በጣም ብዙ ሰዎች ነዳጅ ለመሙላት ሦስት ቀናትን ወረፋ ላይ እንደሚያሳልፉ ለቢቢሲ ተናግረዋል። በተለይ ባለ ባጃጆች ክፉኛ ተማረዋል። በዚህም ሰርተው የቤትና የባጃጅ ኪራይ ለመክፈል እንደተቸገሩም ይናገራሉ።

ድንበሩ እንደተከፈተ በጣም ብዙ ሰዎች በበርሜልና በጀሪካን ነዳጅ ሞልተው በመኪና በመጫን ወደ ኤርትራ ሲያጓጉዙ እንደነበር አንዳንዶች ያስታውሳሉ። ይህ ደግሞ በነበረው እጥረት ተጨማሪ ጫና መፍጠሩን ያመለክታሉ።

ከምጣኔ ኃብት አንፃር እንዴት ይታያል?

ቢቢሲ ያነጋገራቸው የምጣኔ ኃብት ምሁር ዶ/ር ተስፋማርያም መሓሪ “አሁን ላይ እየታየ ያለው ግኑኝነት ጊዜያዊ ነው፤ መደበኛም አይደለም። ቢሆንም የንግድ ግንኙነቱ ሕጋዊ አሰራር ካልተከተለ አለመስማማትን ይፈጥራል” ሲሉ ያላቸውን ስጋት ይናገራሉ።

ዶ/ር ተስፋማርያም የቀደመው ጦርነት መነሻን አሁኑ ካለው ሁኔታ ጋር ያመሳስሉታል። “በወቅቱ ሁለቱ ሃገራት አዲስ የገንዘብ ኖቶችን ማሳተማቸው፣ የገንዘብ ምንዛሬ መጠንና የሚገበያዩበት ገንዘብ ለግጭቱ መንስኤ እንደነበረ መታወቅ አለበት” ሲሉ እምነታቸውን ይገልፃሉ።

ስለዚህ ከዚህ በኋላ ተመሳሳይ አለመግባባትና ግጭት እንዳይፈጠር ከወዲሁ ሕጋዊና መደበኛ አሰራር ላይ አጽንኦት ተሰጥቶ መስራት ይኖርበታል ሲሉ ይመክራሉ ዶ/ር ተስፋማሪያም።