የኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት ከአዲስ አበባ ከተማ ሊያገኝ ስለሚገባው ልዩ ጥቅም የሚያጠና ግብረ ኃይል አቋቋመ፡፡ የተቋቋመው ግብረ ኃይል በክልሉ ከፍተኛ የፖለቲካ አመራሮች የተዋቀረ መሆኑ ታውቋል፡፡ በ1987 ዓ.ም. የፀደቀው ሕገ መንግሥት አንቀጽ 49(5) ላይ እንደተደነገገው፣ የኦሮሚያ ክልል የአገልግሎት አቅርቦት ወይም የተፈጥሮ ሀብት አጠቃቀምና የመሳሰሉትን ጉዳዮች በተመለከተ፣ እንዲሁም አዲስ አበባ በኦሮሚያ ክልል መሀል የሚገኝ በመሆኑ የሚነሱ ሁለቱን የሚያስተሳስሩ አስተዳደራዊ ጉዳዮችን በተመለከተ ያለው ልዩ ጥቅም ይጠበቅለታል፡፡ ኦሮሚያ ክልል ስለሚያገኘው ልዩ ጥቅም በዝርዝር በሕግ እንደሚወሰን ሕገ መንግሥቱ በግልጽ አስቀምጧል፡፡ ነገር ግን ሕገ መንግሥቱ ከፀደቀ 20 ዓመታት ቢቆጠሩም ዝርዝር ሕጉ ባለመውጣቱ፣ በተለያዩ ምሁራን ጥያቄ ሲነሳ ቆይቷል፡፡ የኦሮሚያ ክልል መንግሥት ካቢኔ አባልና የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ኃላፊ አቶ ፍቃዱ ተሰማ ከሪፖርተር ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ እንደገለጹት፣ የኦሮሚያ ክልል ከአዲስ አበባ ማግኘት ያለበት ልዩ ጥቅም እየተጠና ነው፡፡ ‹‹ሕገ መንግሥቱ ላይ የሰፈሩ ድንጋጌዎች በሙሉ ተተርጉመው ወደ ተግባር ተሸጋግረዋል ማለት አይቻልም፡፡ ምክንያቱም ሕገ መንግሥት ትልቅ ፍኖተ ካርታ (ሮድማፕ) ነው፤›› በማለት ሕገ መንግሥቱ በርካታ ጉዳዮችን አቅፎ መያዙን አቶ ፈቃዱ አስረድተዋል፡፡ በዚህ ጊዜ ውስጥ ቅድሚያ የሚሰጣቸው ትላልቅ ጉዳዮች ተለይተው መሠራታቸውን አቶ ፍቃዱ ገልጸው በተለይ የማንነት ጥያቄ፣ ራስን የማስተዳደርና የመልማት ጉዳዮች ትኩረት ተሰጥቶባቸው ሲሠራባቸው እንደቆዩ አመልክተዋል፡፡ ክልሉ እነዚህ ጉዳዮች ላይ ትኩረት ሰጥቶ ሲሠራ የቆየ መሆኑን አቶ ፍቃዱ ገልጸው፣ በአሁኑ ወቅት ግን ሁሉም ሥራዎች መልክ በመያዛቸው ወደ ልዩ ጥቅም ጉዳይ መገባቱን አስረድተዋል፡፡ ልዩ ጥቅም የማያካትትቸው ጉዳዮችና ከአዲስ አበባ ጋር በጋራ ለማደግ መደረግ ስለሚገባቸው ጉዳዮች በጥናቱ ምላሽ ይሰጣል ተብሏል፡፡ ጥናቱ ምን ያህል ጊዜ እንደሚፈጅና መቼ ወደ ሥራ እንደሚሸጋገር አቶ ፍቃዱ ያሉት ነገር የለም፡፡ ውድነህ ዘነበ ከአቶ ፍቃዱ ጋር በኦሮሚያ ክልል ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ያደረገውን ቃለ ምልልስ ለመመልከት እዚህጋ ይጫኑ ፡፡

Source    =  Ethiopian Reporter

 

Leave a Reply