21 May, 2016
የሶማሌላንድ ገዢ ፓርቲ ፕሬዚዳንት ኢትዮጵያን ወቀ
ሊቀመንበሩ ሙስቢሂ አብዲ በዋናነት ኢትዮጵያን ይውቀሱ እንጂ፣ የሶማሌላንድ ጎረቤት የሆኑት ኬንያና ጂቡቲ ብሎም ኢጋድ ሚናቸውን አልተወጡም ብለዋል፡፡
ሶማሌላንድ በፕሬዚዳንት ዚያድ ባሬ ትመራ ከነበረችው ዋናው ሶማሊያ በመገንጠል ነፃነቷን ካወጀች 25ኛ ዓመቷን ባለፈው ረቡዕ ግንቦት 10 ቀን 2008 ዓ.ም. አክብራለች፡፡
በዚህ የነፃነት በዓል ላይ እንዲገኙ ከተጋበዙ የአገር ውስጥ ጋዜጠኛች ጋር ውይይት ያደረጉት የአገሪቱ ገዢ ፓርቲ ሊቀመንበር ሙሴ ቢሂ አብዲ፣ ሶማሌላንድ እንደ ነፃና ራሷን የቻለች መንግሥት እንዳትታወቅ ካደረጓት መካከል ጎረቤቶቿ ዋነኞቹ ናቸው ብለው፣ ‹‹በተለይም ኢ ትዮጵያ ሲሉ›› ወቀሳቸውን ሰንዝረዋል፡፡ ኢትዮጵያን በዋነኘነት ያነሱበትን ምክንያት፣ ‹‹የአካባቢው ታላቅ ወንድም (Big Brother) ኢትዮጵያ ናት፡፡ በመቀጠል ኬንያ፣ ከዚያ ጂቡቲ ናቸው፤›› የሚሉት ሊቀመንበሩ፣ ሶማሌላንድ ዕውቅና እንድታገኝ ከፍተኛ ሚና መጫወት የነበረባት ቢሆንም፣ የተለያዩ ምክንያቶችን በመሰንዘር ሶማሌላንድን ከማገዝ መሸሿን ተናግረዋል፡፡
ኢትዮጵያ እንደ አካባቢው ኃያልነቷ ማድረግ የሚገባትን ላለማድረጓ ከምትሰጣቸው ምክንያቶች መካከል፣ በኢትዮጵያና በሶማሊያ መካከል ያለው የቆየ ጠላትነት አንዱ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
ኢትዮጵያ ለሶማሌላንድ ከምትገልጻቸው ምክንያቶች መካከል ሌላኛው ደግሞ፣ የአፍሪካ ኅብረት ዋና ጽሕፈት ቤት በአዲስ አበባ መገኘቱን ነው፡፡ ‹‹ኢትዮጵያ እንደ አፍሪካ ኅብረት መቀመጫነቷ በአፍሪካ ጉዳዮች ገለልተኛ መሆን አለባት፤›› የሚል መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
በኬንያና በጂቡቲ በኩልም ምክንያቶቹ ተመሳሳይ መሆናቸውን የሚናገሩት ሊቀመንበሩ፣ ‹‹ለሶማሌላንድ ዕውቅና በመስጠት የመጀመርያ አገር መሆን አይፈልጉም፤›› ብለዋል፡፡ ሌላኛው በዋነኝነት የሶማሌላንድ የዕውቅና ጉዳይን እያጓተተ የሚገኘው ደግሞ በአዲስ አበባ እምብርት ላይ በቻይናውያን የተገነባው ትልቁ ሕንፃ ነው ብለዋል፡፡
‹‹በዚህ ትልቅ ሕንፃ ውስጥ የአፍሪካ መሪዎች በየዓመቱ ቢገናኙም፣ በኅብረቱ ቻርተር መሠረት ያቀረብነውን ጥያቄ ወዴትም ፈቅ አላደረጉትም፤›› ሲሉ ወቅሰዋል፡፡
ከአፍሪካ ኅብረትና ከሶማሌላንድ ጎረቤት አገሮች ይልቅ አሜሪካና የአውሮፓ ኅብረት የሶማሌላንድን መገንጠል አይፈልጉም፡፡ በመሆኑም ዋናው ጉዳይ ያለው እነዚህ ኃያላን አገሮች ጋር በመሆኑ፣ የአፍሪካ ኅብረትና ጎረቤት አገሮች የእነዚህን ኃያላን ይሁንታ ካላገኙ ለሶማሌላንድ ዕውቅና ማግኘት ጥረት አያደርጉም የሚል የፖለቲካ ትንተናን መሠረት በማድረግ ለቀረበላቸው ጥያቄ ሲመልሱ፣ ‹‹እኛ አፍሪካውያን ነን ውሳኔዎቻችንን በነፃነት መወሰን ነው ያለብን፤›› ብለዋል፡፡
