15 August 2018
ላለፈው አንድ ዓመት ያህል በአመራሮች መካከል በተፈጠረ ልዩነት ችግር ውስጥ ገብቶ የነበረው የኢትዮጵያዊያን ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢዴፓ)፣ ለአገሪቱ የመድብለ ፓርቲ ሥርዓት እስከ ዛሬ ሲያደርገው የነበረውን ገንቢ ሚና በመቀጠል፣ ከዚህ ቀደሙ አደራጃጀት በተሻለ ሁኔታ ተጠናክሮ በመውጣት የሚያደርገውን ሰላማዊና ዴሞክራሲያዊ የፖለቲካ እንቅስቃሴ አጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታወቀ፡፡
ኢዴፓ ይህን ያስታወቀው ማክሰኞ ነሐሴ 8 ቀን 2010 ዓ.ም. በራስ ሆቴል የመሰብሰቢያ አዳራሽ ‹‹ኢዴፓን ሕዝባዊ ድርጅት የማድረግ ትግላችን ተጠናክሮ ይቀጥላል›› በሚል መሪ ቃል፣ ለአገር ውስጥና ለውጭ የመገናኛ ብዙኃን በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ነው፡፡
በኢዴፓ ውስጥ ተፈጥሮ በነበረው የአመራሮች አለመግባባት ምክንያት የፓርቲው ሥራዎች ታጉለው እንደነበር ያስታወሱት የፓርቲው አመራሮች፣ በዚህም ሳቢያ ፓርቲው ጠቅላላ ጉባዔውን ማድረግ አልቻለም ነበር ብለዋል፡፡ ‹‹ሆኖም አሁን ጉዳዩ በፍርድ ቤት መቋጫ በማግኘቱ፣ እንዲሁም ምርጫ ቦርድ ዕውቅናውን ለእኛ የሰጠን በመሆኑ፣ ጠቅላላ ጉባዔውን በመጪዎቹ ሁለት ወይም ሦስት ወራት እናደርጋለን፤›› ሲሉ፣ የፓርቲው የጥናትና ምርመር ጉዳይ ኃላፊ አቶ ዋስይሁን ተስፋዬ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡
‹‹በፓርቲ ውስጥ ባለፈው አንድ ዓመት ራሳቸውን ከፓርቲው መተዳደርያ ደንብ ውጪና ከሕግ በላይ አድርገው በሚቆጥሩ ግለሰቦች አማካይነት በተፈጠረ ችግር፣ በአገሪቱ ፖለቲካ ውስጥ የሚጠበቅበትን ገንቢ ሚና በተገቢው ሁኔታ እንዳይጫወት እንቅፋት ሆኖ መቆየቱ ይታወቃል፤›› በማለት፣ በአመራሮች መካከል የተፈጠረው አለመግባባት የፓርቲውን እንቅስቃሴ ክፉኛ አዳክሞ እንደነበር አመራሮቹ አስታውቀዋል፡፡
በአመራሮች መካከል የተፈጠረውን ልዩነት በፓርቲው ሕገ ደንብና መተዳደርያ ደንብ መሠረት ለመፍታት ጥረት አድርገው እንደነበር የገለጹት የፓርቲው አመራሮች፣ ነገር ግን ጥረታቸው ፍሬ ሊያፈራ ባለመቻሉ ጉዳዩን ወደ ፍርድ ቤት ወስደው በማስወሰን ችግሩ መፍትሔ እንዲያገኝ ማድረጋቸውን አስረድተዋል፡፡
በዚህም መሠረት ተከሳሽ የፓርቲው ዋና ጸሐፊ የፓርቲውን ሕጋዊ ማኅተም ከፕሬዚዳንቱና ከሥራ አስፈጻሚው ዕውቅና ውጪ ያላግባብ መጠቀማቸውን በማረጋገጥ፣ የፓርቲውን ማኅተምና የገንዘብ ማንቀሳቀሻ ቼክ ለፓርቲው ሕጋዊ አመራርና ለፕሬዚዳንቱ እንዲያስረክቡ ሰኔ 03 ቀን 2010 ዓ.ም. መወሰኑን አስታውሰዋል፡፡
‹‹ከፍርድ ቤት ውሳኔ በኋላ የአገሪቱ ሕግ የማይገዛቸው፣ ‹ነገር ግን ለሕግ የበላይነት ስንታገል ቆይተናል› የሚሉ ግለሶቦች ተራ ድርጊት ውስጥ በመግባት ሕዝብን ለማደናገር እየሞከሩ ይገኛሉ፡፡ እነዚህ ግለሰቦች ሐምሌ 29 ቀን 2010 ዓ.ም. በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ እኛ ከሌለንበት ኢዴፓ ፈርሷል ሲሉ ተደምጠዋል፤› ሲሉ፣ በሌሎች የፓርቲው አመራር የነበሩ ግለሰቦች የተሰጠውን ጋዜጣዊ መግለጫ ኮንነዋል፡፡
ኢዴፓ ግለሰቦች እንደ ግል ድርጅታቸውና ሀብታቸው ቆጥረው ሲከስሩ ዘግተው የሚሄዱት በግለሰብ ሰብዕና ላይ የተንጠለጠለ ፓርቲ ሳይሆን፣ በሺዎች የሚቆጠሩ ወጣቶች ዋጋ የከፈሉበት፣ አሁንም እየከፈሉበት የሚገኝ በፅኑ መሠረት ላይ የቆመ የሐሳብ ፓርቲ ነው በማለትም፣ ፓርቲው አሁንም ሕጋዊ ሰውነቱን ጥብቆ በሰላማዊ ትግል ላይ እንደሚገኝ አመራሮቹ አስታውቀዋል፡፡
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በአዋጅ ከተሰጠው ሥልጣንና መብት ውጪ በፓርቲው የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ በመግባት ፍፁም ሕገወጥ የሆነ ድርጊት በመፈጸሙ፣ ከሐምሌ 29 ቀን 2010 ዓ.ም. ጀምሮ ከፍላጎታችን ውጪ በቦርዱ ሕገወጥ ድርጊት ህልውናችንን ያጣን መሆናችን እንገልጻለን በማለት፣ ፓርቲው መፍረሱን የፓርቲው ነባር አመራሮች ለሕዝብ ይፋ ማድረጋቸውን መዘገባችን ይታወሳል፡፡