March 1, 2019t

በቀጣይ ዓመት በሚከናወነው ሀገራዊ ምርጫ የሲቪክ ማህበራት ከፍተኛ ሚና እንደሚኖራቸው የብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ ወይዘሪት ብርቱካን ሚደቅሳ ተናገሩ።
ወይዘሪት ብርቱካን ሚደቅሳ ይህንን ያሉት በዛሬው ዕለት የሲቪክ ማህበራቱ በቀጣዩ ዓመት በሚደረገው ምርጫ ላይ ሊኖራቸው በሚገባው ሚና ዙሪያ እያደረጉት በሚገኙት ውይይት ላይ ነው።
ውይይቱ በገዢው ፓርቲና በተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች መካከል የነበረውን ሰፊ የግንኙነት ልዩነት ያጠባል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
በውይይቱ ላይ ቁጥራቸው 70 የሚሆኑ የሲቪክ ማህበራት በመሳተፍ ላይ የሚገኙ ሲሆን በአውሮፓ ህብረት አጋዥነት ነው እየተካሄደ የሚገኘው።
ወይዘሪት ብርቱካን ሚደቅሳ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ከዚህ ቀደም ከማህበራቱ ጋር ያለው ግንኙነት ሰፊ እንዳልነበረ በውይይቱ ላይ አንስተዋል።
በቀጣይ በሚካሄደው ምርጫ ግን የሲቪክ ማህበራቱ በስፋት እንዲሳተፉ ለማድረግ ቦርዱ እየሰራ እንደሚገኝም ገልጸዋል።
በውይይቱ ላይ ሲቪክ ማህበራቱ በቅድመ ምርጫ፣ በምርጫ እና በድህረ ምርጫ ሊኖራቸው ስለሚገባው ሚና ተነስቷል።
እንዲሁም ምርጫውን ምክንያት በማድረግ አለመግባባቶች ቢፈጠሩ ማህበራቱ ሰላማዊ በሆነ መንገድ መፍታት በሚችሉባቸው አግባቦች ላይ ውይይቶች ተካሂደዋል።
ማህበራቱ ገለልተኝነት እንዲኖራቸውም የበጀት ድጋፋቸው ከዓለም አቀፍ ድርጅቶች እንዲሆን መደረጉም በውይይቱ ተገልጿል።
በዙፋን ካሳሁን እና በሶዶ ለማ/ ኤፍ.ቢ.ሲ364
