“አማራ የሰውነት ውኃ ልክ ነው።” የሚለው ዘግናኝ አባባል ከሰው አይደለም ከአምላክም ያቆራርጣል። የኢትዮጵያዊነት መለኪያ አይደለም የተባለው፥ ልብ በሉ የሰውነት ነው። ይታያችሁ ለማ መገርሳ ከእኔ ተወዳድሮ አዎ ብቁ ሰው ነው ሲባል፥ ወይም ይሄ ይጎለዋልና ተስተካክሎ ይምጣ ሲባል። እንዲህ የሚያስቡና ለዚህ ተግባራዊነት የሚታገሉ መሪዎች ኢትዮጵያን ቶሎ አፈራርሶ ለመጨረስ ይረዱናል? ወይስ ኢትዮጵያን ለመገንባት? በዐማራነቴ እንዳፍር እንጂ እንድኮራ የሚያደርጉኝ አባባሎች አይደሉም። እስኪደክመኝ ባስብ ባስብ ከዚያም ከዚህ መፈናቀልና መሳደድ ለበዛበት አማርኛ ተናጋሪ ወገን፥ አባባሎቹ እንዴት ሊጠቅመው እንደሚችል አልገባህ አለኝ። ዓለምነው መኮንን ያቆሰለውን ልብ ለማሻር ከሆነም፥ ሁለት ስህተቶች አንድ ትክክል አይወጣቸውም። እነዚህ ሁለቱም (በ ሀ ና ለ የተጠቀሱት) ከላይ እየነደዱበት ዳቦውን እያሳረሩት ነው።
ህወሀት አድብቶ ጊዜ እየጠበቀ እያጠቃ ነው!የአብዮታዊ ዴሞክራሲ ርዕዮት የረከሰበት ህወሀት፥ ፖለቲካው ቢሰናከልበትም በዘረፋ ያካበተው ጥሪት በቀላሉ የሚሙዋጠጥ ባለመሆኑ አገር ለመበጥበጥ ያለው አቅም ላልተወሰነ ጊዜ የሚያዘልቀው ነው። እዛም እዚህ ብሩን እያፈሰሰ አገር እንዳይረጋጋና ለውጡ እንዳይሳካ የማይፈነቅለው ድንጋይ የለም። ከአፋር፥ ከቤኒ ሻንጉልና ከጋምቤላ ክልሎች የህወሀት ጥፍሮች ገና አልተነቀሉም። የህወሀት ማንነትና ምንነት መገለጫ የሆነውን፥ በወንጀል የሚፈለገውን ጨካኝ በማን አለብኝነት በኃላፊነት ሾሞዋል። ህወሀት ዛሬም በዳቦው ሥር እሣቱን እያንበለበለው ነው።
ለሀያ ሠባት ዐመታት የተሰበከው ጥላቻ ያደነደው መንፈስ በተለያዩ የመንግሥት ሥልጣን ላይ እስካሁን ይገኛል። የዘረፋው መንገዶች እንደሚዘጋ ሲገነዘቡ፥ ትናንት የሰሩት ወንጀል ለውጡ ከተሳካ ነገ ሊያስጠይቃቸው እንደሚችል እያሰቡ የለውጡን መሰናክል ሆነዋል። አገር እንዳይረጋጋ፥ ለውጡ እንዳይሳካ፥ የመሪው ስብዕና እንዲወርድ የቻሉትን ሁሉ ያደርጋሉ። እነዚህም ከላይ የሚነደውን እሣት ይቆሰቁሱታል።
ሚዲያዎች የሚሰጡት ትንታኔ አገሪቱና በሥልጣን ላይ ያለውን መንግሥት ያሉበትን መከራ ያገናዘበ ሳይሆን የራሳቸውን የተንታኝነት ክህሎት ለማሳየት የሚጥሩ ይመስላል። ከሩቅ ሆነው እየገመቱ ይኸው ያልነው ሆነ ለማለት ይታትራሉ። የሴረኞቹን ጎራ ሰልሎ በማጋለጥ ለውጡን ለመርዳት ጥረት በማድረግ ፈንታ በማወቅም ሆነ ባለማወቅ ከላይና ከታች እየነደደበት ያለውን ዳቦ ከጎንም እየለበለቡት ነው። የአዲስ አበባ ወጣት በማይረባ ብሽሽቅ ተጠምዶ እንዲደራጅና የመንግሥቱን ራሥምታት ከፍ እንዲያደርገው እየቀሰቀሱ ነው። መብትን ሁሉ በአንድ ጊዜ መጠየቅ እስካሁን የተገኙትን መብቶችም ማስወሰድን ሊያመጣ እንደሚችል ማገናዘብ ተስኖዋቸዋል። የነበርንበትን የህወሀት የበላይነትን የገሀነም ዘመን ዘንግተውት፥ በአንድ ጊዜ የአሜሪካን ዴሞክራሲ ደረጃ እንድንደርስ ዓቢይን ሱሪ ባንገት እያሉት ነው።