የአሜሪካና የአውሮፓ ኅብረት ተፅዕኖ ቢኖር እንኳ አፍሪካዊ ውሳኔዎችን በነፃነት መወሰን እንደሚያስፈልግ በመጠቆም እውነቱ ግን ይህ አለመሆኑን የሚናገሩት ሊቀመንበሩ፣ ማንኛውም አፍሪካዊ አገር የመገንጠል ጉዳይን በፍርኃት መራቁ ነው እውነቱ ብለዋል፡፡ ‹‹እንኳን ማንኛውም አፍሪካዊ መንግሥት የመገንጠልን መብት በሕገ መንግሥት የጻፉት ኢትዮጵያውያን የመገንጠል ጉዳይን ይፈሩታል፣ በሩቁ ይሸሹታል፤›› ብለዋል፡፡
በኢትዮጵያ ገዢው ፓርቲ በምርጫ ካሸነፈ ሊቀመንበሩ የአገሪቱ መንግሥት መሪ እንደሚሆነው በሶማሌላንድም ተመሳሳይ ነው፡፡ በመሆኑም በቀጣዩ ዓመት በሥልጣን ላይ ያለው ፓርቲ ዳግም ከተመረጠ ሊቀመንበሩ ሙሴቢሂ የሶማሌላንድ ፕሬዚዳንት ይሆናሉ፡፡ በአገሪቱ ወቅታዊ የፖለቲካ ሁኔታ ገዢው ፓርቲ ዳግም ሥልጣን ላይ እንደሚቆይ በርካታ ፍንጮች ይስተዋላሉ፡፡ በመሆኑም የሊቀመንበሩ ፕሬዚዳንትነት አይቀሬ መሆኑን በርካታ የአገሪቱ መዲና ሃርጌሳ ነዋሪዎች ይናገራሉ፡፡ አብዛኞቹም ‹‹የፕሬዚዳንት ወንበሩን እየጠበቀ ነው፤›› ይሏቸዋል፡፡
በቀጣዩ ምርጫ ቢመረጡ ሊያሳኳቸው ከሚፈልጓቸው የቅድሚያ ጉዳዮች መካከል እንዲናገሩ የተጠየቁት ሊቀመንበሩ፣ የሶማሌላንድ ዕውቅና በዋነኝነት ከጠቀሷቸው ጉዳዮች መካከል ይገኛል፡፡ አገሪቱ ይህንን ዕውቅና ባለማግኘቷ ከዓለም አቀፍ አበዳሪዎች መበደርና መሠረተ ልማቶችን ማሟላት ተስኗታል፡፡
ከ25 ዓመታት በፊት ስድስት ሚሊዮን ዶላር የነበረው ዓመታዊ በጀቷ በአሁኑ ወቅት ከ300 ሚሊዮን ዶላር አልዘለለም፡፡ የአገሪቱ ዋነኛ የገቢ ምንጭ የሆነው የቁም እንስሳት ንግድ ቢሆንም፣ በረሚታንስ (በውጭ አገሮች ከሚገኙ ዜጎቿ የምታገኘው የሐዋላ ገቢ) ደግሞ ሁለተኛውን ድርሻ እንደሚይዝ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ ኢትዮጵያ በቅርቡ የአገሪቱን ወደብ ለመጠቀም ቀደም ሲል የገባችውን ስምምነት ማደሷ፣ በዚህም ሳቢያ የተባበሩት ዓረብ ኤምሬትስ ኩባንያ የሆነው ዱባይ ወርልድ የበርበራ ወደብን ከሶማሌላንድ መንግሥት ጋር በጋራ ባለቤት ለመሆንና ለማስተዳደር ስምምነት ከሁለት ሳምንት በፊት መፈረሙ ደግሞ አዲስ ተስፋን ፈጥሯል፡፡
‹‹ይህንን ስምምነት ለበርካታ ዓመታት ስንጠብቅ ቆይተናል፤›› የሚሉት የበርበራ ወደብ ባለሥልጣን ዋና ሥራ አስኪያጅ አሊ ኡመር መሐመድ ናቸው፡፡
- ዮሐንስ አንበርብር’s blog
- 7271 reads