በቂሊንጦ በእስር ላይ የሚገኙ የ71 አመቱ አዛውንትና አባት መርጌታ ዲበኩሉ አስማረ ቦጋለ

በእስር ላይ የሚገኙት ሌላኛው የእምነት አባት! (ጌታቸው ሽፈራው)

መርጌታ ዲበኩሉ አስማረ ቦጋለ የ71 አመት አዛውንት እንደሆኑ ክሳቸው ላይ ተጠቅሷል። ጎንደር ባለወልድ ቤተ ክርስትያን አገልጋይ በነበሩበት ወቅት ለእስር ተዳርገዋል።

በእነ ክንዱ ዱቤ ክስ መዝገብ 6ኛ ተከሳሽ የሆኑት መርጌታ ዲበኩሉ የታሰሩት ቤተ ክርስትያንን በማገልገል ላይ እያሉ ነበር። ሆኖም”ለአርበኞች ግንቦት 7 አባላትን በመልመልና በመላክ፣ በማሰልጠን፣ ለሰልጣኞች ትጥቅና ስንቅ በመግዛት፣ ………” የሚል ክስ ተዘርዝሮባቸዋል።

ከ15 አመት እስከ ሞት የሚያስቀጣ የ”ሽብር” ክስ ተመስርቶባቸዋል። መርጌታ ዲበኩሉ ለወራት ማዕከላዊ ጨለማ ቤት በመታሰራቸው አይናቸው እንደተጎዳ፣ ከማዕከላዊ ከወጡ በኋላም ህመሙ እንደበረታባቸው በተደጋጋሚ ለፍርድ ቤት አመልክተው ነበር። ሆኖም አሁንም ሕክምና አላገኙም። መርጌታ ዲበኩሉ ቂሊንጦ እስር ቤት ይገኛሉ።

ቴዎድሮስ አስፋው አለም ደግሞ በትግሬ ወያኔ ከጎንደር ታፍነው አዲስ አበባ ተወስደው በግፍ ቂሊንጦ እስር ቤት ውስጥ እየተንገላቱ ስለሚገኙት ወግኖች የሚከተለውን ጽፏል።

~ “እየተመገብንና እየጠጣን ያለው አሸዋ ነው” ተከሳሾች

~ “ስሜ መሪጌታ ዲበኩሉ አስማረ እንጂ ወይዘሪት ዲበኩሉ አስማረ አይደለም”

~ የመቃወሚያ ብይን ለመስጠት 9 ወር ፈጅቷል

በፀረ ሽብር አዋጅ አንቀፅ 3 ንዑስ አንቀፅ 1 ተጠርጥረው በነ አቶ ክንዱ የክስ መዝገብ ክስ የተመሰረተባቸው 8 ተከሳሾች መጋቢት 3 ቀን 2010ዓ.ም የክስ መቃወሚያ ብይን ለመስጠት ለዛሬ መጋቢት 6 ቀን 2010ዓ.ም ተቀጥሮ በነበረው መስረት ተከሳሾች የሚመለከታቸው አካላት ከጠዋቱ 3 ሰዓት ጀምሮ ችሎቱ በሚካሄድበት የልደታ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 4ኛ ወንጀል ችሎት አዳራሽ ውስጥ የተገኙ ቢሆንም ችሎቱ ግን 5 ሰዓት ላይ ተጀምሯል።

የመሀል ዳኛው ዳኛ በመጓደሉ ምክንያት መዘግየታቸውን ገልፀው ዘግይተው በመጀመራቸው ይቅርታ በመጠየቅ ከሳሽ ዐቃቤ ህግ የተከሳሽ ጠበቆች እንዲሁም ተከሳሾች መኖራቸው በስም ጥሪ በሚያረጋግጡበት ግዜ 6ኛ ተከሳሽ መሪጌታ ዲበኩሉ አስማረን ወይዘሪት ዲበኩሉ ሰመረ ብለው በመጥራታቸው ተከሳሹ ስሜ መሪጌታ ዲበኩሉ ሰመረ እንጂ ወይዘሪት ዲበኩሉ አስማረ አይደለም በማለት ስማቸው እንዲስተካከልለት ጠይቀዋል።

በዚህም መሰረት ዳኛው መዝገቡ ላይ ወ/ት ተብሎ መመዝገቡን ገልፆ ለስህተቱ ይቅርታ ጠይቋል። በመጨረሻም የክስ መቃወሚያ ብይኑን በዳኛ መጓደል ምክንያት እንዳልሰሩት በመግለፅ ተለዋጭ ቀጠሮ ለመስጠት የተከሳሽ ጠበቆችና ተከሳሾች አስተያየት እንዲሰጡ ጠይቀዋል።

ከ2ኛ እስከ 6ኛ እና የ10ኛ ተከሳሾች ጠበቃ መዝገቡ በዚህ ሳምንት ብቻ ብይን ለመስጠት ለ3ኛ ግዜ መቀጠሩን በመግለፅ የአሁኑ ቀጠሮ የመጨረሻ እንዲሆን ጠይቀዋል። 7ኛ ተከሳሽ ሀብታሙ እንየው መዝገቡ እየተጓተተ ያለው በኔ የመቃወሚያ ብይን ነው ይህም 9 ወር መፍጀቱ አሳዛኝ ነው ብሏል። ከዚህ በተጨማሪ 10ኛ ተከሳሽ ለገሰ ወልደሃና በማረሚያ ቤቱ የሚቀርብልን ምግብና መጠጥ አሸዋ ያለበት በመሆኑ በተደጋጋሚ ግዜ እንዲስተካከልልን ለአስተዳደሩ ብናቀርብም መልስ ማግኘት ስላልቻልን ፍርድ ቤቱ ውሳኔ ይስጥልን ሲል አቤቱታውን በጽሁፍ ጭምር አቅርቧል።

የመሀል ዳኛው ፍርድ ቤቱ በማረሚያ ቤቱ የውስጥ አስተዳደር ጣልቃ የማይገባ ቢሆንም የምግብና የመጠጥ አቅርቦቱን በሚመለከት አስተዳደሩን ጠርተን እናናግራለን ዛሬ ከሰዐትም አጠቃላይ የፍትህ አካላት ውይይት ያለ በመሆኑ በዚሁ አጋጣሚ መልስ እንደሚያገኝ ገልፀዋል። ቀጠሮውንም በሚመለከት ለቀጣዩ ሳምንት ለመጋቢት 13 ጠዋት ላይ እንዲሆን በመወሰን የመጨረሻ እንደሚሆን ገልፀዋል።

የተከሳሾች ስም ዝርዝር
1ኛ. ክንዱ ዱቤ
2ኛ. ዘመነ ጌጤ
3ኛ. ደበበ ሞገስ
4ኛ. ዘራይ አዝመራው
5ኛ. ገብረስላሴ ደሴ
6ኛ. መሪጌታ ዲበኩሉ ሰመረ
7ኛ. ሀብታሙ እንየው
10ኛ. ለገሰ ወልደ ሃና ናቸው
8ኛ እና 9ኛ ተከሳሾች ክሳቸው መቋረጡ በፍርድ ቤቱ ተገልፆል።

ቴዎድሮስ አስፋው አለም እንደዘገበው