~ ሰበር ዜና ! ክፉ ወሬም ! ኢትዮጵያችን ለሽያጭ ቀረበች
~ ሻጭ: – ህውሓት/ኢህአዴግ
~ ገዢ: – ህውሓት / ኢህአዴግ
~ ደላላው ግን ማነው ?
~ ውድ ጓደኞቼ ፤ ዛሬ ያለወትሮዬ ከኢንተርኔቱ ዓለም ራቅ ብዬ፣ ሀገርም አማን ብዬ ስልኬንም ዘግቼ Die, Der, Das እያልኩ የጀርመን አስኳላን ስቆጥር ነበር የዋልኩት። በአውሮጳ ሙቀት ላይ በስተ እርጅና ፊደል ቆጠራና አስኳላ ሲጨመርበት ደግሞ አስቡት። በዚህ መሃል ፌስቡክ ከተከፈተ ደግሞ ከኢትዮጵያ የሚመጣው ዜና ሁሉ ናላ የሚበጠብጥ፣ አናትም የሚያዞር በመሆኑ ጠርቅሞ መሸምደዱ ይመረጣል። ያለበለዚያ አስኳላን ውኃ በላው ማለት ነው። ወዳጄ በትምህርት መሃል ፌስቡክ ድንገት ከተከፈተ በኋላ አከተመ። ትምህርት ደህና ሰንብቺ ማለት ነው ከዚያ በኋላ Entschuldigung ቢሉ bitte ቢሉ ወፍ የለም። ጭራሽ ሰሚም የለም። ለዚህ ሲባል ቢያንስ ፈተና ሲቃረብ ጠፋ ማለቱ አዋጭ ነው።
የሆነው ሆኖ አሁን ከመሸ ወደ ፌስቡክ መንደራችን ስገባ ዓለም ቀልጦ ጠበቀኝ። የምሰማውን ወሬ ለማረጋገጥ ያለወትሮዬ ኢቲቪን ፈልጌ ሰማሁት። በህይወቴ ለመጀመሪያ ጊዜ ኢቲቪ እውነት ሲናገር ሰማኹት።
~ ከዜናው በኋላ እንዲህ አሰብኩ። የዐማራው መደራጀት ለህውሓት ምቾት አልሰጣትም። በዚያ ላይ ይኼ ጣጠኛ ዲያስፖራ እንደከዚህ ቀደሙ ሁሉ ዶላርን ወደ ሀገር ቤት እንዳይላክ በማሳመፁና በማስቀረቱ ምክንያት የዶላር ጠኔ ያጠናገረው አገዛዙ ” እንደ ወንደላጤ” ቋሚና ውድ የቤት ዕቃ አውጥቶ መሸጥ መጀመሩን የሚያትቱ ዜናዎችን ሰማሁ።
የዶክተር ዐቢይ ግን አልቸኮሉም ? እኔ ግን ሲመስለኝ ፣ ሲመስለኝ፣ ስጠረጥርም እንዲህ ግራ ግራውን አስቤ የሆነ ጥርጣሬ ተከሰተልኝ። ሰሞኑን ዶክተር ኮሎኔር ሆዬ በሰሜን አሜሪካ የስፖርት ውድድር ላይ ጋብዙኝ ብለው አፍ አውጥተው ጠየቀው መከልከላቸው ይታወሳል። እናም አጅሬ ታዲያ ያንን ለመበቀልም ይመስላል፤ እኔ ጋብዙኝ ብዬ ስለምናችሁ እምቢ ያላችሁኝንና አንጀቴን ያሳረራችሁኝን በሙሉ እኔም በተራዬ ይኸው ኢትዮጵያን የምታኽል ታላቅ ሀገር ሽጬ አንጀታችሁን ነው የማሳርረው የሚሉ ይመስላሉ። ለማንኛው ዛሬ ኢትዮጵያ በቁሟ ከነ ህዝቧ ተሽጣለች። አከተመ ።
~ በድመ፣ ሽራሮ፣ ጾረና፣ ዛለአምበሳ፣ ቡሬም ቀደም ብላ ለተሸጠችው ኤርትራ በዛሬው ዕለት ተመርቀውላታል። መቐለ የሚገኘው የአይዴር ትምህርት ቤትም ወደፊት ለሻአቢያ እንደሚመረቅለት አንዳንድ የመቐለ ከተማ ነዋሪዎች በመናገር ላይ ናቸው። አቶ ስዩም መስፍን ግን ምን ይሰማቸው ይሆን ? ባድመ ተወሰነልን ብለው እንደዚያ ሲያስጨፍሩን ውለው አሁን ምን ይሰማቸው ይሆን? ውይ አይ 8ተኛው ሺህ። እነ ነውር ጌጡ የበዙበት ዘመን።
