29 MAY, 2016
BY ውድነህ ዘነበ
 የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የመልሶ ማልማት ፕሮጀክቱን በጥልቀት በመግፋት፣ 360 ሔክታር መሬት ላይ የሠፈሩ ዕድሜ ጠገብ መንደሮችን ሊያነሳ ነው፡፡

አስተዳደሩ የሚያነሳቸው በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ መርካቶ የሚገኙት ጎጃም በረንዳ፣ አውቶብስ ተራና ቁጭራ ሠፈር፣ በአራዳ ክፍለ ከተማ ጣሊያን ሠፈር፣ ገዳም ሠፈርና ሠራተኛ ሠፈር፣ በየካ ክፍለ ከተማ አቧሬና መገናኛ ዳያስፖራ አደባባይ አካባቢ፣ በቂርቆስ ክፍለ ከተማ ገነት ሆቴል አካባቢ የሚገኙ ነባር መንደሮች ናቸው፡፡

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የመሬት ልማትና ከተማ ማደስ ኤጀንሲ ምክትል ሥራ አስኪያጅ አቶ ግርማ ብርሃኑ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ በተያዘው በጀት ዓመት ከነዋሪዎች ጋር ምክክር ከተደረገ በኋላ በሚቀጥለው ዓመት መጀመሪያ ማንሳት ይጀመራል፡፡

በአዲስ አበባ ከተማ በተለይ መካከለኛውን ክፍል በመልሶ ማልማት ፕሮጀክት ማንሳት ከተጀመረ አሥር ዓመታት ቢቆጠሩም፣ አዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ አሜሪካ ግቢን በማንሳት የፕሮጀክቱ አካል ሆኖ ነበር፡፡

ነገር ግን አሁንም ቢሆን አሜሪካ ግቢን ለማንሳት ለከተማው አስተዳደር ትልቅ ተግዳሮት ሆኖ ቀጥሏል፡፡ በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ የሚገኘው የአሜሪካ ግቢን አንድ አካል በመስከረም 2008 ዓ.ም. ማንሳት ተጀምሮ ነበር፡፡ ነገር ግን ከተነሺዎች የሚቀርብ ቅሬታ እየገፋ በመምጣቱ እስካሁን ሙሉ ለሙሉ ማንሳት አልተቻለም፡፡

አቶ ግርማ እንደሚሉት እስከ ሰኔ 30 ቀን 2008 ዓ.ም. መንደሩ ሙሉ ለሙሉ ፈርሶ ማለቅ ያለበት በመሆኑ፣ አስተዳደሩ በተቻለው መጠን ከነዋሪዎች ጋር እየተነጋገረ ቤቶቹን በማፍረስ ላይ ይገኛል፡፡

ይኼም ቢሆን ግን ነዋሪዎች ቅሬታቸውን ማቅረብ አላቆሙም፡፡ የአሜሪካ ግቢ ተነሺዎች ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ የተሰጣቸው ጊዜ አጭር በመሆኑና ወቅቱም የዝናብ  እንደመሆኑ መንግሥት ሊታገሳቸው ይገባል፡፡

አቶ ግርማ በዚህ አይስማሙም፡፡ በቂ ጊዜ፣ ምትክ ቦታ፣ የቤት መሥሪያ ካሳ መሰጠቱን፣ እንዲሁም ለዕቃ ማጓጓዣ ደግሞ 11,000 ብር ተሰጥቷል ይላሉ፡፡ ይህንን ክፍያና ምትክ የተረከበ በሙሉ መነሳት ስላለበት፣ እነዚህን ክፍያዎችና ምትክ ቦታ ያልተሰጠው ነዋሪ ግን እንዲነሳ አለመገደዱንና እንዲነሳ የተገደደ ነዋሪ ካለ ቢሯቸው ክፍት መሆኑን አቶ ግርማ ተናግረዋል፡፡

‹‹ግማሹን አፍርሶ ግማሹን መተው ለፀጥታ ችግር ይዳርጋል፡፡ ክረምት ነው ተብሎ በጋ ከተጠበቀ ልጆች ትምህርት ይጀምራሉ ይባላል፡፡ ይህ ተቀባይነት የለውም፡፡ በአሁኑ ወቅት ማንኛውም ትምህርት ቤት ለልማት ተነሽዎች ቅድሚያ እንዲሰጥ በመወሰኑ የሚነሱ ነዋሪዎች ቅድሚያ ያገኛሉ፤›› በማለት ጉዳዩ ያለበትን ደረጃ አቶ ግርማ አስረድተዋል፡፡

በሚቀጥለው ዓመት የሚነሱት የመርካቶ ሦስት ነባር መንደሮች ብቻ አይደሉም፡፡ በአጠቃላይ በአምስት ክፍላተ ከተሞች 360 ሔክታር መሬት ላይ ያሉ ይዞታዎች በሙሉ ይነሳሉ፡፡

ከእነዚህ መካከል በአራዳ ክፍለ ከተማ የሚገኙት ጣሊያን ሠፈር፣ ሠራተኛ ሠፈርና ገዳም ሠፈር እንዲሁም የተወሰነው የአቧሬ መንደር፣ እንዲሁም ለመጀመሪያ ጊዜ በመልሶ ማልማት ውስጥ የገባው የካ ክፍለ ከተማ አቧሬና መገናኛ አካባቢ የሚገኙ ነባር መንደሮች እንዲነሱ ተወስኗል፡፡

በዚህ ዓመት ከነዋሪዎች ጋር የተለያዩ ውይይቶችና የካሳና የምትክ ቦታ፣ እንዲሁም ተለዋጭ ቤቶች ጉዳይ ላይ ምክክር ተደርጎ፣ በሚቀጥለው ዓመት መጀመሪያ ላይ ወደ ማፍረስ እንደሚገባ አቶ ግርማ አስታውቀዋል፡፡

ምንጭ      –    ኢትዮጵያን ሪፖርተር

Leave a Reply