“እግዚአብሔርም ሳሙኤልን አለው። እነሆ የሰማውን ሁሉ ሁለቱን ጆሮዎቹን ጭው የሚያደርግ አንድ ነገርን በእስራኤል አደርጋለሁ!” 1ኛ ሳሙ. 3፤11
የካህኑ ዔሊ ለደፋርና በእግዚአብሔር ላይ ላመፁ ልጆቹ ማድላትና ለሕገ እግዚአብሔር፣ ለእግዚአብሔር ክብር አለመቅናት እግዚአብሔርን የመናቅ፣ ክብሩን የመድፈር፣ ልዕልናውን የማዋረድ ከባድ ኃጢአት ሆኖ ተቆጥሮባቸው ሕዝበ እስራኤልን በጠላቶቻቸው ድል እንዲመቱና ታቦተ ሙሴ ወይም ጽላተ ሙሴ ተማርካ በአሕዛብ እጅ እንድትወድቅ አድርጎ ከላይ የጠቀስኩት የነቢዩ የሳሙኤል ትንቢት ወዲያው ተፈጽሞባቸዋል፡፡ 1ኛ. ሳሙ. 4፤1-22
ሰሞኑን የሱማሌ ክልል በሚሉት ዐሥራ አንድ አብያተክርስቲያናት መቃጠላቸውን፣ ካህናትና ምዕመናን በአሰቃቂ ሁኔታ ተገድለው መቃጠላቸውን ሰምተናል፡፡
የእግዚአብሔር ፍርድ መፍጠኑ በእጅጉ ገረመኝ እንጅ ይሄ እንደማይቀርልህ አስቀድሜ ነግሬህ አስጠንቅቄህም ነበረ፡፡ ገና ገና መግቢያ እስክታጣ በአራቱም አቅጣጫ እሳት ይነድልሃል፡፡ የዚህን መዓትና ቁጣ ምክንያት የተረዳ ሰው ለመኖሩ እጠራጠራለሁ፡፡
ቀኖና ቤተክርስቲያንን “የኦርቶዶክስን አከርካሪ እንዳያንሠራራ አድርጌ ሠብሬያለሁ!” ብሎ በአደባባይ ለሚፎክር ፀረ ቤተክርስቲያን አላዊ አገዛዝ ጥቅም፣ ፍላጎትና ምቾት ሲባል ያውም “በጎቸን፣ ጠቦቶቸን፣ ግልገሎቸን ጠብቅ!” ተብለው በእረኝነት የተሾሙት ሰዎች ከነፍስ መከራ ይልቅ የሥጋ መከራ ከብዶባቸው፣ ከዘለዓለማዊው ፍዳ ይልቅ ጊዜአዊው ፍዳ አስፈርቷቸው፣ ከሰማያዊው ክብር ይልቅ ምድራዊው ክብር በልጦባቸው በእግዚአብሔር ላይ በማመፅና ለሥጋ ለባሽ በመታዘዝ ቀኖና ቤተክርስቲያንን፣ ሕገ ቤተክርስቲያንን በይፋ በአዋጅ በመጣስ፣ በመሻር፣ በማፍረስ የእግዚአብሔርን ክብር በመድፈራቸው፣ በመናቃቸውና በመርገጣቸው ይሄ የሰማውን ሁሉ ሁለቱን ጆሮዎቹን ጭው የሚያደርግ መዓትና ቁጣ እረኛ ተብየዎቹ ቀኖና ቤተክርስቲያንን በሻሩለት አላዊ አገዛዝ አሳዛኝና እጅግ ነውረኛ ሸፍጥ ሊፈጸምብን ችሏል፡፡
እና ታዲያ የአንድ ካህን የዔሊና የሁለት ልጆቹ በደል ሕዝበ እስራኤልን ለዚያ ሁሉ መከራ ዳርጎ፣ ታቦተ ጽዮንንም አስማርኮ የዚህ ሁሉ የአላዊው ፀረ ቤተክርስቲያን አገዛዝ የወያኔ አገልጋዮች ቅጥረኛ ጳጳሳትና ካህናት ተብየዎች በደል፣ ድፍረትና ንቀት ምንም ቅጣት ላያመጣብህ ኖሯል???
እግዚአብሔር አገልጋዮቸ ባላቸው ሰዎች ለአላዊ አገዛዝ ተብሎ ተንቆ፣ ተደፍሮና ተዋርዶ ሰላም እንዲኖርህ ትመኛለህ??? እንቅጩን ልንገርህ አይደል? ከዚህ በኋላ መልካም ቀን የለም!!!
ልዑል እግዚአብሔር ለንስሐ ሞት ያብቃን!!! በል ብልህ ከሆንክ፡፡
ሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው
amsalugkidan@gmail.com