ብዙ የፖለቲካ ፓርቲዎችና አክቲቪስቶች የሽግግር መንግሥት እንዲመሠረት ሲጠይቁ ነበር። ዶር ዓቢይ ለውጡን ማንም ከጠበቀው በላይ በማፋጠናቸው የሽግግር መንግሥትን የሚጠይቅ ድምፅ አሁን የለም። ማንም በምንም ቢለካው ዶር ዓቢይ ያበጁት ከብዙዎች ግምት በላይ ነው። ጥፋት አልተሰራም ለማለት አይደለም። የዶር ዓቢይ የለውጥ ሂደት ዛሬ ቢጨናገፍ የአገሪቱ ህልውናም የሚያከትምበት ቀን ነው የሚፈጠረው። OMN ላይቸግረው ይችላል ኢሣት ግን የለፋበት ሁሉ ገደል ገብቶ አመድ አፋሽ ከመሆኑም በላይ አዲስ ስም ማውጣት ያስፈልገዋል። ቢያንስ ‘ኢ’ን ከስሙ ውስጥ ለመፋቅ ይገደዳል። ይህ አይሆንም አንበል። “ኤርትራ አንገት ነች።” ሲል የነበረው የደርግ መንግሥት አንገቱን አስቆርጦ በኖዋል። አሁንም ሊሆን ይችላልን ይዘን፥ ያ እንዳይሆን ጠንክረን ነገሮች ወደፊት ይሻሻላሉ በሚል ተሥፋ ከለውጡ ኃይሎች ጎን እንቁም። በነገራችን ላይ በአሜሪካ ካሉ ሜድያዎች ወገንተኛነትን የሚያሳዩ አሉ። በሥልጣን ላይ ያለውን መንግሥት ሁልጊዜም የሚቃወሙ እንዳሉ ሁሉ ሁልጊዜም የሚደግፉም አሉ። አሜሪካ ችግር ውስጥ በገባች ጊዜ ውነትን (objectivism) ገሽሽ አድርገው ተባብረው ለአገሪቱ ጥቅም በአርበርኝነት አንድ ሆነው ይቆማሉ። ኢትዮጵያም የሜድያውን አርበኝነት የምትፈልግበት ነው ወቅቱ። ዓቢይ አፍ አውጥቶ “እርዱኝ!” ብሎዋል።
ዶር ዓቢይ ከሚነቀፉበት ዋና ዋና ምክንያቶች አንዱ የሕግ የበላይነትን ለማስፈን አቅመቢስ በመሆናቸው የሚሞት፥ የሚፈናቀልና ጥቃት የሚደርስበት ዜጋ ቁጥር ከጊዜ ወደጊዜ እየጨመረ መሄዱ ነው። ይሄንን እሳቸውም የሚያውቁትና እንቅልፍ የሚያጡበት ጉዳይ እንደሆነ መገመት ይቻላል። ለሀያ ሰባት ዓመታት በቤተ ዕምነቶች ላይ በሽምግልናና በባህል ላይ የተደረገው ጥቃት አገሪትዋን ኦና አድርጎዋታል። ትኅትና ይሉኝታና መደጋገፍ ከእያንዳንዱ ዜጋ ዐዕምሮ እንዲረግፉ ተደርገዋል። ተቁዋማት የሕዝብን አደራ ተሸክመው በተጠያቂነት መንፈስ ሥራቸውን ከሚያከናውኑ ይልቅ ኪሳቸውን የሚያደልቡበትን መንገድ ማጠናከር ተገቢ መሆኑን ተምረዋል። በጥቅሉ ማኅበራዊ ካፒታልም ሆነ የሕግ አስከባሪ ተቁዋማት አቅም ዜሮ ነው። ይህን ችግር መፍታት ጊዜ ይወስዳል። አማራጭ የለንም – መታገስና በምንችለው መንገድ ሁሉ መደገፍ ብቻ።
