Mamushet 469x555

የካቲት 7 2010 ዓ. ም

ትላንትና በቀለ ገርባ እና ጓደኞቹ ከእስር መፈታታቸው ይታወቃል:: በዛሬው ዕለትም መንግስት ተጨማሪ ሰባት መቶ አርባ ስድስት የፖለቲካ እስረኞችን ፈቷል::

ማሙሸት አማረ ፤ አንዱዓለም አራጌ ፤ እስክንድር ነጋ ፤ እማዋይሽ ዓለሙ ፤ ክንፈሚካኤል ደበበ ከተፈቱ የፖለቲካ እስረኞች ውስጥ ይገኙበታል::

በመቶዎች የሚቆጠሩ ደጋፊዎቻቸው በቃሊቲ ማረሚያ ቤት በር ተሰባስበው ለተፈቱት የፖለቲካ እስረኞች ደማቅ አቀባበል አድርገዋል::

ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ሰላማዊ ትግሉን እንደሚቀጥል ወኔ እየተናነቀው ለደጋፊዎቹ ተናግሯል:: እስክንድር ነጋ እና አንዱዓለም ጌታቸው መንግስትን በኃይል ለመጣል አሲራችሁአል በሚል የሃሰት ውንጀላ የአስራ ስምንት እስራት ተፈርዶባቸው ለሰባት ዓመታት ያህል በግፍ መታሰራቸው ይታወቃል::

ወ/ሮ እማዋይሽ አለሙ ከነ ጄኔራል አሳምነው ጽጌ ጋር በመፈንቅለ መንግስት ሙከራ ተከሰው ብዙ ግፍ እና መከራ ተቀብለዋል:: የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጂት አመራር የሆኑት ማሙሸት አማረ ለበርካታ ዓመታት ሲታሰሩ እና ሲፈቱ የቆዮ ሲሆን ዛሬ በመፈታታቸው የተለየ ደስታ እንዳልተሰማቸው እና ደስተኛ የሚሆኑት የኢትዮጵያ ህዝብ ነጻ ሲሆን መሆኑን ተናግረዋል::

የፖለቲካ እስረኞቹ የተፈቱት መንግስት በታህሳስ ወር የ”ዲሞክራሲ ምህዳሩን ለማስፋት” እና “ለብሔራዊ መግባባት” እስረኞችን እለቃለሁ በማለት ካሳወቀ በኋላ ነው፥፥ ሆኖም አሁንም ቢሆን እነ አንዳርጋቸው ጽጌን ጨምሮ በርካታ የፖለቲካ እስረኞች አልተለቀቁም::