May 24, 2018
(ዘ-ሐበሻ) የኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳንት አቶ ለማ መገርሳ በኢትዮጵያ ውስጥ እርሳቸው የማያውቁት ድብቅ እስር ቤት ካለ ሕዝብ እንዲጠቁማቸው ጠየቁ።
ፕሬዚዳንቱ በዛሬው ዕለት ለ7611 እስረኞች ምህረት በማድረግ ከ እስር ቤት እንዲለቀቁ አድርገዋል። እስረኞቹም 7183 ወንዶች ሲሆኑ ቀሪዎቹ 428ቱ ሴቶች ናቸው።
ይህን ዜና በቪድዮ ለማየት እዚህ ይጫኑ
አቶ ለማና አስተዳደራቸው ሰላማዊ ዜጎችን አስሯል በሚል በየሄዱበት ሕዝባዊ ስብሰባ ሲወቀሱ ቆይተዋል። ‘እኛ እስረኞችን በየጊዜው እየፈታን ነው። አሁንም እንፈታለን። ሆኖም ግን እኛ የማናውቃቸው እስር ቤቶች ካሉ ጠቁሙንና አብረን የድብቅ እስር ቤቶችን ፈልገን ወገኖቻችንን እናስፈታለ ” ሲሉ ለሕዝቡ ጥሪ አቅርበዋል።
በተለይ በኦሮሞ፣ በአማራ፣ በሶማሊና በደቡብ ክልሎች ላለፉት 27 ዓመታት በርካታ ዜጎች ከቤታቸውና ከስራ ገበታቸው ተወስደው የት እንደደረሱ አይታወቅም። የሕወሓት መንግስትም በትግራይ ድብቅ እስር ቤቶች እንዳሉት የሚታወቅ ሲሆን አቶ ለማ ከልብ ካሰቡበት ይህ አይጠፋቸውም የሚሉ አስተያየት ሰጪዎች አሉ።
በቅርቡ ከትግራይ ድብቁ እስር ቤት ለ24 ዓመታት በኋላ ለቤተሰቦቻቸው ደብዳቤ የሳፉት የሊቁ መምህር አግማሴ ጉዳይ በትግራይ ምን ዓይነት ሰው የማያውቃቸው እስር ቤቶች እንዳሉ ያሳያል የሚሉት አስተያየት ሰጪዎች በቅርቡም የት እንዳሉ የማይታወቁ የኦሮሞና የአማራ ተወላጅ በመቶዎች የሚቆጠር ስም ዝርዝር በሰብ አዊ መብት ተከራካሪዎች እንደተለቀቀ አስታውሰው አቶ ለማ የድብቅ እስር ቤቶችን የሚፈልጉ ከሆነ ወደ ትግራይ ይሂዱ ሲሉ ጥቆማቸውን ሰጥተዋል።
በሌላ ዜና ትናንት ኢትዮጵያ የገቡት የኦሮሞ ዴሞክራሲያዊ ግንባር አመራሮች ዛሬ በብሄራዊ ቤተመንግስት ዶ/ር ዓብይ አህመድና ከአቶ ለማ መገርሳ ጋር ተወያይተዋል። በውይይታቸውም የኢትዮጵያ ብሄራዊ አንድነት ለማጠናከርንና የዴሞክራሲያዊ ሥርዓቱ ስር እንዲሰድ በጋራ ለመስራት መስማማታቸውን የጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽህፈት ቤት አስታውቋል።

