ወያኔ አዲስ አበባ የመግባት ፈቃድ ባኘበት የለንደኑ ስመ ድርድር ላይ ተዋናይ ከነበሩት አሜሪካዉያን አንዱ ኢትዮጵያ ወደብ ያስፈልጋታል የሚል ሀሳብ ሳነሳ መለስ አያገባህም አለኝ በማለት ነገሩ ካለፈ በኋላ መናገራቸውን እናስታውሳለን፡፡የኤርታር ጉዳይ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት መድረክ ክርክር ይካሄድበት በነበረበት ወቀት ኤርትራ ራሷን የቻለች ሀገር አንድትሆን ይከራከር የነበረው ጣሊያን ሳይቀር ኢትዮጵያ በአሰብ በኩል ወደብ እንድታገኝ ይደግፍ ነበር፡፡አቶ መለስና ድርጅታቸው ግን ከጣሊያንም ብሶ ኤርትራን በማስገንጠል ሳይወሰን ኢትዮጵያ በየትም አቅጣጫ የባህር በር እንዳይኖራት አደረጉ፡፡

ወደብን የሚያህል ነገር የግመል መጠጫ ብለው አናንቀው አሳልፈው የሰጡ ለሀገር ክብርና ሉአላዊነት፤ ለዳር ድንበር መጠበቅ ወዘተ ደንታ የሌላቸው ሰዎች ባድመ በኤርታራ ተወረረ ብለው ሁለት መላጣዎች በማበጠሪያ ሲጣሉ የሚል ስላቅ ላስከተለ ጦርነት ኢትጵያውያንን ሲማግዱ ነገሩ እንቆቅልሽ ነበር፡፡ የጦርነቱ ሂደትና አፈጻጸም በተለይም  በፊሽካ አንደሚቆም የስፖርት ውድድር ጦርነቱ  በአቶ መለስ ትዕዛዝ የቆመበተ ምሲጢር ፣ከዚህ በኋላም ይግባኝ የሌለው ውሳኔ ለመቀበል በመስማማት ወደ አለም አቀፍ ፍርድ ቤት የተኬደበት ሁኔታ በአቶ መለስ ብቻ የሚታወቅ እንቆቅልሽ ነበር፡፡

የኢትዮፕን ሕዝብ ምንም አንደማያውቅ አድርገው ተፈርዶባቸው ተፈረደለን ብለው የአለም አቀፍ ፍርድ ቤት የወሰነው ውሳኔ ምስጢር ተደርጎ የሚያዝ ወይንም ከሕዝብ ተደብቆ የሚቀር ይመሰል ህዝቡ በአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ ወጥቶ ደስታውን እንዲገልጽ ጥሪ ማስተላለፋቸውም ሌላኛው አንቆቅልሽ ነበር፡፡

አድበስብሰው ለማለፍ ያደረጉት ሙከራ ሁሉ ከሽፎ ከየአቅጣጫው በተለይ ከትግራዊያን ተቃውሞ ሲበረታባቸው በውሳኔው መሰረት  በመሬት ላይ ችካል ቸክሎ የድንበር ማካለል ለማካሄድ ሰዎችን ያለ ፍላጎታቸው ወደዛና ወደዚህ የሚያደርግ ስለሆነ ውሳኔውን አንቀበላለን ስለ አፈጻጸሙ ግን አንነጋገር የሚል ጥያቄ አነሱ፡፡ ይህ ጥያቄ በሻዕቢያ በኩል ተቀባይነት ባለማግኘቱም በሁለቱ ሀገሮች መካከል ይሄው እስከ ዛሬ ሰላምም ጦርነትም የለም፡፡

ይን ያነሳሁት ስለ ባድመ ለማውራት ፈልጌ አይደለም፡፡ለሱዳን መሬት ለመስጠት የተነሳሱበት ምክንያት አንቆቅልሽ ቢሆንብኝ እንጂ፡፡ሱዳኖች የመሬት ይገባኛል ጥያቄ አነስተው በጉልበትም ይሁን በህግ ያደረጉት ነገር ስለመኖሩ አልሰማንም፡፡በአካባቢው የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንም ተጠይቀው ፈቃደኝነታቸውን አልገለጹም፡፡ በዚህ ሁኔታ ወያኔዎች ከመሬት ተነስተው አለያም ውስጥ ለውስጥ ተነጋግረው ለም መሬት ለሱዳን ለመስጠት መነሳታቸው ለኢትዮጵያውያን አንቆቅልሽ ነው፡፡ አቶ መለስ የቋጠሩትና ለጥቂት ታማኝ ወዳጆቻቸው በአደራ ያስተላለፉት ምስጢር እንደሆነ የሚገመት የድንበር ጉዳይ በኢህአዴጋውያን ቀርቶ ህውኋቶችም ሁልም የሚያውቁት ስለመሆኑ ያጠራጥራል፡፡

ያ ባድመ ላይ የታየ የአለም አቀፍ ፍርድ ቤትን ውሳኔ ተግባራዊ እስካለማድረግ የዘለቀ ወኔ የት ገባ፡፡ ነው ወይንስ ለወያኔ ከትግራይ የሚወሰድና ከቀሪው የኢትዮጵያ ክፍል የሚወሰድ መሬት ልዩነት አለው፡፡ ነው ወይንስ ሰሞኑን እየተነገረና እየተጻፈ እንዳለው ኢትዮጵያ መግዛት የማይችሉበት ደረጃ ሲደርሱ ትግራይን ገንጥለው ወደ ሚመሰርቱት ሀገር ለማጠቃለል እስከዛ በሱዳን እጅ  በአደራ እንዲቀመጥላቸው ነው፡፡

