Tuesday, 29 December 2015 07:12

Written by  አለማየሁ አንበሴ

 “ግጭቱን ተከትሎ እስከ 4ሺ ሰዎች ታስረዋል” ፓርቲው

 “በፓርቲ ሽፋን የሻዕቢያን ተልዕኮ ለማሳካት በተሯሯጡት ላይ እርምጃ ይወሰዳል” – ጠ/ሚ ኃይለማርያም

የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ (ኦፌኮ) ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ በቀለ ገርባና 6 ከፍተኛ አመራሮችን ጨምሮ ከ500 በላይ አባላት ሰሞኑን እንደታሠሩበት ፓርቲው ገለፀ፡፡ የኦፌኮ ዋና ፀሐፊ አቶ በቀለ ነጋ ለአዲስ አድማስ እንደተናገሩት፤ ጉርሜሣ አያኖ የፓርቲው ም/ሊቀመንበር፣ አዲሱ ቡላላ የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ፣ ደረጀ መርጋ የድርጅት ጉዳይ ሃላፊ፣ መ/ር አለሙ አብዲሳ ፀሐፊ፣ መ/ር ታሪኩ ኦዲተር፣  አቶ ደጀኔ ጣፋ ም/ዋና ፀሐፊ እንዲሁም አቶ በቀለ ገርባ ተቀዳሚ ም/ሊቀመንበር ሰሞኑን በፖሊስ ተይዘው ታስረዋል፡፡
ከፓርቲው አማካሪ ም/ቤት አባላት መካከልም የታሠሩ እንዳሉ የገለፁት ዋና ፀሐፊው፤ ከዞን አመራሮች የቄለም ወለጋ ዞን አመራር አቶ መሠረት ዳባ፣ የምስራቅ አርሲ ዶዶላ አመራር አህመድ ኢቦ፣ የባሌ አመራር አቶ ሁሴን አምዳ፣ የሆሮ ጉዱሩ አቶ ደገባስ ዋቀዩ፣ የኢሊባቡር አመራር አቶ እስማኤል ሁሴንና አቶ ያዛቸው አብዲሣ ታስረዋል ብለዋል፡፡
የወረዳ አመራሮችና ባለፈው ግንቦት በምርጫ የተሳተፉ ግለሰቦችን ጨምሮ እስከ 500 የሚደርሱ የፓርቲው አባላት በተለያዩ አካባቢዎች መታሠራቸውን አቶ በቀለ ገልፀው፤ ፓርቲው ባለው መረጃ መሰረት በአጠቃላይ ተቃውሞውን ተከትሎ የታሠረው ሰው ብዛት እስከ 4ሺ ይደርሳል ብለዋል፡፡
ከ300 በላይ የደረሱበት ያልታወቁ ሰዎች እንዳሉ የተናገሩት ዋና ፀሐፊው፤ በግጭቱ የቆሰሉ ከ1500 በላይ ተጎጂዎች በወሊሶ ሉቃስ ሆስፒታል፣ በቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል፣ በሚኒልክና በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ህክምናቸውን እየተከታተሉ እንደሚገኙ ገልፀዋል፡፡
የፓርቲው አመራሮችና አባላት የታሠሩበት ምክንያት ባይገለጽም በሌላ በኩል ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ትናንት በህዝብ ተወካዮች ም/ቤት ባደረጉት ገለፃ “የራሳቸውን ድብቅ አጀንዳን ይዘው የሃሰት ፕሮፖጋንዳ በማሠራጨት ህዝብን በማደናገር የሰው ህይወት እንዲጠፋ አቅደው የመሩ አካላት በህጋዊ ፓርቲ ሽፋን የሻዕቢያን ተልዕኮ የማሳካት በተሯሯጡ ሃይሎች ላይ መንግስት ህገመንግስታዊ እርምጃ ይወስዳል ብለዋል፡፡

Leave a Reply