ቀድሞም የኢትዮ ኤርትራው ጦርነት በጠበብ የተዘጋጀ ነበር። ያውም በምክክር። ጦርነቱ የዐማራውን ነገድ ቁጥር ለመቀነስ በጥበብ የተዘጋጀም ነበር። በኤድስ፣ በመርፌ፣ በሽፍታ ስም ከተገደለው ዐማራ ጋር የሚደመር የዘር ማጥፋት ለመፈጸም ሲባል ነው የባድመ ጦርነት የተፈጠረው የሚሉ አሉ። ታዲያ ብልጡ ህውሓት ሆዬ ይኼን የዐማራውን ወጣት ለመቀነስ ታስቦ የተፈጠረውንና ከ120 ሺህ በላይ የዐማራ ታዳጊ ህጻናት የተጨፈጨፉበትን “#የደም” ምድር በዛሬው ዕለት እልልልል ብሎ እያጨበጨበ ለአሳዳጊ አባቱ ለሻአቢያ በነፃ አስረክቧታል ተብሏል።
ይኽቺን [ የባድመን ] ጉዳይ ለመሸፈን ታዲያ አጅሬው ሌላ ያን የተለመደውን ማስቀየሻ ይሁን ወይም ከምር ያመረረ ነገር ብቻ ለጊዜው ያልታወቀ የሽያጭ ጨረታ ካርድም ስቦ አምጥቷል። የቀደሙ መንግሥታት ላባቸውን ጠብ አድርገው ለሀገሪቱ የገቢ ምንጭ እንዲሆኑ የመሠረቷቸውን እንደ አየርመንገድ፣ ቴሌ፣ ኤሌክትሪክ ኃይል፣ የኢትዮጵያ ንግድ መርከብ፣ የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫ ግድቦች፣ የምድር ባቡር ኮርፖሬሽኖችንን በሙሉም ሆነ በከፊል፣ ለሀገር ውስጥና ለውጪ ሀገር ባለሃብቶች ለመሸጥ መወሰኑም ተነግሯል።
እንደተለመደው ገንዘቡም ያለው እንግዲህ ያው እነሱው ጋር ነው። ስለዚህ ገዢም ሻጭም እነሱው ይሆናሉ ማለት ነው። ከዚህ ቀደም የጋምቤላን፣ የቤንሻንጉልንና የአፋር ክልሎችን፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን አዲስ የሚቋቋም ” ዳሎል ባንክ ” የተባለ አክሲዮን የገዙትም የሸጡትም እነዚሁ ባለ ጊዜዎቹ ናቸው። ባለሃብቶች እንዲያው ከባንክ ይበደራሉ እንጂ የተበደሩትን እንደሁ አይከፍሉም። አሁንም ሀገር የዘረፉበት ገንዘብ በእጃቸው ስለሆነ ከያሉበት መጠተው እነዚህኑ ለጨረታ የቀረቡትን የኢትዮጵያ ንብረቶች በጅምላ ይገዟቸዋል ማለት ነው። አዳሜ ዐይንህ እያየ አብረህ ትሸጣለህ። ለማንኛውም ኢትዮጵያ ከነ ህዝቧ ተሽጣ ለማየት ስለበቃን እንኳን ደስ ያለን።
