25 November 2015 ተጻፈ በ 

 

የኢትዮጵያና የሱዳን ድንበርን የማካለል ሥራ በሚቀጥለው ወር እንደሚጀመር  ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ መግለጻቸውን፣ ሱዳን ትሪቡን የተባለው የሱዳን ድረ ገጽ ዘገባ አመለከተ፡፡

የሱዳን ሁለተኛ ምክትል ፕሬዚዳንት ሃሳቦ መሐመድ አብዱልራህማን ኅዳር 13 ቀን 2008 ዓ.ም. ከጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ጋር መወያየታቸውን ብሔራዊ የቴሌቪዥን ጣቢያ የሆነው የኢትዮጵያ ብሮካስቲንግ ኮርፖሬሽን ቢገልጽም፣ ከውይይቱ ጭብጦች መካከል የድንበር መካለሉን ጉዳይ አልጠቀሰም፡፡ ይሁን እንጂ የቴሌቪዥን ጣቢያው የሁለቱ አገሮች የጋራ ኮሚሽን ነፃ የኢኮኖሚ ዞን፣ አመቺ ነፃ የንግድ ሥርዓትና የባንክ ትብብር ለማድረግ መስማማቱን ዘግቧል፡፡

የሱዳን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ዴኤታ ከማል አልዲን ኢስማኤል ለሱዳን ትሪቡን ገለጹ እንደተባለው ግን፣ የሱዳን ሁለተኛ ምክትል ፕሬዚዳንት ሐሳቦ መሐመድ ከጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ጋር በተወያዩበት ወቅት ካነሷቸው ጉዳዮች አንዱ የድንበር ማካለል ይገኝበታል፡፡

ከዓመት በፊት ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያምና የሱዳን ፕሬዚዳንት ኦማር ሐሰን አል በሽር የድንበር ማካለሉ የሚከናወንበትን ወቅት የሁለቱ አገሮች የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴሮች እንዲወስኑ ተስማምተው ነበር፡፡

ማካለሉ የሚከናወነው በተለይ ሁለቱ አገሮች በአማራ ክልል ውስጥ በሚዋሰኑበት ድንበር የሚገኝ 250 ካሬ ኪሎ ሜትር ቦታ ላይ በሱዳን በኩል የይገባኛል ጥያቄ በመኖሩ ነው፡፡

የድንበር ማካለሉ ሥራ በታኅሳስ ወር ይጀመራል ቢባልም፣  የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አቶ ተወልደ ሙሉጌታ በጉዳዩ ላይ መረጃ እንደሌላቸው ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያምና የሱዳን ሁለተኛ ምክትል ፕሬዚዳንት በዚህ ጉዳይ ላይ ስለመወያየታቸውም ዝርዝር መረጃ እንደሌላቸው ተናግረዋል፡፡

በሌላ ዜና በኢትዮጵያና በኬንያ ድንበር በተቀሰቀሰ ግጭት ሦስት የኬንያ ፖሊሶች መገደላቸውን ተከትሎ፣ በአካባቢው ውጥረት መንገሱን የኬንያ ሚዲያዎች እየዘገቡ ይገኛሉ፡፡

ዘ ሲትዝን የተባለው የኬንያ ጋዜጣ እንደዘገበው ሦስት የኬንያ ፖሊሶች በኢትዮጵያ ወታደሮች ከተገደሉ በኋላ፣ የኬንያ የመከላከያ ኃይል ሶሎሎ በተባለችው የኬንያና የኢትዮጵያ ድንበር እንዲሰማሩ ተደርገዋል፡፡

የኢትዮጵያ ወታደሮች ግድያውን የፈጸሙት የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ) አባላትን እየተከታተሉ በነበረበት ወቅት መሆኑን ዘገባው ያመለክታል፡፡

በጉዳዩ ላይ ሪፖርተር ያነጋገራቸው የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አቶ ተወልደ፣ በኢትዮጵያና በኬንያ ድንበር ላይ ያለው ግጭት በተደጋጋሚ የሚከሰት መሆኑን ገልጸዋል፡፡

በአካባቢው ያሉ አማፂያን በሁለቱም አገሮች ድንበር በመዝለቅ የሚፈጽሙት ችግር እንደሆነ፣ ይህንን ችግር ለመፍታትም የሁለቱ አገሮች የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴሮች ቅርንጫፍ ቢሮዎች እየተወያዩ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ ይህ ችግር ጠንካራ በሆነው የኢትዮጵያና የኬንያ ወዳጅነት ላይ ተፅዕኖ ሳይፈጥር መስተካከል የሚችል መሆኑን የገለጹት አቶ ተወልደ፣ ኢትዮጵያና ኬንያ አሸባሪ የሆነውን አልሸባብን ለመታገል የተሠለፉ አገሮች መሆናቸውን አስታውሰዋል፡፡

Source   +  Ethiopian Reporter

 

Leave a Reply