1) የዶ/ር ደብረፂዮን መግለጫ ጭብጥ
ዶ/ር ደብረፂዮን ትላንት የሰጠውን መግለጫ ቀድሞ ያወጣው የትግራይ ብዙሃን መገናኛ ኤጀንሲ ድረገፅ ነበር። በመቀጠል የሸገር ራዲዮ እና ጌቱ ተመስገን ድረገፆች አውጥተውታል። ትንሽ ቆይቶ ደግሞ እንደ ኢዘኣ፣ የአማራ ብዙሃን መገናኛ ኤጀንሲ፣ ፋና እና የመሳሰሉት ይዘው ወጥተዋል። ነገር ግን በእነዚህ ሚዲያዎች የወጣው የመግለጫ ይዘት ከመጀመሪያው ብዙም የተለየ አይደለም። በኋላ ላይ በህዝብ ግንኙነት ሰዎች ተሸሽሎና ተስተካክሎ የቀረበው መግለጫ ቀደም ብሎ ፊት ለፊት የተገለፀውን የህወሓት አቋም በቃላት ከመሸፋፈን በዘለለ ጭብጡ አልተለወጠም።
ዶ/ር ደብረጺዮን ገ/ሚካኤል የትግራይ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳደር
በመግለጫው መሰረት “የፌደራል መንግስት ከፍተኛ ሌብነትና የሰብዓዊ መብት ጥሰት ፈፅመዋል” ብሎ በጠረጠራቸው አካላት ላይ “የጀመረውን” እርምጃ በሁሉም ተቋማት ዘንድ አጠናክሮ ሊቀጥልበት እንደሚገባ ያትታል። ይህን ከጠቀሱ በኋላ ግን ዶ/ር ደብረፂዮን አፅንዖት ሰጥተው ከተናገሯቸው ውስጥ የሚከተሉትን ሶስት ነጥቦች ወስደን እንመልከት፦
1ኛ) “የህግ ልዕልና የማስከበር ስራው በተወሰኑ ተቋማት ላይ መታጠር የለበትም”፣
2ኛ) “በቁጥጥር ስር የማዋሉ ስራ ወደ አንድ ወገን ያዘነበለ እንዳይሆን በጥንቃቄ ሊሰራ ይገባል” እና
3ኛ) “የህግ ልዕልናን የሚረጋገጥበት እንጂ የፖለቲካ መጠቀሚያና ቁማር ሊሆን አይገባም”
በመጀመሪያ ደረጃ “የህግ ልዕልና የማስከበር ስራው በተወሰኑ ተቋማት ላይ መታጠር የለበትም” የሚለው አሁን ላይ እየተሰራ ያለው የህግ ማስከበር ስራ የህወሓት አባላትና ደጋፊዎች በሚበዙባቸው የተወሰኑ ተቋማት ላይ የታጠረ እንደሆነ ይጠቁማል።
ሁለተኛ ላይ የተጠቀሰው “በቁጥጥር ስር የማዋሉ ስራ ወደ አንድ ወገን ያዘነበለ እንዳይሆን በጥንቃቄ ሊሰራ ይገባል” የሚለው ደግሞ የህግ ማስከበር ስራው ከሌሎች ብሔር ተወላጆች ይልቅ የህወሓት አባላትና ደጋፎዎች በሆኑ የትግራይ ተወላጆች ላይ ያነጣጠረ ነው የሚል አንድምታ አለው።
ሶስተኛ “የህግ ልዕልናን የሚረጋገጥበት እንጂ የፖለቲካ መጠቀሚያና ቁማር ሊሆን አይገባም” በማለት ሦስተኛ ላይ የተጠቀሰው ደግሞ ህግ የማስከበሩ ስራ ለፖለቲካ መጠቀሚያና የፖለቲካ ቁማር መጫዎቻ እየሆነ ነው የሚል ስጋት እንዳላቸው በግልፅ ይጠቁማል።
በዚህ መሰረት የመግለጫው ፍሬ-ሃሳብ “አሁን እየተካሄደ ያለው የህግ ማስከበር ስራ የህወሓት አመራሮች፣ አባላትና ደጋፊዎችን ኢላማ ያደረገ የፖለቲካ ቁማር ነው” ከሚል እሳቤ የመነጨ እንደሆነ መገንዘብ ይቻላል። ነገር ግን “የህግ ልዕልና የማስከበር ስራው የህወሓት አባላትና ደጋፊዎች በሚበዙባቸው የተወሰኑ ተቋማት ላይ የተወሰነ ወይም የታጠረ ነው” ማለት ይቻላል?
