December 18, 2018e

ትንታኔ
የአብዮታዊ ዴሞክራሲ ትርክት መፈናቀልን አባብሷል፡፡

“ኢንተርናሽናል ዲሲፕለስመንት ሞኒተሪንግ ሴንተር” የሚባለው እና በዓለም በሀገራቸው ላይ ስደተኛ የሆኑ ዜጐችን ጉዳይ የሚያጠናው ተቋም ይፋ እንዳደረገው ኢትዮጵያ በአገር ውስጥ የስደተኞች ቁጥር ዓለምን ትመራለች:: ተቋሙ እንደገለፀው በፈረንጆች 2018 አጋማሽ ብቻ በዓለም ሶስት ነጥብ ሶስት ሚሊዮን ዜጐች ሲፈናቀሉ በኢትዮጵያ ደግሞ አንድ ነጥብ አራት ሚሊዮን ዜጐች ተፈናቅለዋል:: ይህ አኃዝ ጦርነት ካለባቸው ከነ የመን እና ሶሪያ ሁሉ የበለጠ ነው::
በ2018 አጋማሽ በኢትዮጵያ የተፈናቀሉ ዜጐች ከሶሪያ በ200ሺህ ይበልጣሉ:: ኢትዮጵያ የፖለቲካ ብልሽት እና የተፈጥሮ አደጋ ከገጠማቸው ሀገሮች ሁሉ በልጣ በሀገር ውስጥ ስደተኛ ብዛት ኡጋንዳን ተከትላ ደግሞ ከአፍሪካ ሀገራት ቀደሚ ሆናለች:: የኢትዮጵያዊያን መፈናቀል ከባለፈው የፈረንጆች ዓመት ጋር ሲነፃጻር በስድስት እጥፍ እየጨመረ እንደሄደ ጥናቱን ጠቅሶ አፍሪካ ኒውስ አስነብቧል::

የመፈናቀል መንስኤው

የህግና የፌዴራሊዝም ስርዓት ተመራማሪ የሆኑት አቶ ደሳለኝ በላቸው ይፋዊ ጦርነት ካለባቸው ሀገራት ይልቅ ኢትዮጵያ የራሷን ዜጐች በማሰደድ የምትመራው ቀደም ሲል ሀገሪቱ ስትከተለው በቆየችው አብዮታዊ ዴሞክራሲ ምክንያት ነው ይላሉ :: አሁን እየተሸረሸረ ቢሆንም የኢህአዴግ ርዕዩተ ዓለም አብዮታዊ ዴሞክራሲ ነው::
አቶ ደሳለኝ አብዮታዊ ዴሞክራሲ በባህሪው የጨቋኝ እና የተጨቋኝ፣ የአሸናፊ እና የተሸናፊነት ሜዳ በማዘጋጀት ህዝቦች በተቃራኒ እና በጐራ እንዲከፋፈሉ ያደርጋል ይላሉ:: ስርዓቱ የተዋቀረበት መንገድም ጥላችን እንደ ፖለቲካ መርህ በተከተለ ቅኝት በመሆኑ “እኛ እና እነሱ” የሚል የማያገናኝ የልዩነት ሸለቆ ተፈጥሯል::
“በአሸናፊ እና ተሸናፊነት ጐራ የተሰናሰለው ስርዓት ሀገሪቱን አሸናፊ ሊያደርግ አይችልም:: ሁሉም ካላሸነፈ ሀገሪቱ አታሸንፍም” የሚሉት አቶ ደሳለኝ መፈናቅሉም ህገ መንግስታዊ መሠረት ያለው ነው ብለው ይሞግታሉ::
በአብዮታዊ ዴሞክራሲ መርሆ መሠረት የተቃኘው የየክልሎች ህገ መንግስትም “ነባር እና መጤ” ብሎ ዜጐችን አንደኛ እና ሁለተኛ ደረጃ ዜጋ ብሎም ይፈርጅሉ ይላሉ አቶ ደሳለኝ::

