እግር ኳስ ኢትዮጵያ ውስጥ አስቀያሚ ገጽታ ይዟል፡፡ ለምሥራቅ አፍሪካና ለአፍሪካ ዋንጫ ማለፍ ቢያቅተን በሰላም መጫወት እንዴት ያቅተናል? እግር ኳሱም ጎጠኛ ሆነና ጥፋትና ጥፋተኛን በድርጊቱ ከመውቀስና ከመቅጣት ይልቅ የዚህ ስለሆነ ነው የዚያ ስለሆነ ነው ወደሚል ደይን ዘቀጠ፡፡
ዳኛና ዳኝነት በሀገሪቱ ያለውን ቦታ እያየን ነው፡፡ ፖለቲካው ሲቪል ዳኝነትን ይደበድባል አምባ ገነን ግለሰቦችና ቡድኖች የእግር ኳስ ዳኝነትን ይደበድባሉ፡፡
እንዲህ ከሆነ እግር ኳስ ምን ያደርግልናል? ለምን ወደ ቦክስ ወይም ድብድብ ስፖርት አንቀይረውም? እንደሚታየው ምርጥ ተቧቃሾችና የቡቀሳ ደጋፊዎች አሉን፡፡ እንደልብህ ትደባደብና ጎሳህ ውስጥ ትደበቃለህ፡፡ እዚህ ሀገር ድብድብን ስፖንሰር የሚያደርገው ብዙ ነው፡፡
ፌዴሬሽኑ በስብሰባው ላይ በውኃ ኮዳ ባርኮ ያስጀመረውን ድብድብ ቡድኖቹ በተሰጣቸው አቅጣጫ መሠረት እየተገበሩት ነው፡፡ ዳኞችም ካሁን በኋላ አምስት ወታደር ካላጀበን አናጫውትም በሉ፡፡ የአትሌቲክሱን አሰልጣኝ የደበደበው ሯጭ ጎሳው ውስጥ ተደብቆ በአንድ በግ ተገላግሏል፡፡ የሚጎዳው ዳኛና አሠልጣኝ ነው፡፡
ለዚህ ውጤት ለራቀው እግር ኳስ ቢቀርስ፡፡ ስታዲዮሙን ጤፍ እንዝራበትና የጤፍ ዋጋ ይቀንስ፡፡ እግር ኳሱ እንኳንስ ዘንቦበት እንዲያውም እንዲያው ነው፡፡
