March 9, 2019
አዲስ አበባ፣ የካቲት 29፣ 2011(ኤፍ.ቢ.ሲ) ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ አዲሱ የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ዶክተር አምባቸው መኮንን በአዲስ መንገድ አዲስ አስተሳስብና መንፈስ የአማራ ክልልን ህዝብ ከመቼውም ጊዜ በበለጠ ደረጃ እንደሚያገለግሉ ያለቸውን እምነት ገለፁ፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ ለቀድሞው የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ገዱ አንዳርጋቸው በባህር ዳር ከተማ በተዘጋጀ የሽኝት ስነ ስርዓት ላይ ተገኝተዋል፡፡
በስነስርዓቱ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባደረጉት ንግግር የቀድሞው ርዕሰ መስተዳድር አቶ ገዱ አንዳርጋቸው በአመራር ዘመናቸው የነበራቸውን በእርጋታ የማሰብና የመወሰን ብቃታቸውን አድንቀዋል።
ከጥቂት ቀናት እረፍት በኋላም ለሚወዱት ህዝብ በሌላ መንገድ ለማገልገል ለአዲስ ፈተና እና ለአዲስ ተግዳሮት መዘጋጀት እንዳለባቸው አሳስበዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ አዲሱ ርዕሰ መስተዳድር ዶክተር አምባቸው መኮንን የአማራ ክልልን ህዝብ ከሌሎች የሀገሪቱ ህዝቦች ጋር ያለውን አንድነትና መፈቃቀድ እንደሚያጠናክሩ የፌደራልና የሌሎች የሀገሪቱ ክልሎች መንግስታት እምነት የጣለባቸው መሆኑንም ነው የተናገሩት፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ ዛሬ በአማራ ክልል የተካሄደው የስልጣን ሽግግር ለሌሎች አመራሮች ትምህርት እንደሚሆንም ተናግረዋል፡፡

ማንኛውም ስልጣን ላይ ያለ አካል እንደ አቶ ገዱ በኩራት ስልጣኑን እንዲያስረክብ በተሰጠው ስልጣን ለሰላም፣ ለህዝብ እንደነት፣ እኩልነትና ፍትሃአዊ ተጠቃሚነት መስራት እንዳለበት ነው ያሳሰቡት፡፡
“በለው በለው” ለውጭ ወራሪ ጠላት እንጂ ለሀገሪቱ ህዝቦች የማይበጅ ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ፥ የኢትዮጵያ ህዝቦች የጋራ ቤተሰብ ያላቸው የተዋለዱና የጋራ ታሪክ የተጋሩ በመሆኑ መለያየት አይቻልም ሲሉ ተናግረዋል፡፡
አሁን ላይ በሀገሪቱ በየቀኑ መጥፎ ዜናዎች የሚሰሙ መሆኑን በመግልጽ፥ አመራሩ ችግሮችን በመጋፈጥ በአሸናፊነት ትውልድን ወደ ተሻለ ደረጃ ማሸጋገር ይጠበቅበታል ብለዋል፡፡
ለዚህም የኢትዮጵያ ህዝብ የዘመናት ታሪክን ብቻ ሳይሆን የቅርቡንም ችግር ይቅር ማለት እንደሚያስፈልግ ነው ተናገሩት፡፡
አሁን ላይ ሀገሪቱን የገጠማት ችግር በአንድነት ብቻ የሚፈታ መሆኑን በመጠቆም ለአፍታ እርካታ የሚከናወኑ ተግባራት መኖራቸው አንስተዋል፡፡
የህዝቦችን አብሮ የመኖር እሴቶችን የሚሸረሽሩ ተግባራት ነገ ከታሪክ ተወቃሽነት እንደማያድኑም አስገንዝበዋል፡፡
በስነ ስርዓቱ ላይ ለቀድሞ የአማራ ክልል ርእሰ መስተዳድር አቶ ገዱ አንዳርጋቸው የእውቅና ሚዲሊያ ተብርክቶላቸዋል፡፡