ወያኔዎች ከወያኔዎቹም የተለዩት ወያኔዎች በተለይ አቶ መለስ እስከ 1991 ዓ.ም የፈጸሙዋቸው የኢትዮጵያን ጥቅሞች የማሳጣትና የመጉዳት ተግባር ሁሉንም በሻዕቢያ በኩል እናገኘዋለን ከሚል እቅድ ይመስል ነበር፡፡ የሞታችሁለትን ኤርታራን የማስገንጠል ዓላማችሁን ተግባራዊ ስታደርጉ ቢያንስ ኢትዮጵያ የባህር በር እንዳታጣ አሰብን አትስጡባት ሲባሉ ጦረኞች የቀድሞ ሥርዓት ናፋቂዎች ህዝቡን ሳይሆን መሬቱን የሚፈልጉ ወዘተ እያሉ የውግዘት መአት ሲያወርዱና ከሻዕቢያ ብሰው ጠያቂዎቹን ሲያጠቁ  ለነጋ ትግራይ ወደብነት አሰብ በወዳጃችን እጅ ትቆይልን ብለው ያደረጉት ነው በማለት ብዙ ኢትዮጵያውያን ጥርጣሬአቸውን ይገልጹ ነበር፡፡ ግና ፈጣሪ ኢትዮጵያን አይረሳትምና ያሰቡት ሁሉ እንዳይሆን ሆኖ ጸባቸው ከራሳቸው አልፎ ለመላው ኢትዮጵያውያን ተረፈ፡፡ ወያኔዎች ግን መቼም በምንምና ከምንም የማይማሩ ናቸውና ዛሬም የኢትዮጵያን ሉዐላዊነት እየተፈታተኑ ዳር ድንበሯን እያስደፈሩ ለም መሬቷን( በአደራ ለማስቀመጥም ይሁን፣ በሽፍትነት ዘመናቸው ለተደረገላቸው ውለታም ይሁን  በሽያጭም ይሁን ) ለመስጠት ሽር ጉድ እያሉ  ነው፡፡

ብሶት ደስታውን ቁጭት ፍላጎቱን በቀረርቶ በመግለጽ የሚታወቀው የሀገሬ አርሶ አደር መሬት እግር አለው ይሄዳል እንደ ሰው፣ ጀግና ልጅ ተወልዶ ቦታው ካልመለሰው ይላል፡፡ አባቶቻችን በየዘመናቱ ከየአቅጣጫው ከመጡ ወራሪዎች ጋር ተፋልመው ወድ ህይወታቸውን ሰውተው ያቆዩአት ሀገር በሀገር በቀል እንቆቅልሽ ፍጥረቶች አለም የሚያውቃት መልኳ ተቀይሯል፡፡ አልባ ብሎአቸው ዛሬም ድንበሯን አስገፍተው በአለም ካርታ ላይ ሌላ ቅርጽ ሊያሰጧት ነው፡፡ለነገ ያሰቡትን ደግሞ አናውቀቅም፡፡

ሀገር እግ አለው ይሄዳል አንደ ሰው አንደተባለው ያለፈው ሲቆጨንና ዛሬም ሌላ ሊሄድ ነው፡፡ በባለፈ ከመቆጨት የአሁኑን እኩይ ሴራ በመግታት ባለበት በነበረበት እንዲቆም ማድረግ የዚህ ትውልድ ታሪካዊ ኃላፊነት ነው፡፡ኮረኔል ምግሽቱ በቅርቡ አንደተናገሩት በርሳቸው የሥልጣን ዘመን ሱዳኖች አንድም ግዜ የድንበር ማካለል ጥያቄ አቅርበው አያውቁም፡፡ አሁንም ወያኔ በድንበር ማካለል ስም መሬት ለመስጠጥ የጠነሳው በሱዳኖቹ ጥያቄ ስለመሆኑ በቂ ማረጋገጫ የለም፡፡ ቢሆንም ደግሞ መሬት የተስካር ዳቦ አይደልም ለጠየቀ ሁሉ እየተቆረሰ የሚሰጥ፡፡

የድንበር ማካለል በድብቅ ጓዳ ለጓዳ በሚደረግ ስምምነት የሚካሄድ አይደለም፡፡ ሁለት ወዳጃሞች ወይንም ባለውለታዎች እዛና እዚህ ሥልጣን ላይ ሥላሉ የሚከናወንም አይደለም፡፡ የራሱ ሂደትና የአፈጻጸም  ሕግና ስርዓት አለው፡፡ ይህ ሁሉ እንቆቅልሽ ሲጠቃለል ምክንያቱ አንድ ነገር ነው፡፡ የወያኔ ኢትዮጵያዊ አጀንዳ አለመኖር፡፡ ሀገራዊ ስሜትና ኢትዮጲያዊ አጀንዳ ሳይዙ ሀገር መግዛት ደግሞ ቅኝ ግዛት ይሆናል ፣ሌላ እንቆቅልሽ፡፡

Source    =   Ethiopian Media Forum