ።” ወንድሙን የእናቱን ልጅ አንድ ቀን ተጸንሰው አንድ ቀን የተወለዱ ሆኖ እያለ “አላውቅም” ማለት ዓይን ያወጣ ውሽት ፣ ክህደትና ሽፍጥ ነው። ከጭካኔ የመነጨ የግዴለሽነትና «ማን አለብኝ» የሚል የድፍረትና የትዕቢት አባባል ነው። የቃየልን አባባል ዛሬ ሥልጣንን ሙጥኝ ያለው መንግሥት ፣ እንዲጠብቅ የተሰጠውን መንጋና የገዛ ወገኑን በጭካኔ ሲገርፍ ፣ ሲያስርና ሲገድል፣ እኩይ ግብሩ እንደማያውቀው ቃየላዊ ድርጊቱ ያረጋግጣል። ከጥቂቶቻችን በቀር የእያንዳንዳችን ልብ(ኃሣብ) ቢመዘንና ተከፍቶ ቢታይ ቃየላዊ ልብ(ኃሣብ) ነው የሚታየው።
፬. እግዚአብሔር በገዳዩ ላይ ምን አደረገ?
“እግዚአብሔር እንዲህ አለ ምንድን ነው ያድረከው? የወንድምህ ደም ወደ እኔ ይጮኃል።እንግዲህ የተረገምክ ነህ። የወንድምህን ደም ከእጅህ ለመቀበል አፏን ከከፈተችው መሬት ትሰደዳለህ … በምድር ላይ ኮብላይ ተቅብዝባዥ ትሆናለህ።” አቤል በወንድሙ በግፍ ቢገደልም እንኳን እስከ አሁን እምነቱ ጽድቅ ሆኖ ሲነገር ይኖራል። ምክንያቱም በወንድሞቻቸው ላይ ክፉ በሚያደርጉ ሰዎች ምክንያት ደማቸው የፈሰሰው ፣ ወደ እግዚአብሔር ከመጮህ አያቋርጥም። እርግማኑ በበዳዩና ክፉ አድራጊው ላይ ብቻ ሳይሆን ፣ በዘሩ ፣ በማንዘሩ ፣ በከብቱ ፣ በሀብቱ ፣ በሚያርሰው ምድር ሳይቀር የሚፈጸም ነው። ገበሬ የሚዘራውን ያጭዳል። መከሩም ደርሷል። ኮርቻውም ዘሟል። ከመውደቁ በፊት አስተካክለው። ኮርቻቸው ዘምሞ ሳያስተካክሉ የወደቁትን እነሳዳም ፣እነሙባርቅ ፣ እነጋዳፊ ምሳሌ ይሁኑህ። “ንስሐ ግባ፤ አለዚያ ቶሎ እመጣብኃለሁ ፤ በአፌም ሰይፍ እዋጋኃለሁ” ይላል የሠራዊት አምላክ እግዚአብሔር።
፭/ ገዳዩ ቃየል ከእግዚአብሔር ፍርድ በኋላ፤ ምን አለ?