እንግዲህ ሻጮቻችን እስከ አሁን ” የኤርትራ ተላላኪ ” በማለት በየወኽኒ ቤቱ ያጎሯቸውን ዜጎች በአስቸኳይ ቢፈቱ ለራሳቸው ለአሳሪዎቹ ጤንነት መልካም ነው። ምክንያቱም በሽያጩ ብር ጥቂት ጊዜም ቢሆን ዘና ብለው እንዲከርሙ እንዲያ ቢያደርጉ መልካም ነው። ሌላ የዳቦ ስም ፈልገው በአዲስ መልክ ዜጎችን እስኪያስሩና ደግሞም ከሻአቢያ ጋር የመላላኩን ሥራ ራራሳቸው ከሳሾቹ በክብር ስለወሰዱት በዚህ ስም ማሰሩ ቢበቃ መልካም ነው። ኧረ እንዲያው ለመሆኑ ለኤርትራ እነ ባድሜ ከተሰጡ ለሻአቢያ ተላላኪዎች ምን ሊሰጣቸው ነው። ለላኪዋ ትግራይ ተቆርሳ ከተሰጠች ለተላላኪዎቹ ምን ሊሰጣቸው ይሆን? ።
መቆሚያውን አላወኩትም እንጂ ከወደ ሰሜን የሚነሳ እሳት ማጥፊያም ያለው አይመስልም። ሰደድ እሳቱ ቤንዝንና ጭድ እየቀረበለትም ነው። በፍጥነትም እየተቀጣጠለ ነው። በተለይ ይኼ የዐማራው ከየቦታው የመፈናቀል፣ የመገደል፣ የመዘረፍ፣ የመሰደድ ጉዳይ በቅርቡ የሚያመጣውን ጣጣ ለማየት ያብቃን። ከምር ዕድሜ የሰጠው ሰው ቁጭ ብሎ ውጤቱን ያየዋል።
እመኑኝ የኢትዮጵያ ትንሣኤ በዐማራው መመከትና፣ ጨከን ፣ ቆረጥ፣ ደፈር ማለት በቅርቡ ይበሠራል። ቱ ምንአለ በሉኝ። ኤርትራም ወደ እናት ሀገሯ ትመለሳለች። ህውሓት ግን እንደጉም ብን ብላ ትጠፋለች። ያውም በትግራይ ልጆች በትር ። አከተመ ።
በመጨረሻም ! እንዲህ ማለት አማረኝ።
የኢትዮጵያ ቴሌኮምኒኬሽን በእምዬ ሚኒሊክ ተመሠረተ። የኢትዮጵያ ቴሌኮሚንኬሽን በህውሓት ተሸጠ።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ በግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ተመሠረተ።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ በህውሓት ተሸጠ።
የኢትዮጵያ መብራት ኃይል ኮርፖሬሽን በጃንሆይ ተመሠረተ
የኢትዮጵያ መብራት ኃይል ኮርፖሬሽን በህውሓት ተሸጠ
የኢትዮጵያ ባህር ኃይል በአጼ ካሌብ መሠረቱ ተጥሎ በአጼ ኃይለ ሥላሴ በዘመናዊ መልኩ ተመሠረተ።
የኢትዮጵያ ባህር ኃይል በህውሓት ፈረሰ።
የኢትዮጵያ ንግድ መርከብ ድርጅት በአጼ ኃይለሥላሴ ተመሠረተ
የኢትዮጵያ ንግድ መርከብ ድርጅት በህውሓት ፈረሰ።
የኢትዮጵያ ባቡር ድርጅት በእምዬ ሚኒሊክ ተመሠረተ
የኢትዮጵያ ንግድ ድርጅት በህውሓት ተሸጠ
ራሷ ኢትዮጵያ በእግዚአብሔር ተፈጠረች
ራሷ ኢትዮጵያ በህውሓት ተሸጠች።
ይኸው ነው።
ሀገሬ ተደፈረች ብለው አካኪ ዘራፍ ብለው በባድመ ደማቸውን አፍስሰው ለሞቱት ብዙ ዐማሮች ጥቂት ብሔር ብሔረሰቦች ነፍሳቸውን ይማርልን !
ሻሎም ! ሰላም !
ዘመድኩን በቀለ ነኝ
ግንቦት 28/2010 ዓም
ከራየን ወንዝ ማዶ።