2) የአንድ ወገን የበላይነት እና ተጠያቂነት
በህግ ቁጥጥር ስር የዋሉትና በፖሊስ ክትትል እየተደረገባቸው ያሉት በዋናነት ከፍተኛ የሆነ የሌብነትና ዘረፋ ተግባር የተፈፀመባቸው እና በዜጎች ላይ የሰብዓዊ መብት ጥሰት የፈፀሙ ሰዎች ናቸው። ከእነዚህ ውስጥ ደግሞ ሜቴክ እና ብሔራዊ የመረጃና ደህንነት መስሪያ ቤቶች በግንባር-ቀደምትነት ይጠቀሳሉ። እንደ ዶ/ር ደብረፂዮን አገላለፅ የህግ ልዕልና የማስከበር ስራው በእነዚህ ተቋማት ላይ ብቻ መታጠር የለበትም። ባለፉት አመታት በሀገር ሃብት ላይ ከፍተኛ የሆነ ዘረፋና ሌብነት፣ እንዲሁም በዜጎች ላይ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ሲፈፀምባቸው የነበሩ ተቋማት አመራሮች እና ሰራተኞች ላይ ተመሳሳይ እርምጃ መወሰድ አለበት።

በዚህ ረገድ ከሜቴክ ቀጥሎ ከፍተኛ የሆነ ዘረፋና ሌብነት ከሚፈፀምባቻ መስሪያ ቤቶች ውስጥ የኢትዮጵያ ስኳር ኮርፖሬሽን በግንባር ቀደምትነት ይጠቀሳል። የኢህአዴግ መንግስት ወደ ስልጣን ከመጣ ግዜ ጀምሮ በሀገሪቱ ከሚገኙ የስኳር ፋብሪካዎች “የስኳር ልማት ፈንድ” በሚል የተሰበሰበ 65 ቢሊዮን ብር የት እንደ ገባ አንኳን አልታወቀም። በዚህ ላይ ደግሞ በአባይ ፀሓዬ የሚመራው የኢትዮጵያ ስኳር ኮርፖሬሽን አስር የስኳር ፋብሪካዎችን እገነባለሁ በሚል ሰበብ 77 ቢሊዮን ብር ተበድሮ አጥፍቶታል። ከዚህ በተጨማሪ አስር ሺህ ኩንታል አሸዋ ስኳር ተብሎ ከውጪ ሀገር ተገዝቶ ጅቡቲ ወደብ ላይ መራገፉ ሳያንስን ባለፈው አመት ሀገር ውስጥ የተመረተ አስር ሺህ ኩንታል ስኳር በኬኒያ በኩል ወደ ውጪ ሀገር ሲላክ በቁጥጥር ስር መዋሉ አይዘነጋም።
አሸዋ እየገዛ ስኳር ሲሸጥ የነበረ፣ ከነባር የስኳር ፋብሪካዎች 65 ቢሊዮን ብር እየሰበሰበ አዳዲስ ፋብሪካዎች ለመገንባት በሚል 77 ቢሊዮን ብር ከባንክ የተበደረ፣ ነገር ግን አንድም ፋብሪካ በአግባቡ ገንብቶ ሳይጨርስ ብሩን ያባከነ አመራር ለፍርድ መቅረብ አለበት። መቼም በዚህ ጉዳይ ላይ መጠየቅ ያለበት የመጀመሪያ ሰው አቶ አባይ ፀሓዬ መሆን አያጠያይቅም። ከስኳር ኮርፖሬሽን በመቀጠል ከፍተኛ ዘረፋና ሌብነት ከሚፈፀምባቸው ተቋማት ውስጥ ኢትዮ-ቴሌኮም እና የኢትዮጵያ መብራት ኃይል በቀዳሚነት ይጠቀሳሉ። በእነዚህ መስሪያ ቤቶች የህግ ማስከበርና ተጠያቂነት ማስፈን ከተጀመረ የእስር ማዘዣ ከሚወጣባቸው የቀድሞ ከፍተኛ አመራሮች ውስጥ የመጀመሪያው ዶ/ር ደብረፂዮን ገ/ሚካኤል ነው።
