ቢንያም ዘ ጨርቆስ
* እስከዛሬ ኢትዮጵያ ስትነድ፣ ስትፈርስ ዝም በማለቷ የምንገበገብባትን ትግራይን አየኋት። አየኋት ስለኢትዮጵያ ስታነባ፣ አየኋት ስለ ሀገሬ ደረቷን ስትደቃ። በጅግጅጋ ለታረዱ ካህናትና ምዕመናን ስታነባ አየኋት። በሻሸመኔ ተዘቅዝቆ ስለተሰቀለው፣ በደቡብ በቁማቸው በቤንዚን ተቃጥለው ስለሞቱት ሲያነቡ አየኋቸው።
የመቐለ የአቡነ ተክለሃይማኖት የዕረፍት በዓል አከባበር በተለየ መልኩ #በለቅሶና በምስጋና ነበር የተከበረው። ማኅሌቱና ውዳሴው እንዲሁም ወረቡ የደስታችን ምንጮች ነበሩ። ታላቁ ሊቅ ሊቀሊቃውንት ያሬድ ካሳ ስለ ተክልዬ ጽድቅና አገልጋይነት ከሕይወታችን ጋር እያስተሳሰሩ ሲያስተምሩ ሳለ ድንገት የጅግጅጋው የካህናት መጨፍጭፍ አንስተው ትምህርቱን አቁመው የእናታቸው ልጅ እንደሞተባቸው ዕንባ ተናነቃቸው! “ህ! ህ! ህ!” ብለውም አለቀሱ።
የቤተመቅደሱ መቃጠል፣ የካህናቱ መታረድ አንገብግቧቸው ከንፈራቸው ተንቀጠቀጠ። ያ ሁሉ ሕዝብም ዕንባውን መያዝ አልቻለም። በግፍ ስለሞቱት ኢትዮጵያውያን ሁሉ በአንድ ቃል እዬዬ ብሎ አለቀሰ! በዘር ቢለያይ ኢትዮጵያዊነት ላስተሳሰረው ወገኑ የሚያለቅስ ይህ ሕዝብ ታላቅ ነው።

ያኔ አባታችን ለቅሶውን በግድ ገትተው፣ ምኅላ ለመጀመር “እግዚኦ…” ብለው ሲጀምሩም ድጋሜ በለቅሶ አፋቸው ተያዘ። ሲቃቸው ሕዝቡ መሃል ገብቶ ምህላው ላይ ዕንባን ጨመረበት። የተለቀሰው ስለ አንድ የመቀሌ ልጅ ወይ ስለ አንድ ትግራዋይ አልነበረም። ብሔራቸው ለማናቀው የጅጅጋ ካህናት፣ በቋንቋ ለማይመስለን በግፍ ለተሰቀለው ወንድም፣ በዘር ለማይገናኘን በቤተ ክርስቲያን ለተጨፈጨው ኢትዮጵያዊው ወገናችን እንጂ። ሕዝቡ ታላቅ ነው ስልህ።