በኢትዮጵያ ውስጥ የተከሰተው የለውጥ ሂደት የከፈተውን ዕድል በመጠቀም ሕብረቱ የተቋቋመበትን ዓላማ ለሕዝብ ለማስረዳትና እንቅስቃሴውን በአገር ደረጃ ለማካሄድ የሚችልበትን መንገድ ለማመቻቸት በዛሬው እለት ሦስት የምክር ቤት አባላት ወደ ኢትዮጵያ ተጉዘዋል።
የምክር ቤቱ አባላት ከሕብረቱ አባል ከሆነው የጎንደር ህብረት ለኢትዮጵያ አንድነት ማህበር ልዑካን ጋር አብረው የሄዱ ሲሆን ፣የጎንደር ህብረት የክፍላተሃገሩ ሕብረት አባል በመሆኑ የምክር ቤቱ አባላት በሚያደርጉት እንቅስቃሴ ሁሉ ተካፋይ በመሆን የታቀደውን ተግባር የማሳካት ግዴታውን ለመወጣት ቃል ገብቷል።
የኢትዮጵያ ክፍላተ ሃገር ህብረት ከአንድ ዓመት በፊት በአሜሪካ ሴያትል ከተማ ውስጥ በአምስት ክፍላተሃገር ተወላጆች በተመሰረቱ ማህበራት የተቋቋመ ህብረት ሲሆን ከዚያ ወዲህ የሌሎቹ ክፍላተ ሃገር ተወላጆች በማህበር ተደራጅተው በመቀላቀል የሕብረቱ አባላት ቁጥር እያደገ በመምጣት ላይ ይገኛል።
የህብረቱ ዓላማ
1 በኢትዮጵያ ውስጥ ላለፉት 27 ዓመታት የሰፈነው የዘርና የጎሳ ፖለቲካ ተወግዶ የአገር አንድነትና የሕዝቡ ሰላማዊ ኑሮ የሚረጋገጥበትን ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ለማስፈን
2 በጎሳና በቋንቋ ተዋረድ ሕዝብ በጠላትነት እየተያዬ እርስ በርሱ እንዲጋጭ፣የተገነባው የክልል ግምብ ፈርሶ ሃገራዊ የአንድነት ድልድይ እንዲገነባ የድርሻውን ለማበርከት
3 አሁን የሚታዬው አገር በጎሳ ተከፋፍላ ሕዝቡም ተነጣጥሎ የመበታተኑ አደጋ የሚወገደው በሕዝቡ ነባር ስብጥርና አገራዊ አወቃቀር መሆኑን በማመን በቀድሞው የክፍላተሃገር አወቃቀር ቢሆን የተሻለ መሆኑን ለሕዝቡ ለመግለጽና ለዚያ ውጤት ለማብቃት፣-
4 የቀድሞ ክፍላተሃገር አወቃቀር ሲባል የቀድሞውን ስርዓት ለመመለስ ሳይሆን ከቀድሞው ታሪክ፣ባህልና ልማድ መልካሙን እየወሰዱ የሚሻሻለውን በማሻሻል አገርን መገንባት እንደሚቻል በሚል እምነት በመነሳት የፌዴራላው አስተዳደሩ ፍጹም ዴሞክራሲያዊና ለሕዝቡ የሚበጅ፣ሕዝቡም የአስተዳደሩ ባለቤት የሚሆንበትን ስርዓት ለማስፈን እንደሆነ በግልጽ ለማስተዋወቅ ነው።የክፍላተሃገር አስተዳደር በሌሎቹም አገሮች የተለመደና ስኬታማ ሰላምና እድገትን ያበሰረ መሆኑን ከአሜሪካ፣ከአውሮፓና ከሌሎቹም አገሮች ልምድ ጋር እያስተያዩ በአገራችንም ሕዝብ ሳይለያይ በሰላም የኖረበት አወቃቀር እንደነበረ ለአዲሱ ትውልድ ማስረዳት፣-
5 የክፍላተ ሃገር አስተዳደር አወቃቀር በክልል ስም ሕዝብ ለጉዳዩ ከሚኖርበት አካባቢ በብዙ መቶ ኪሎ ሜትር እርቀት ላይ ከሚገኘው ወደ ክልሉ አስተዳደር ጽ/ቤት የሚጓዝበት አሠራርና ግዴታ ተወግዶ በሚኖርበት አካባቢ ባለው አስተዳደር ጥያቄው መልስ የሚያገኝበትንና ችግሩ የሚፈታበትን ሁኔታ ይፈጥራል የሚለውን እምነቱን ለሕዝቡ ለማስረዳትና ተግባራዊ የሚሆንበትን መንገድ ለመሻት፣-
ይህን መመሪያ አንግቦ የተንቀሳቀሰውን የመጀመሪያውን ቡድን የሚቀላቀል በዛ ያሉ አባላት የሚገኙበት ቡድን በቅርቡ ለመጓዝ በዝግጅት ላይ ይገኛል።
የክፍላተ ሃገሩ ልዑካን የሚያደርጉት እንቅስቃሴ ከማንኛውም የፖለቲካ ድርጅት እንቅስቃሴ ጋር ያልተያያዘና ግንኙነትም እንደሌለው የክፍላተ ሃገሩ ህብረት ለማሳሰብ ይወዳል።
ኢትዮጵያ በአንድነትና በነጻነት ትኑር! የኢትዮጵያ ክፍላተ ሃገር ሕብረት ዋና ጸሐፊ አገሬ አዲስ
ነሐሴ 1ቀን 2010 ዓም(07-08-2018)