ሌላው ነቀፋ ግልፅ አለመሆናቸው ነው። አንዳንዴም ከመለስ ዜናዊ ጋር የሚወዳደሩ ሀሰት ተናጋሪ አድርገው የሚስሉዋቸውም አሉ። አገሪቱ ያለችበት አስቸጋሪ ሁኔታ የአስቸኩዋይ ጊዜ አዋጅ ግድ ሊል ምንም ባልቀረው ሁኔታ ውስጥ ነው። በዚህ ጊዜ ውስጥ ቀደም ብለው በገቡት ቃል መሠረት መንግሥታዊ መረጃን ከሥር ከሥሩ ቢለቁ ኢትዮጵያ ውስጥ ተንጋግተው የገቡ እርስ በእርስ የማይታረቅ ቅራኔ ያላቸው የፖለቲካ ድርጅቶች እንደመሆናቸው መጠን ድርጅቶቹ የሚሰጡት ምላሽ አገሪቱን ገደል እንዳይከታት ያስፈራል። ተቁዋማቱ ተገንብተው እስኪያልቁ ትዕግስትን ቢሰጠን።
በዶር ዓቢይ ላይ ከሚነሳባቸው ወቀሳዎች ሌላው፥ ሁሉ ቦታ ሁሉን ነገር አዋቂ ሆነው እየታዩ የራሣቸውን ስብዕና እየገነቡ ነው ይህ ደግሞ ለአንባገነንነት ይጋብዛቸዋል የሚል ነው። ስለዚህም አንዳንድ ጉድፎችን እያወጡ ለማሳየት በመጣር ሊገነቡ ነው ብለው ያመኑትን ስብዕና ለመናድ ጥረት ሲደረግ ይታያል። በዚህ ክፉ ቀን የአገሪቱ ዕጣ ፈንታ በአንድና በሁለት ግለሰቦች እጅ ባለበት ሁኔታና ከኢትዮጵያ መፍረስ እናተርፋለን ብለው የሚጠብቁ ወገኖች በሞሉበት ወቅት፥ የዶር ዓቢይ ስብዕና መግነን ከመኮስመኑ በተሻለ ኢትዮጵያን ይጠቅማል። ሥልጣን ላይ በወጡበት ሰሞን በደቡብ በተደረገ ግጭት “በሚቀጥለው ሣምንት መጥቼ እስክንነጋገር ድረስ ግጭቱን አቁሙ!” ብለው ከርቀት የላኩት መልዕክት ተቀባይነት አግኝቶ ግጭቱ ቆሞ እንደነበር የቅርብ ጊዜ ትዝታችን ነው። አሁንም ያልረጋች አገር ነችና ልቀው መታየታቸው ከጉዳቱ ጥቅሙ ያይላል – እምንመካባቸው ተቁዋማት እስኪገነቡ ድረስ።
ዶር ዐቢይ ለረዥም ጊዜ፥ ከልጅነት ጊዜያቸው ጀምረው የሠሩበት ነውና ከከበቡዋቸው ባለሥልጣኖች አንፃር በዕውቀት ገዝፈው የወጡ ናቸው። የሣቸው መግዘፍ ብቻ አይደለም ብዙዎቹ ካድሬዎች የቀድሞው የኮሙኒኬሽን ሚር ደኤታ ጥሩ አድርገው እንዳስረዱን፥ በካድሬ ትምህርት ቤት (ዶምቦስኮ) ገብተው ስፍትዌራቸው ዲሊት ተደርጎ አብዮታዊ ዴሞክራሢ የተጫነበት በመሆኑ ለዶር ዓቢይ ተማሪ እንኩዋን የመሆን ብቃት ያንሳቸዋል። ሥልጠና በሚሰጡበትም ሆነ ትንታኔ ሲሰጡ ብስለት እንዳላቸው ብዙ ምሁራን የመሰከሩላቸው ነው። በተወካዮች ምቤት መናገሪያውን በያዙ ጊዜ ሁሉ የፓርላማ አባላት በማሸለብ ፈንታ፥ ጆሮዋቸውን አቁመው፥ ዐይናቸውን በልጥጠው፥ አፋቸውን ከፍተው ሲያዳምጡዋቸው ዶሩ አንድም ስጦታ ወይም የረዥም ጊዜ ጥረት ስኬት ባለቤት እንደሆኑ መስካሪ ነውና ስብዕናቸውን አፍ አውጥተው መናገር አይጠበቅባቸውም። ለፍተው ያገኙትን ብስለትና ዕውቀት ለምን ልንነሳቸው ይከጅለናል?