“ቃየልም እግዚአብሔርን እንዲህ አለው ፥ ቅጣቴ ከምሸከመው በላይ ነው። እነሆ ዛሬ ክምድሪቱ አሳደድከኝ፤ ከፊትሕም እሸሻለሁ ፤ በምድር ላይ ኮብላይና ተቅበዝባሽ እሆናለሁ፤የሚያገኘኝ ሁሉ ይገድለኛል።” ቃየል ከፈጸመው በደል የተነሣ በደረሰበት የእርግማን ምት ለራሱ አዘነ እንጂ ኃጢአቱን አስቦ ፤ ጸጸቱ የንስሐ ፀፀት አልነበረም። ይባስ ብሎ ኃጢአትን በኃጢአት ላይ እየደራረበ ይፈጽም ነበር። ለምሳሌ በምንባቡ እንደተገለጸው፤ እግዚአብሔርን ናቀ፤ ቀናተኛና ነፍሰ ገዳይ ሆነ፤ ዋሾና እራስ ወዳድነቱን አጠነክረ፤ የዚህ ሁሉ ውጤት ከእግዚአብሔር እንዲለይ አድረገው። የዚህ ዓይነቱን ጸጸት በሐዲስ ኪዳን ይሁዳም ደግሞታል። የኢትጵያ መንግሥት ገና ከጅምሩ እያቃጠለ እያፍረሰ እየገደለ እንደመጣ የቅርብ ጊዜ ተውስታ ነው። ኦርቶዶክሱንና አማራውን ለማዳክምና ብሎም ለማውደም የቤት ሥራ ተስጥቶት በደደቢት የተቀበለው የጥፋት ወንጌል ነው። በትረ–መንግሥቱን ከጨበጠም በኋላ በጎንደር መካነ ኢየሱስ አደባባይ፣ በአዲስ አበባ እስጢፋኖስ ቤተ ክርስቲያን ፣ ቃየላዊ ግድያን ፈጽሟል። የዋልድባ ገዳማትን መዝብሯል። መነኮስቱ ታሥረዋል ፤ መነኮሳይያቱም ተደፍረዋል። እስከ አሁን በአደረገው ወንጀል እንዲጸጸትና ንስሐ እንዲገባ ጊዜ ተሰጠው፤ ብሔራዊ እርቅና ይቅርታ እንዲያመጣ ተነገረው፤ ይባስ ብሎ ጸጸቱን ወደ ቁጭትና ጭካኔ በመለወጥ በአለፈው ሳምንት በወልድያ የጥምቀትን በዓል በማክበር ላይ ባሉ ክርስቲያኖች ላይ ጭፍጨፋ እንዲፈጸምባቸው ተደረገ። በሃያ አንደኛው መቶ ክፍለ ዘመን በጅማ ክፍለ ሀገር በሻሻ አቡነ አረጋዊ ቀበሌ በአረማውያን የታረዱ የመጀሪያዎቹ ሰማዕታት ሲሆኑ ፣ በሊብያ በውቅያኖስ ዳርቻ በአይሲሲ የታረዱና የተረሸኑ ሁለተኛው ሰማዕታተ–ኢትዮጵያን እናስታውሳቸዋለን። የኢትዮጵያ ሥርወ–መንግሥት መጀመሪያ የብሉይ ኪዳን መሠረቱ የክርስትና ምንጩ በአኩስምና በአድዋ ተወላጆች ክርስቲያኖች በክርስቲያኖች የተሰዉ ሦስተኞቹ ሰማዕታተ–ወልድያ በመባል ሲታሰቡ ይኖራሉ።
በመጨረሻም
ይድረስ ለኢትዮጵያ መንግሥት፥
ሀ/ ለሃያ ዓመታት ያህል መንጋውን እንድትመራ ሥልጣኑ ተሰጠህ ያከበረህን እግዚአብሔርን ናቅኸው፤ እሱም የሰጠህን የመሪነት ሥልጣኑን ከአንተ ወስዶታል። በሌለህ ሥልጣን ሕዝብ አታስፈጅ ፣ ንብረት አታውድም “ክወደቁ በኋላ መንፈራገጥ ለ….” እንደተባለው ይሆንብኃል።