የክልሎች ህገ መንግስት እና መፈናቀል

ከአማራ ክልል ውጭ ያሉት የብዙ ክልሎች ህገ መንግስት የመሬት ባለቤትነቱን ነባር ብለው ለሚያስቡት ብሔረሰብ ብቻ ይሰጣሉ:: ለአብነት የቤሽንጉል ጉሙዝ ክልል ህገ መንግስት ከበርታ እና ከጐሙዝ በእኩል አማራ እና ኦሮሞም በክልሉ ቢኖሩም ለአማራ እና ለኦሮሞ ህገ መንግስቱ እውቅና ይነፍጋል:: ቢሻንጉል ጉሙዝ ውስጥ አማራ መጤ መባሉ ህገ መንግስታዊ እና ስርዓታዊ ሆኖ ተዋቅሯል ይላሉ::
ስርዓቱ ግጭትን እንደ ፖለቲካ ማራዘሚያ ይጠቅምበት ስለነበር ከሦስት ሺህ ዘመን በላይ በጋራ የኖሩ ህዝቦች መለያየትን፣ መገደደልን፣ መጨካከን ክፉኛ እየለመዱት ይገኛል:: በአንድ ሀገር ውስጥ ልጅና የእንጀራ ልጅ እንዲፈጠር ስርዓቱ በተቋም ደረጃ ሰርቷል:: ይህ ሁኔታ ኢትዮጵያውያን ከኢትየጵያ በመፈናቀል ከዓለም የመጀመሪያ በመሆን ያደፈ ታሪክ እንዲኖራት እያደረገ መሆኑንም አቶ ደሳለኝ አስረድተዋል ::
በህገ መንግስቱ ጉደይ ጥናት የሰሩት እና “አንቀፅ 39 ” የሚል መፅሐፍ የጻፉት አቶ ውብሸት ሙላትም ህገ መንግስቱ “ታጋይ” ነን የሚሉ ወገኖች ጫካ ላይ እያሉ የፃፉት በመሆኑ የጫካ እሳቤ ይስተዋልበታል ይላሉ:: የህገ መንግስቱን መሻሻል በመፍትሔነትም ይወሰዳሉ::

ህገ መንግስቱ የፈጠረው ህዝባዊ እሳቤ

የዜግነት እና የሀገር ክብር በብሔር ላይ ብቻ ወድቋል:: ከሀገር በላይ ብሔር በመግነኑም ብሔርተኞች ከኔ ወዲያ ሌላው አይመለከተውም ብለው በራሳቸው ግዛት የሚኖረውን የሌላ ብሔር አባል እየገፉት ነው ይላሉ አቶ ደሳለኝ::
አማራን በጠላትነት ፈርጆ የተነሳው ስርዓት ገና ከ1983 ዓ.ም ጀምሮ በአማራው ላይ መፈናቀል አስከትሏል:: ይህ መፈናቅል በአማራው ላይ ተጀምሮ ተጠናክሮ ይቀጥል እንጅ ሌሎች ህዝቦችንም አዳርሷል” የሚሉት አቶ ደሳለኝ ህዝቦች በጠላትነት እንዲተያዩ ህጐችና ስርዓቶች ሠርተው አልፈዋል ሲሉ ያስረዳሉ::
በሰመራ ዩኒቨርስቲ የህግ መምህር የሆኑት መምህር ጌትነት አያሌውም እንደ ስርዓት አማራን በጨቋኝነት ፈርጆ የተነሳው ስልተ መንግስት ጥላቻን አምርቶ በማህበረሰቡ ዘንድ ጥርጣሬን አንግሶ ወደ ማያባራ መፈናቀል መርቷል ይላሉ::

መፈናቀል እና ኢኮኖሚ

ካደጉበት ቀየ፣ ቡና ተጠራርተው ከኖሩበት መንደር፣…. በድንገት ተፈቅሎ መውጣት ስነ – ልቦናዊ ሸክሙ ከባድ ነው:: ይህ የስነ – ልቦና እና የማህበረሰባዊ ትስስር መላላት በተፈናቃዮች ጤና ላይ እክል ይገጥማል:: ጤነኝነታቸው አደጋ ውስጥ ይወድቃል::
በባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ የስነ – ምጣኔ ሀብት መምህር የሆኑት ዶክተር ለጤናህ እጅጉ በተፈናቃዮች ላይ የሚደርሰው መገፋት ጤነኝነታቸው ላይ እንቅፋት ስለሚፈጥር መንግስት ተጨማሪ የጤና ተቋማት ያስፈልጉታል:: ይህ ደግሞ ከመደበኛ በጀት ውጭ በመሆኑ ልማትን ይጐዳል:: መፈናቅል አቅም ያለውን ሰራተኛ በድንኳን እንዲኖር ስለሚያደርግ የሀገር ኢኮኖሚ እንዲንገዳገድ ያደርጋል::
ከሰብአዊ መብት ጥስቱ በተጨማሪ የሀገር ውስጥ መፈናቅል የስራ ወኔንና ዘላቂ ልማትን በማዳከም እድገትን ቁልቁል እንዲጓዝ እንደሚያደርግ ዶ/ር በጤናው ያስረዳሉ::

የመፈናቀል መፍትሔው ምን ይሆን?

