June 17, 2016

ኖአሚን በጋሻው

(ሎንግ ቢች – ካሊፎርኒያ)
naominbegashaw@gmail.com

ሁለት ራዲዮ ጣቢያዎች አሉ። ከዲሲ የሚተላለፉ። የግንቦት ሰባት አመራር የሆኑትን አቶ ንአመን ዘለቀን አቅርበው አወያይተው ነበር። የነጻነት ራዲዮና የአቶ አበበ በለው አዲስ ድምጽ ራዲዮ። በሁለቱ ራዲዮዎች መካከል ትልቅ ልዩነቶች ይታያሉ። አንደኛው፣ የነፃነት ራዲዮ፣ የወያኔው ፋና ራዲዮ ነው የሚመስለው። የፕሮፖጋንዳ ራዲዮ። ገና አዳምጬ ሳልጨርስ ነው የዘጋሁት። ሁለተኛው የአዲስ ድምጽ ራዲዮ ግን፣ ለሁለት ሰዓት የተላለፈ ቢሆንም ሙሉዉን አደመጥኩት። የተለያዩ አመለካከቶች የተስተናገዱበት ዘመናዊ ራዲዮ ጣቢያ ነው።

በፕሮፖጋንዲስቱ የነጻነት ራዲዮ በተላለፈው ላይ ብዙ ጊዜ አላጠፋም። የአዲስ ድምጽ ራዲዮ ላይ ግን በተላለፈው ላይ አንዳንድ ሐሳብ መጨመር እፈልጋለሁ።

አቶ ንአመን፣ አቶ አበበ ጥያቄዎችን እንኳን እስኪጨርሱ ለመታገስ ትግስት ጎድሏቸው በመሃል ጣልቃ እየገቡ ፣ እየደጋገሙ ያቋርጡ ነበር። ዶናልድ ትራምፕን ነው የመሰሉኝ።

“በምን ምክንያት ነው ግንቦት ሰባት ሻእቢያን በመደገፍ ፔቲሽን ለማስፈረም የሚንቀሳቀሰው ?” የሚል ጥያቄ ነው መጀመሪያ አቶ ንአመን የቀርበላቸው። ሲመልሱም ሶስት ምክንያቶች አስቀምጡ። አንደኛው ምክንያታቸው “በኤርትራ ያለው ግፍ በኢትዮጵያ ካለው አይበለጥም። Double standard ፣ hypocrisy አለ ” የሚል ነበር። “ኮሚሽኑ ፣ ኢትዮጵያ የሰዎች መብት የሚከበርባት አገር ናት ብሎ ቢናገርና እናንተ ያንን ብትቃወሙ እሺ። ግን ስለኢትዮጵያ የተናገረው ነገር የለም። ከኢትዮጵያ ጋር ምን ግንኙነት አለው ?” ብለው ሲጠየቁ አቶ ንአመን መልስ አልነበራቸው። በሻእቢያ ላይ የደረሰው ማበረታቻ ሆኖን፣ “ወያኔዎችም ለፍርድ የሚቀርቡበትን ሁኔታ ለማመቻቸት የበለጠ መስራት አለብን፤ ከኤርትራዉያኖች መማር አለብን” ማለት ሲገባ “ወያኔዎች የሚሰሩት ግፍ ስላልተካተተ የሻእቢያ ግፍ ለምን ይነሳል” ብሎ መንጨርጨር አስፈላጊ አልነበረም።

ሁለተኛው አቶ ንአመን ያቀረቡት ምክንያት በጣም የሚያስቅና የሚያስተዛዝብ ነበር፡፡ “እንዴ …ምን ነካቸው አቶ ንአምን ? “ ብዬ እጆቼን ራሴ ላይ እስካደረግ ድረስ ነበር የደነገጥኩት። “ኮሚሽኑ በኤርትራ ያሉ ጥሩ ነገሮችን ያላገናዘበ ነው። በኤርትራ ማህበረሰባዊ ፍትህ (social justice) አለ። እንደዉም እዚያ ሄጄ ያነጋገርኳቸው ኤርትራዉያን፣ ነጻ ምርጫ ቢደረግ ኢሳያስን ነው የምንመርጠው ነው ያሉኝ” ሲሉ ነበር፣ ሰው በላውን ኢሳያስ አፈወርቂን፣ ሳያፍሩና አይናቸውን በጨው አጥበው እንደ መልአክ ሊያቀርቡልን የሞከሩት።

እነዚህ ሁለት ምክንያቶች ፈር የለቀቁና ዉሃ የማይቋጥሩ፣ ደካማ ምክንያቶች ናቸው። ግንቦት ሰባቶች በሚሊዮኖች ለሚቆጠሩ ኤርትራዊያን ብቻ ሳይሆን ለስብእና ትልቅ ንቀት እንዳላቸው ነው ያሳዩት።

