ሙሉነህ ዮሐንስ እንደዘገበው

ከጎንደር ከተማ 100 ኪ.ሜ እርቃ በምትገኘው የራስ ዳሸን ተራራ ፈርጥ በሆነችው ደባርቅ ከተማ ውጥረት ነግሷል። የእጅ ቦንብ ጥቃቱ የተፈፀመው በ25/06/2010 ከምሽቱ አምስት ሰዓት ሲሆን የከተማውን ከንቲባ ቢሮና ፍትህ ፅህፈት ቤትን ኢላማ በማድረግ እንደነበር ምንጮች ይጠቅሳሉ። በሚቀጥለው ቀን የስርአቱ የፀጥታ ኃይሎችን እንዲሁም የደህንነት ኃላፊዎችን ለታላቅ ድንጋጤ፣ ስጋትና ፍርሃት ዳርጓቸው ተስተውሏል። የአካባቢው ሚሊሻና ልዮ ኃይል አባላት አካባቢውን ወረው በስጋት ሲጠብቁ ታይተዋል። ህዝቡ ግን በሁኔታው ተደስቶ መነጋገሪያ አድርጎታል። ተቋማቱ ህዝብ መበደያ እና የህወሃት ተላላኪ የሆነው የብአዴን ማእከላት ስለሆኑ ይውደሙ ነው ያለው።

ለጊዜው ማንነታቸውን መግለፅ ያልፈለጉት አካላት እንደገለፁት በቀጣይ ተመሳሳይ ጥቃቶችን በተጠናከረ መልኩ እንደሚፈፅሙ ጠቅሰዋል፡፡ የተያያዘው ምስል ከቦታው የተወረወረው የእጅ ቦንብ ንቃይ መሆኑን መረጃውን የላኩልን አካላት ገልፀዋል።

በሌላ ዜና ደግሞ በመተማ መስመር ያለችው ነጋዴ ባህር ከተማ ላይ አጋዚ ህዝቡን እያሸበረ ይገኛል። ሰበብ አድርገው ሰዎችን እያሰሩ መሆኑን አጣርተናል። ነጋዴ ባህር ከጎንደር ከተማ ወደ 80 ኪ.ሜ. እርቃ የምትገኝ ስትሆን ህዝቡ የድረሱልን ጥሪ እያሰማ ነው።

ከጎንደር እና ጎጃም ወደ አዲስ አበባ የመጓጓዣ አገልግሎት ሙሉ ለሙሉ እንደተቋረጠ ነው። በመላው የአማራ ክልል ወጥ የሆነና የተቀናጀ ህዝባዊ አመፅ ለማድረግ ዝግጅት እየተደረገ ነው። ይህ በኦሮሚያ ካለው ጋር ተቀናጅቶ መላ ኢትዮጵያን የሚያናውጥ ህዝባዊ ማእበል እንደሚደረግ ከተለያዩ አካላት የሚመጣው መረጃ ያሳያል።