ያሬድ ሃይለማሪያም

ያሬድ ሃይለማሪያም

የራያ፣ የወልቃይት፣ የቅማንት እና በሌሎችም አካባቢዎች የሚነሱ የማንነት ጥያቄ በውስጣቸው ብዙ አውዛጋቢ የሆኑ የግዛት፣ የታሪክ፣ የባህል እና የማንነት መገለጫ ጥያቄዎችን የያዙ ጉዳዮች ስለሆኑ አፋጣኝ ምላሽ ካላገኙ አላስፈላጊ ወደሆነ ደም አፋሳሽ ግጭት ሊያመሩ እንደሚችሉ ምልክቶች ከወዲሁ እየታዩ ነው።

የተነሱትን የማንነት ጥያቄዎች ተታከው እርስ በርስ እየተገፋፉ እና እየተናቆሩ ያሉት ህውሃት እና አዴፓ ውጥረቱ እንዲባባስ የበኩላቸውን እያደረጉ ነው። የተነሱት ጥያቄዎች ከዘር ማንነት መገለጫ ጋር በተያያዘ ‘እገሌ ተብዮ ልታወቅ’ አይነት ጥያቄ ብቻ ሳይሆን የሁለቱን ክልሎች ግዛትም የሚመለከት በመሆኑ ሁለቱ ድርጅቶች የውጥረቱ ዋና ተዋናዮች ናቸው። ጥያቄዎችም የፖለቲካ እና የሕግ ምላሽ ይፈልጋሉ።

የፌደራል መንግስቱ እነኚህን ጥያቄዎች በማያዳግም መልኩ ፖለቲካዊ እና ሕግን መሰረት ያደረገ ምላሽ እስኪሰጥ ድረስ ግን ከዚህ የሚከተሉትን እርምጃዎች በመውሰድ ውጥረቱ ወደ ደም አፋሳሽ ግጭት እንዳያመራ ማድረግ ይችላል፤

– በመጀመሪያ ጥያቄዎቹ ምላሽ እስኪያገኙ ድረስ እነዚህ አካባቢዎች ወይም አወዛጋቢና የግጭት ቀጠና የሆኑት ሥፍራዎች ላይ ያሉ የየትኛውም ክልል ታጣቂዎች ከስፍራው እንዲወጡ በማድረግ በምትካቸው የፌደራል የጸጥታ ኃይሎችን መተካት እና ሰላም የማስከበሩን እና ጸጥታ የማስፈኑን ሥራ እነሱ እንዲያከናውኑ ማድረግ፣

– በእነኚህ አካባቢዎች ያለውንም የሲቪል አስተዳደር ለተወሰነ ጊዜ በፌደራል መንግስቱ ቁጥጥር ስር እንዲውል ማድረግ፣

– ሁለቱ ክልሎች በመካከላቸው ያለውን መናቆር እንዲያቆሙ እና ጥያቄዎቹ እልባት እስኪያገኙ ድረስ በእነዚህ ስፍራዎች የሚያደርጉትን ጣልቃ ገብነት እንዲያቆሙ ማድረግ፣

– የእያንዳንዱን አካባቢ የማንነት ጥያቄ መርምሮ እና ማስረጃዎችን አሰባስቦ ለፌዴሬሽን ምክር ቤት ሪፖርት የሚያቀርብ ገለልተኛ አካል ቢቋቋም፣

– በሕገ መንግስቱ መሰረት እንዲህ አይነት የማንነት ጥያቄን ተቀብሎ የሚያስተናግደው አካል የፌዴሬሽን ምክር ቤት ቢሆንም ተቋሙ እየተመራ ያለው በተነሱት ጥያቄዎች በተለይም በራያ እና በወልቃይት ጉዳይ ቀጥተኛ ተሳታፊና ባለጉዳይ የሆነው የትግራይ ክልል አመራር አባል እና የህውሃት ባለስልጣን በሆኑት የምክር ቤቱ አፈ-ጉባዔ ስለሆን ይህም በሂደቱ ላይ የራሱ የሆነ ተጽዕኖ ይኖረዋል። በመሆኑም በእነዚህ ጉዳዮች ላይ እኚህ ግለሰብ ገለልተኛ አቋም ይዘው ምክር ቤቱን ሊመሩ አይችሉም። በቅርቡ የሰጡትም አወዛጋቢ መግለጫ ጥሩ ማሳያ ነው። እንዲህ አይነት ችግር ሲገጥም ምክር ቤቱ ገለልተኝነቱን በጠበቀ መልኩ ውሳኔ ለመስጠት የሚያስችል አሰራር ሊያበጅ ይገባዋል።

– እነዚህን የማንነት ጥያቄዎች ተከትሎ በአካባቢዎቹ በሰው ሕይወት እና ንብረት ላይ ጉዳት እየደረሰ ነው። በመተማ በጦር መሳሪያ የተደገፈ ግጭት ውስጥ ተገብቷል። በራያ ሰዎች ሞተዋል፣ ታስረዋል፣ ተፈናቅለዋል፤ በወልቃይትም ተመሳሳይ ጉዳቶች ደርሰዋል። በቅርቡ በእነዚህ ስፍራዎች ስላለው የጸጥታ ሁኔታ ከፌደራል መንግስቱ መግለጫ ሊሰጥ ሲገባው ጉዳዩ በዝምታ ተይዟል። መንግስት እስካውን ስለደረሰው ጉዳት፣ ችግሩን ለመቅረፍ እየተወሰደ ስላለው የመፍትሔ እርምጃ እና ጥያቄዎቹ ስለሚመለሱበት መንገድ ግልጽ መግለጫ ለሕዝብ መስጠት አለበት።

የሰላም ሚኒስትሯም በዚህ ዙሪያ ምን እያከናወኑ እንደሆነ ቢገልጹልን መልካም ነው፡፤

በቸር እንሰንብት!