ለ/ አሁንም ጀንበሯ ለመጥለቅ እየፈጠነች ነውና ጨርሳ ከመጥለቋ በፊት የናቅኸውን ፈጣሪህን ተማለለው ፤ ንስሐ ግባ ፤ ሕዝብን ይቅርታ ጠይቅ።
ሐ/ “ሰው ሌላውን ቢበድል እግዚአብሔር ጣልቃ ገብቶ ይፈርዳል ፤ ሰው እግዚአብሔርን ቢበድል ማን ይማልድለታል?” የተባለው በአንተ እየተፈጸመ ነውና የአለህበትን ጊዜ ፣የቆምክበትን ሥፍራ ተመልከት።
መ/ ለአሥራ ሰባት ዓመታት በበረሃ የተንክራተትከው ፣ የተገርፍከው ፣ የሞትከው ፣ ከደርግ ጋር የተፋለምከው ፣ ደርግን ተክተህ በቀልህን በመውጣት ወንድምህን (ወገንህን) ለማሠር ፣ ለመግረፍ ፣ ለማሰቃየትና ለመግደል ነበርን? የነበርክበትን አስብ። ብላቴን ጌታ ኅሩይ ወ/ሥላሴ በንጉሠ ነገሥቱ ጊዜ የውጪ ጉዳይ ሚኒስተር ነበሩ፤ የአብነት ተማሪ በነበሩ ጊዜ ይለብሷት የነበርችውን ደበሎ ሳሎን በክብር ቦታ አስቀምጥዋት ነበር ይባላል፤ «ምነው ?» ተብለው ለተጠየቁት ጥያቄ «የነበርኩበትን እንዳልረሳ» አሉ ይባላል።
ሠ/ ይድረስ ለቤተ ክርስቲያን መሪዎች ፥ ቤተ ክርስቲያኒቱን እንደጥገት የምታልቧት ፤ በዚህ ዘመን ያላችሁ ከጥቂቶች በቀር ጳጳሳት ፣ መነኮሳት ፣ ቆሞሳት ፣ ቀሳውስት ፣ ሰባክያን ፣መዘምራንና የማኅበራት አባላት ፤ እንዲሁም በክርስትና ስም የምትነግዱ ፓስተሮች ፤ በኢትዮጵያ ለፈሰሰውና ለሚፈሰው ደም ተጠያቂዎች ናችሁ(ነን)። ለምን እንደሆነ እናንተም ታውቁታላችሁ ፤ ለሚጠይቀኝ መልስ አለኝ።
ረ/ ይድረስ ለኢትዮጵያ ተቃዋሚ ኃይሎች፥ በውስጥም ፣ በውጪም የአላችሁ “ጨቋኝ ለመሆን ጭቆናን መቃወሙን አቁሙ(እናቁም)። ደርግና ወያኔ አንግበው የመጡት ምን እንደነበር ፣ ምን ሠርተው እንደአለፉ ፣ ምን እየሠሩ እንደሆነ ትምህርት ይሁናችሁ(ይሁነን)። ኢትዮጵያ ሀገረ-እግዚአብሔር እንደሆነች በመጽሐፍ ቅዱስም ሆነ በቁራኑ ይነበባል፤ ሕዝቧም እድሉ እግዚአብሔር ነው። እምነቱን ለፖለቲካ ግባት አናድርገው(አታድርጉት)። እግዚአብሔር እውነት ፣ ቅን ፣ ፍቅር ነው። በእውነት ፣ በቅንነትና በፍቅር ላይ የተመሠረት የፖለቲካ ዓላማና ግባት ይኑረን (ይኑራችሁ)።
ሰ/ ይድረስ ለኢትዮጵያ ሕዝብ፥ የአርባ ዓመታት የፖለቲካ ፣ የንውውጽታ ዘመን አሳልፈሐል ፤ የአለፉት የመክራና የስቃይ ዘመናት ትምህርት ሊሆኑህ ይገባል። ደግመህ ያለፈውን ስሕተት እንዳትፈጽም ተጠንቀቅ። በእሳት አትጫወት ፤ ተቃውሞህ በጥበብና በማስተዋል ይሁን። ጠላት በአንተ ሊጠቀም ያስታጠቀህን የዘር ትጥቅህን ፈትተህ ጣለው።ዘርህ ኢትዮጵያዊነት ነው። ኢትዮጵያዊነትህ ደግሞ መታወቂያህ ፣ ክብርህ ፣ ሞገስህ ፣ ድልህ ፣ ሐብትህ ፣ ንብረትህና ሕይወትህም ነው።