ኢሳትና OMN የፋይናንስ ችግር ይገጥማቸዋልና ባለሀብቶች ማስታወቂያችሁን በነሱ ላይ አውጡ ብለው ላደረጉት የፈንድ ሬይዚንግ ውለታ፥ “አለምነህ ዋሴን በስም የጠቀሱት ለኖቤል ሽልማት ስላጫቸው ነው።” የሚል መልስ ማግኘታቸው ያጎረሰን እጅ የመንከስ ያህል ነው። ያልተረጋገጠ ግምት ከመሆኑም በላይ ተራ ብሽሽቅ ነው። ያስተዛዝባል። ወታደር በመሆን ፋንታ ሲቪል ቢሆኑ ኖሮ የወታደሮቹ ጥያቄ አጉዋጉል መጨረሻ ይኖረው እንደነበር መግለፃቸው ራስን ማግዘፍ ሆኖ አልታየኝም። በተለይ ወታደሩ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ገብቶ ፖለቲካውን ካጨቀየው በሁዋላ ወታደርነት የሚኮራበት ሙያ አልነበረም። ከቀደሙት መሪዎች የሚሻሉበት የትምህርት ደረጃ አላቸው – ፒኤችዲ። ራሳቸውን ለማግዘፍ ከመንግሥቱ ኃ/ማ ጋር መወዳደር አይጠበቅባቸውም።
ዶር ዓቢይና ቡድናቸው ካለሕዝቡ ማናም ከጎናቸው የለም። ይህንንም አፍ አውጥተው ተናግረዋል። ይህ ብቻ አይደለም ለኢትዮጵያም በዚህ ወቅት ከዶር ዓቢይና ቡድናቸው በላይ ምንም ምድራዊ ጠባቂ የላትም። በተለይ የአዲስ አበባ ሕዝብ አሁንም ከጎናቸው እንዳይለይ ሜድያዎች በርትተው ሊሰሩ ይገባል። አዲስ አበባችንን እናስመልስ ብለን ኢትዮጵያችንን እንዳናስወስድ። ሰንበትን እየገደፉ በስራ የሚጠመዱትና ከሰማያዊው ፀጋ ቆንጥረው የሚያፈሱት ለኢትዮጵያ ሲሉ ነውና ምሣሌነታቸውን ባንከተል እንኩዋ በትችት ከመጥበስ እንታቀብ። ሜድያ ዐይን ጆሮና አንደበት ብቻ ሳይሆኑ አመዛዛኝ ዐዕምሮም ሊሆኑ የግድ ነው – ድልድዩን እስክንሻገር። ኢትዮጵያን እስከጠቀመ ድረስ አይቶ እንዳላየ፥ ሰምቶም እንዳልሰማ ማለፍ፥ አይቶና ሰምቶም ዝም ማለት አርበኝነት ነው። ከኢትዮጵያ የሚበልጥ እውነት የለም።
ይልቅ:
- ፕሮጀክት ተነድፎ የትግራይ ወጣት በህወሀት ላይ እንዲነሳበት ቢሠራ።
- ኢትዮጵያ ከርሰ ምድርዋ ሙሉውን አዱኛ መሆኑንና ወጣቱ ተስፋው የትየለሌ መሆኑን ቢስበክ
- በቪድዮ የተደገፈ አገርን የማስተዋወቅና የማስጎብኘት ፕሮግራም ቢተላለፍ
- የሶስት ሺህ ዘመናት የአንድነት ታሪካችንን መለፈፍ
- የብሔር መከፋፈል አደገኛነትን በምሣሌ በኪነትም ተደግፎ ማራገብ ላይ ብንጠመድ
- የሞራል ትምህርቶች በወጣቱ እንዲሰርፁ ቢደረግ ወዘተ
ሚዲያው ችግሩን ሳያስተውል ቀድሞ አድጎዋል!ለውጥ ያስፈራል ዋጋም ያስከፍላል!