Tuesday 19th of April 2016 07:14:11 AM
በሳውዲ ኢትዮጵያውያን ሠራተኞች ፍላጎት ከፍ ብሏል !
* ሳወዲዎች ይወዱናል ፣ ይጠሉናል
… የባለጸጎች ቤት ያለ በቂ የቤት ሠራተኛና ኦና ነው። የሳውዲ ወይዛዝርትና ልጃገረዶች መኪና መንዳት አይፈቀድላቸውምና እንዳሻቸው መውጣት መግባት ሲፈልጉ ውሎ አዳራቸው ያለ ሹፊር የሰመረ አይሆንም። በአጠቃላይ ያለ ቤት ሠራተኛና ሹፊር ኑሯቸው የሚመሰቃቀልባቸው ሳውዲዎች ባገኙት አጋጣሚ ሁሉ መንግሥትታቸው የሠራተኛ አቅርቦቱን እንዲያፋጥን እየወተወቱ ይገኛሉ። ባሳለፍነው ሳምንት የወጣው ታዋቂ ጋዜጣ ሳውዲ ጋዜጥ የቤት ሠራተኛ ፍላጎት መጨመሩን በመጠቆም Housemaids’ black market booms ብሎ የድለላውና የሕገ ወጥ ሠራተኛ አቅርቦቱ ገበያ ስለ መድራቱ ዘርዘር ያለ መረጃ አቅርቧል። በጥቁር ገበያ የአንድ ሰዓት ክፍያ እስለ 40 ሪያል ማሻቀቡን ጋዜጣው ጠቁሞ አንድ ሠራተኛ በወር በአማካኝ እስከ 9 ሽህ ሪያል ገቢ እንደሚያገኙ በዝርዝር ያስረዳል። ጋዜጣው በሳውዲ ቤተሰቦች ተመራጭ ካላቸውን የቤት ሠራተኞች መካከል በአንደኝነት የኢንዶኖዥያ ዜጎች ሲጠቀሱ በሁለተኛ ደረጃ የኢትዮጵያ ሠራተኞች ተመራጭ መሆናቸውንም አልደበቀም።
የተዘጋው የሠራተኛ አቅርቦት ጉዳይ ከወራት በፊት መነሳቱን የሳውዲ መንግሥት ሲያስታውቅ ከኢትዮጵያም በኩል አዲስ የሥራ ስምሪት ተረቆ መጽደቁ ይጠቀሳል። ጸደቀ በተባለው ረቂቅ ባለድርሻ ከሚባሉት መካከል በስደት የችግሩ ዳፋ ቀማሽ ስደተኛ እንዲመክርበት ያልተደረገው ረቂቂ ለሳውዲ መንግሥትት ከቀረበ ወራት ቢቆጠርም ከሳውዲ በኩል ሠራተኛ ስምሪቱን ለመጀመር በተፈለገው ፍጥነት ይሁንታን አልተገኘም። በአንጻሩ የኢትዮጵያ መንግሥት መገናኛ ብዙሃን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ከፍተኛ ኃላፋዎችን ዋቢ በማድረግ ደጋግነው “ስምምነቱ ጫፍ ላይ ደርሷል” ቢሉም የሥራ ስምሪት ስምምነት እስካሁን አለመፈረሙ ይጠቀሳል።
ስምምነቱ እንዳይፈረም ዋናው ምክንያት የሆኑት የሳውዲ አልሹራ የምክር ቤት አባላት መሆናቸው ሲያስታውቅ ከአንድ አፍሪካ አገር ጋር ለሳውዲ ምክር ቤት የቀረበውን ረቂቅ ተከትሎ የምክር ቤት አባላት በሰጡት አስተያየት ከኢትዮጵያ ጋር ሊጀመር የታሰበውን ስምምት መቃወማቸው ባሳለፍነው ሳምንት አረብ ኒውስ አስነብቦናል፡፡ በጋዜጣው የቀረበው መረጃ እንደሚያስረዳው ሱልጣን አል ሱልጣን የተባሉት የሳውዲ አልሹራ ምክር ቤት አባል ከዚህ ቀደም ስለተደረገው የቤት ሠራተኛ ቅጥር አንስተው “ማኅበረሰባችን ከአፍሪካ በቀጠርናቸው ሠራተኞች እጅግ አስፈሪና ሰቅጣች የሆነ ድርጊት ማየታችን አንርሳ ” ብለው መናገራቸው ተጠቅሷል። ሌላው የምክር ቤት አባል ናስር አልዳውድ “እንደኔ ተሞክሮ በተጠቀሰው አገር የመጡ ሠራተኞች በሽብርና በወንጀል ተሳታፊዎች እንደነበሩ አውቃለሁ” በማለት ተናግረዋል።
አስፍ አቡ ተንያን የተባሉት ሌላው የአልሹራ ምክር ቤት የቅጥር ጉዳይ አስተዳደር ባልደረባ በበኩላቸው “ይህ ከሆነ እውነቱ ከዚህች አገር ሠራተኞችን ለማስመጣት ማሰቡስ ለምንስ አስፈለገ ?” ብለው በመጠየቅ የአገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስትር ከኢትዮጵያ የሚመጡ ሠራተኞች በሚፈጽሙት ወንጀል ከፍ ያለውን ደረጃ የያዘችው ኢትዮጵያን መሆኗ በጋዜጣው ተመልክቷል፡፡ በሠራተኛ ስምሪቱ ዙሪያ አስተያየት የሚሰጡ ሳውዲ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን በበኩላቸው ሲናገሩ “ካለፈው አልተማርንም፤ ዛሬም በቂ ዝግጅት አልተደረገም ፤ ነገም ማዘናችን አይቀርም፡፡ ሌላ ስምሪት በከፋው ስማችን መባቻ አያዋጣም። በመላ ሳውዲ በመቶ ሽዎች የሚቆጠሩ ዜጎች እንደጨው ተበትነው ይገኛሉ። አንዳንዶች መዳረሻቸው አይታወቅም። ማንነታቸውን መለየት ሳይቻል ቀርቶ የተቀበሩ አሉ። የጅዳ ቆንሰልና የሪያድ ኢንባሲ ወደ ሳውዲ ስለመጡት ዜጎቻቸው አያያዝ መዳረሻቸው የሚያውቁት የለም። የሚታወቂት ቁጥር በጣም ትንሽ ነው። አደረ ራሻቸው የጠፋ፣ ታመው ማንነታቸው ሳይታወቅ ያሸለቡት፣ አብደውና ተሰናክለው ያሉበት የማይታወቀውን ቁጥር ቤቱ ይቁጠረው” ካሉ በኋላ ስለ አዲሱ ስምሪት ሲናገሩ “አሁንም ከበፊቱ አልተማሩም፤ ሥራው ሁሉ ለብለብ ነው፤ የቤት ሠራተኞች መብት ማስከበር የሚችል አደረጃጀት የለንም፡፡ የዜጎችን መብት ለማስከበር ክህሎቱ ያለው በቂ የሰው ኃይል በጅዳ ቆንስልና በሪያድ ኢንባሲ የለም። ገጽታችን ለመገንባት ከተፈለገ አሁንም ዝግጅቱ ይቅደም ” ሲሉ መንግሥት አሁንም እየሠራው ያለው ስህተት ብዙ እህቶችን ከቤተሰብ የሚለያይና የሚያሳዝን ፍጻሜ እንዳይሆን በውል ሊገነዘብ ይገባል ሲሉ አስተያየት ሰጥተዋል !
ቸር ያሰማን!!!!
http://gudnew.com