በሰመራ ዩኒቨርሲቲ የህግ መምህር የሆኑት አቶ ጌትነት አያሌው ከህግ አኳያ ኢትዮጵያ እ.ኤ.አ በ2009 የካምፓላ ስምምነትን ተቀብላ ማፅደቅ አለባት ይላሉ:: የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮችን በተመለከተ በካምፓላ በተካሄደ ጉባኤ 40 የአፍሪካ ሀገራት ፈርመዋል:: 27 ሀገራት ፈርመው አፅድቀዋል::
“ኢትዮጵያ ፈረመች እንጅ አላፀደቀችም” የሚሉት መምህሩ፤ ብታፀድቅ ኑሮ ተፈናቃዮች ከዓለም አቀፍ ተቋማት እርዳታ እንዲያገኙ ይረዳ ነበር ይላሉ:: መንግስት ግዴታውን እንዲወጣም ስምምነቱ ያዝዛል ይላሉ:: ከዚህ በተጨማሪም በሀገሪቱ ምክር ቤት በ1980 ዎቹ ከተቋቋመው የብሔራዊ አደጋ መከላከል እና ዝግጁት ኮሚሽን ውጭ በምክር ቤቱ የሚመራ ብሔራዊ የተፈናቀዮችን ጉዳይ የሚመለከት ተቋም ያስፈልጋል ይላሉ::
አቶ ደሳለኝ በላቸው ደግሞ የህግ ክፍተቶችን ማረም፣ ሀገራዊ እና ብሔራዊ ማንነቶችን ማጣጣም፣ ህዝብና ህዝብን ማቀራረብ ተገቢነት እንዳለው ያስረዳሉ::

ተፈናቃዮች ምን አሉ

በዚህ ሰሞን ብቻ ከተለያዩ ክልሎች ከ28ሺ በላይ አማራዎች ተፈናቅለዋል:: መንግስት ለተፈናቃዮች የሰጠው ምላሽ ደካማ እንደሆነም እየተናገሩ ነው:: መምህር እያሱ በርሄ እና የግብርና ባለሙያው አቶ አማረ ዳርጌ ከመደበኛ ስራቸው ከትግራይ ክልል ከሐምሌ ጀምረው ተፈናቅለው ቆቦ ከተማ በድንኳን ኑሯቸውን እየመሩ ነው:: ከቤተሰብ ጋር መገናኘትም ሆነ ወደ ስራ ለመሰማራት ተቸግረዋል:: መንግስትም ተግባራዊ ምላሽ መስጠት እንዳልቻለ ይናገራሉ፤ ለአምስት ወራት ያህልም ያለስራ ተቀምጠዋል::

በአዴፓስ በኩል መፍትሔው ምንድን ነው?

ለዘመናት በተሰራው አማራ ጠል ፖለቲካዊ ትርክት እና አማራ በሀገር ግንባታ ምክንያት በተለያዩ ክልሎች እንደመገኘቱ ከክልሉ ውጭ ያለው አማራ ልዩ ትኩረትን እንደሚሻ የህግ ባለሙያዎቹ ያሰምሩበታል::
የአማራ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ /አዴፓም/ መስከረም መጨረሻ አካባቢ ባደረገው ጉባኤ ከክልሉ ውጭ ያለው የአማራ ህዝብ የፖለቲካ ውክልና እንዲያገኝ እስራለሁ ማለቱ ይታወሳል:: ለመፈናቀል መንስኤ የሆነውን የተዛነፈ ታሪክ ለማረቅም እንደሚሰራ ገልጾ ነበር::
በአማራ ክልል በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የማህበራዊ ዘርፍ ኃላፊና የባህልና ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊ አቶ ንጉሱ ጥላሁን ከአምና እስከ ዘንድሮ ተፈናቃዮች ከተፈናሉባቸው ቦታዎች ድርስ በመሄድ ምላሽ እየሰጠን ነው ብለዋል:: በዘላቂነት ለመፍታትም አዴፓ መዋቅሩን በሌሎች ክልሎችም ዘርግቷል:: እንደ ቤኒሻንጉል ባሉ ክልሎች ደግሞ የአዴፓ መዋቅር እስከ ወረዳ ድረስ እየተዘረጋ ነው ያሉት አቶ ንጉሱ ለተፈናቃዮች ጊዜያዊ መፍትሔ ለመስጠት ደግሞ የምግብ እና መጠለያ አገልግሎት በበቂ ሁኔታ ባይሆንም እየቀረበ ነው ብለዋል::
አቶ ንጉሱ መፈናቀሉን ከየክልሎች እና ከፌዴራል መንግስቱ ጋር በመነጋገር እልባት ለመስጠት እንቅስቃሴ ላይ ነን ያሉ ሲሆን፣ለዘላቂ መፍትሄውም እንሰራለን ብለዋል::
በኩር ጋዜጣ
በየሺሀሳብ አበራ ታሕሳስ 08/2011 ዕትም