ሰሞኑን የህወሓት አመራሮች፣ አባላትና ደጋፊዎች ነገረ-ሥራ በብዙዎች ዘንድ ግርምትን ፈጥሯል። ለምሳሌ የትግራይ ክልል ም/ፕረዜዳንት ዶ/ር ደብረፂዮን ገብረሚካኤል “ሜ/ጄ ክንፈ ዳኘውን እጁን ይዘን ለፌደራል መንግስት የሰጠነው እኛ ነን” ካሉ በኋላ “እጁ በሰንሰለት ታስሮ በቴሌቪዥን መታየቱ” የትግራይን ህዝብ ለማሸማቀቅ፣ ለፖለቲካ ዓላማ ሲባል የተፈፀመ እንደሆነ ተናግረዋል። የዓረና ፓርቲ ሊቀመንበር የሆነው አቶ አብርሃ ደስታ ደግሞ ከዋልታ ጋር ባደረገው ቃለ-ምልልስ “ህወሓቶችን አሳልፈን አንሰጥም! ነገር ግን ህወሓት እንዲመራን አንፈቅድም” ማለቱን ሰማሁ።

ትላንት “ሰፊው ምህዳር” በተሰኘው የኤልቲቪ ፕሮግራም ላይ ባደረግነው ውይይት አቶ አስራት አብርሃም ተመሳሳይ ይዘት ያለው ነገር ሲናገር ነበር። ቀድሞ በኢትዮጵያዊ አንድነት ላይ ፅኑ አቋም የነበረው አስራት እልም ያለ ብሔርተኛ እና ከአክራሪ ከህወሓት አባላት በላይ ቀንደኛ የዶ/ር ደብረፂዮን ደጋፊና አድናቂ መሆኑ በጣም አስቆኛል። በእርግጥ አስራት እኔና ሌሎች ሰዎችን በብዙ ነገሮች ላይ ተጠያቂ አድርጎናል። ይህን ስል ግን በወዳጄ አስራት ላይ ምንም ዓይነት አሉታዊ ስሜትና አመለካከት ኖሮኝ አይደለም። ከውይይቱ በኋላም መንገዳችን እስከሚለያይ ድረስ አብረን እያወራንና እየተከራከርን ነው የሄድነው። ለማንኛውም ውይይቱ በቀጣዩ እሁድ በኤልቲቪ ስለሚተላለፍ እንድትመለከቱ ተጋብዛችኋል።

እንደው ነገሩን አልኩኝ እንጂ ህወሓቶች እና ዓረናዎች፣ እንዲሁም ገለልተኛ አቋም አለን የሚሉት ወገኖች በተጠቀሰው ጉዳይ ላይ ለምን አንድ ዓይነትና አቋም አመለካከት ሊኖራቸው እንደሚችል አውቅ ነበር። ነገር ግን አሁን ላይ በጉዳዩ ዙሪያ የሚሰጡ ሃሳብና አስተያየቶች በጅምላ የሚፈረጁና በአብዛኛው የአንባቢዎች ትኩረት ከፅሁፉ ይዘት ይልቅ በፀሃፊው ማንነት ላይ የሚያተኩሩ በመሆኑ ለአሁኑ በጉዳዩ ላይ የራሴን ትንታኔ እና የማጠቃለያ ሃሳብ ከመስጠት መቆጠብ መርጬያለሁ፡፡ ነገር ግን በዚህ ጉዳይ ላይ በተደጋጋሚ ስለፃፍኩ አሁንም ደግሜ ለመፃፍ አልፈለኩም። ከዚያ ይልቅ ከዚህ ቀደም በጉዳዩ ዙሪያ ባወጣኋቸው ፅሁፎች ውስጥ በማጣቀሻነት ስጠቀማቸው የነበሩ ሁለት ትንታኔዎችን እና አሁን በትግራይ ካለው ነባራዊ ሁኔታ ጋር በተመሳሳይ በሆነ ጉዳይ ላይ የቀረበን ዘገባ እንድታነቡት ጋብዤያችኋለሁ። እነዚህን በዋቢነት የተጠቀሱ ፅሁፎችን በጥሞና ያነበበ ሰው ህወሓቶች እና የትግራይ ልሂቃን እያሳዩት ያለው ተመሣሣይ አቋምና ባህሪ ከምን የመነጨ እንደሆነ በአግባቡ መገንዘብ ይችላል፡፡ ከዚህ በመነሳት “ትጋሩዎች እና ሰርቦች፡ አክራሪ ብሔርተኝነት አንድ ላይ ያስተሳስራል- አንድ ላይ ያውራል!” በሚል ርዕስ የሚከተሉትን ፅሁፎች እንድታነቡ እጋብዛችኋለሁ፡፡

Advertisements