ሸ/ ሀገር የምትመራው የመምራት ጸጋው (ክራዝማው) የተሰጣቸው እንደነ ሙሴ ፣ ዳዊት ሰሎሞንና ጌድዮን ያሉ በፖለቲካ ሰዎች(ምሁራን) ነው። እግዚአብሔርን የሚያስቀድሙ ፣ሕዝብን የሚያከብሩ (ፍቅረ እግዛብሔርና ፍቅረ ቢጽ የአላቸውን) መሪዎችህን ምረጥ።”ተከትል አለቃህን ፣ ተመልከት ዓላመህን” እንደሚባለው ፣ የመረጥካቸውን መሪዎችህን ተከትል ፤ ዓላማህን የኢትዮጵያን አንድነት ተመልከት።
ቀ/ ይድረስ ለዲስና ለአካባቢው ማኅበረ ምዕመናን፥
በዲሲ በአካባቢውና በዝርወት ለአላችሁ ማኅበረ ምዕመናን ፥ በሀገራችን ለተከሰተው ፣ እየተከሰተ ለአለው ግድያ ፣ ንውውጽታ ግድ ይለናል። አፍ ላጣው አፍ ፣ ምግብ ለአጣው ዳቦ ፣ ቤት ለአጣው መጠለያ ፣ ጤና ላጣው ህክምና ፣ ለተራቆመተው ልብስ ልንሆነው ይገባል። እንደየአቅማችን ፣ እንደ ችሎታችን ፣በሁሉም አቅጣጫ ልናደርግ የሚገባንን እናድርግላቸው። ትልቁና መልስ የምናገኝበት ወደ እግዚአብሔር በጸሎትና በምልጃ መቅረብ ነው። ሀገራችንን ክፍርስራሽ ክምር ፣ ከእሳት ቃጥሎ ፣ ከሙታን ከተማ ፣ ከተቃጣው ሠይፍ ፣ ክተወረወረው ጦር ፣ ማዳን የሚችል እግዚአብሔር ብቻ ነው። ቅንቅን ከሆነብን ቅናትና ምቀኝነት ፣ እንደ ጦር ከሚወጋን ቂም ፣ እንደ ሰይፍ ከሚቆራርጠን በቀልና ጥላቻ እንላቀቅ። እርስ በርሳችን ክልብ ይቅር እንባባል። የመምሰልና የማስመሰልን ይቅርታ እግዚአብሔር ይጸየፈዋልና ከዚህ እንራቅ። በአለፈው የልደት ማግሥት ጀምረን ለአምስት ቀናት እንደአደረግነው ፣ ዛሬም ከነገ ጥር ፳፩ ቀን ጀምሮ እስክ ጥር ፳፭ ቀን ድረስ ሦስቱን የነነዌ ጾም ቀናት እስከ ሠርክ በመጸም ፤ የሠርክ ጸሎት በሚካሄድባቸው አብያተ ክርስቲያናት በመገኘት ፣ የምኅላ ጸሎት ማድረስና ምንባባቱ ሰቆቃው ኤርምያስ ከምዕራፍ አንድ እስክ አምስት በተመቸ ጊዜያት ፣ በግልም ፣ በኅብረትም በአንብአ ንስሐ ሆነን እንድናነበውና እንድንጸልይ ፣ በእግዚአብሔር ስም የአደራ መልዕክቴን በአክብሮት አስተላልፋለሁ።
እግዚአብሔር ሀገራችንንና ሕዝባችንን ከተቃጣው ሠይፍ ክተወረወረው ጦር ይታደግልን።
አሜን።
ሊቀ ማእመራን ቀሲስ ዶክተር አማረ ካሣዬ (amare.kassaye @gmail.com)
በዝርወት ላይ ያለችው የርእሰ አድባራት ደብረ ሰላም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን አስተዳዳሪ
ዋሽንግተን ፣ ዲሲ