በአጠቃላይ የህግ ማስከበር ስራው ሌሎች ተጨማሪ ተቋማትን እያካተተ በሄደ ቁጥር የሚታሰሩ የህወሓት አባላትና ደጋፊዎች ቁጥር ይበልጥ እየጨመረ ይሄዳል። በመሆኑም በቁጥጥር ስር የማዋሉ ስራ ወደ አንድ ወገን ያዘነበለ መሆኑ አይቀርም። ባለፉት አመታት ቁልፍ በሆኑ የመንግስት ተቋማት ውስጥ ለምሳሌ በታክስና ጉምሩክ ባለስልጣን፣ የውጪ ሚኒስቴር መስሪያ ቤት፣ በውጪ የሚገኙ ቆንፅላ ፅ/ቤቶች፣ ቁልፍ በሆኑ የንግድ ሴክተሮች፣ በኮንስትራክሽን እና ግንባታ ዘርፍ፣ በእርሻ፣ የማዕድን ዘርፍ፣…ወዘተ በትግራይ ተወላጆች ቁጥጥር ስር መሆኑን ስንናገር ሰሚ አልነበረም። የአንድ ብሔር ተወላጆች የሀገሪቱን የገቢ ምንጭ፣ የንግድ፣ ኮንስትራክሽን እና ሌሎች እንዱስትሪዎችን በበላይነት የተቆጣጠሩት ከህወሓት በሚያገኙት አድሏዊ ድጋፍ እና ማበረታቻ ነው።
በዚህ ረገድ በጋምቤላ የእርሻ ኢንቨስትመንት ከተሰማሩት ውስጥ ከ98% የሚሆኑት የትግራይ ተወላጆች ከመሆናቸው በተጨማሪ ያለ ማስያዣ ቁጥሩ በውል ያልታወቀ ቢሊዮን ብር ብድር ከኢትዮጵያ ልማት ባንክ መውሰዳቸው እንደ ማሳያ ሊጠቀስ ይችላል። በዚህ ምክንያት የልማት ባንክ ከሰጠው ብድር 40% የሚሆነው የማይመለስ ብድር “Bad debt” ሲሆን በተመሳሳይ መንገድ በተሰጠ ብድር ምክንያት የኮንስትራክሽን ባንክ ለኪሳራ ተዳርጎ ከነዕዳው ለንግድ ባንክ መሸጡ ይታወሳል። በሀገሪቱ ላይ ከፍተኛ የሆነ ዘረፍና ሌብነት በተፈፀመባቸው ሌሎች ተቋማት ላይ የህግ ልዕልና ማስከበር ስራ ከተሰራ የእስር ማዘዣ ከሚቆረጥባቸው ሰዎች አብዛኞቹ የህወሓት አባላትና ደጋፊ የሆኑ ባለሃብቶችና የመንግስት ኃላፊዎች ናቸው።
በሀገሪቱ የመከላከያ፣ ፖሊስና ደህንነት ተቋማት ውስጥ ሲሰሩ የነበሩና በዜጎች ላይ የሰብዓዊ መብት ጥሰት የፈጸሙ ተጨማሪ ሰዎች በህግ ቁጥጥር ስር መዋል አለባቸው ከተባለም በብዛት የሚታሰሩት የትግራይ ተወላጅ የሆኑ ሰዎች ናቸው። “ለምን?” የሚለው ጥያቄ መልስ የሚያገኘው ዛሬ ላይ ሳይሆን ትላንት ነው። ከሞላ ጎደል ሁሉም የብሔራዊ መረጃና ደህንነት መስሪያ ቤት እና የመረጃ መረብ ደህንነት ኤጀንሲ ኃላፊዎች እና አብዛኞቹ ሰራተኞች፣ ከ90% በላይ የሚሆኑት የመከላከያ አዛዦች፣ እንዲሁም በፌደራል ፖሊስ፣ የወንጀል ምርመራ እና ማረሚያ ቤቶች ውስጥ ያሉ ቁልፍ የሆኑ የኃላፊነት ቦታዎች በህወሓት አባላትና ደጋፊዎች ቁጥጥር ስር እንዲሆን መደረጉን ስንገልፅ በትግራይ ህዝብ ላይ ጥላቻ እንደሆነ ተደርጎ ሲነገር ነበር። ትላንት ሀገሪቱ የፀጥታና ደህንነት መዋቅር ውስጥ የአንድ ብሔር ተወላጆችን በኃላፊነት ማስቀመጥ ዛሬ ላይ የህግ ተጠያቂነትን ይዞ ይመጣል። በመሆኑም በእነዚህ ተቋማት ውስጥ የህግ ልዕልና ለማስከበር ተጨማሪ ጥረት ሲደረግ ከሁሉም ብሔሮች በተለየ በትግራይ ተወላጆች ላይ የእስር ማዘዣ ይወጣል፡፡