አቶ ንአመን ያቀረቡት ሶስተኛ ምክንያት፣ በኔ አስተሳሰብ ትልቁና ዋና ምክንያታቸው ነው። “ኤርትራ ብቸኛ ደጋፊያችን ናት። ሻእቢያ ተዳከመ ማለት እኛ ተዳከምን ማለት ነው” ሲሉ በትክክል ጭንቀታቸውን ነው ለሕዝብ ይፋ ያደረጉት። በርግጥም ሻእቢያ ከተመታ ፣ ሻእቢያ ከሞተ፣ የግንቦት ሰባት መጨረሻ ነው የሚሆነው። ግንቦት ሰባት እድል ፈንታዉ ሙሉ ለሙሉ ከሻእቢያ ጋር ስላደረገ ባለው አቅሙና ጉልበቱ ሻእቢያ ከመጠበቅ ዉጭ ሌላ አማራጭ አይኖረዉም። ለነርሱ ሻእቢያን መደገፍ የሕልዉና ጉዳይ ነው። ለዚህም ዶር ብርሃኑ ነጋ፣ በዲሲ ባደረጉት ስብስባ፣ ለሻእቢያ ድጋፍ እንዲሰጥ፣ የሰብአዊ መብት ድርጅቶችን የሚቃወም ፊርማ እንዲፈረም፣ ተማጽኖ ያቀረቡት። ለዚህም ነው ግንቦት ሰባት እንደ ድርጅት፣ የወልቃይት ጠገዴ ፣ ለሱዳን የሚሰጠው መሬት የመሳሰሉትን በርካታ ኢትዮጵያዊና አገራዊ ጉዳዮችን ያካተቱ ፔትሽኖችን የማሰባሰብ ሥራ በተሰራበት ወቅት፣ አንዳቸውም ጊዜ “ይሄን ፔቲሽን ፈርሙ “ ብሎ ፣ መግለጫ አውጥቶ የቀሰቀሰበት ሁኔታ ሳይኖር፣ ሻእቢያን ለመደገፍ በአዝማችነት ፔቲሽኖችን እያስፈረመ ያለው። ለዚህም ነው፣ እንደ አቶ ንአምን ያሉ አመራሮች በተለያዩ ሜዲያዎች በመቅረብ (media blitz) ከፍተኛ “ሻእቢያዊ” ቅስቀሳ ማድረግ የተያያዙት።

በነገራችን ላይ የተባበሩት መንግስታት የሰብአዊ መብት አጣሪ ኮሚሽን የኤርትራ መሪዎችን በሰው ዘር ማጥፋት ቢከስም ዉሳኔው የመጨረሻ ዉሳኔ አይደለም። ዉሳኔው 47 አገራት ( ኢትዮጵያን ጨመሮ 12 ከአፍሪካ፣ 8 ከአሜሪካ፣ 13 ከእሲያና 14 ከአዉሮፓ) ባሉበት በተባበሩት መንግስታት የሰብአዊ መብት ጉባዬ ይታያል። ጉባዬዉም የአጣሪ ኮሚሽኑን ሪፖርት ተመልክቶ ዉሳኔ የሚሰጠው ከአንድ ሁለት ሳምንት በኋላ ሲሆን፣ በአለም ዙሪያ ሁሉ ያሉ ኤርትራዉያን ጉብዬው፣ የኮሚሽኑን ዉሳኔ እንዲያፀድቅ ግፊት ለማድረግ፣ በጄኔቫ በሂን 23 ቀን 2016 ዓ.ም ታላቅ ሰላማዊ ሰልፍ ጠርተዋል።

ጉባዬው ዉሳኔውን ካጸደቀ፣ ወደ ተባበሩት መንግስታት የጸጥታው ምክር ቤት ያመራል። የጸጥታው ምክር ቤትም የጉባዬዉን ዉሳኔ በማጽደቅ የአለም ፍርድ ቤት አቶ ኢሳያስን እና ጓዶቻቸዉን ለፍርድ እንዲቀርቡ መመሪያ ይሰጣል። ክሱ በጸጥታው ምክር ቤት የሚወሰን በመሆኑም እነ አቶ ኢሳያስ አፈወርቂን ከነሚሎሶቬች ምድብ ይቀመጣሉ።

በመጨረሻ አንድ ነጥብ ላስቀምጥ። ሻእቢያ ከተባበሩት መንግስታት ጋር በሰብአዊ መብት፣ በፍትህና በሕግ የበላይነት …ዙሪያ የሚነሱ ጥያቄዎችን ለመመለስ ፍቃደኛ ከሆነ፣ ግንቦት ሰባቶችና ሻእቢያ እንደተመኙት፣ የተባበሩት መንግስታት የሰብአዊ መብት ጉብኤ፣ የአጣሪ ኮሚሽኑን ዉሳኔ ሊቀለብሰው ይችላል።
ሻእቢያዎች የሰብአዊ መብት አጣሪ ኮሚሽኑን ለማነጋገርም ሆነ ወደ ኤርትራ ገብቶ ማጣራት እንዲያደርግ ፍቃድ ለመስጠት ከጅምሩ ፍቃደኛ አልነበሩም። ሪፖርቱ ከወጣ በኋላም፣ ኮሚሽኑን መሳደብና ማውገዝ ነበር የመጀመሪያው ስራቸው። ሆኖም ጥቂት ቀናት እንዳለፉ፣ የጉዳዩን አሳሳቢነት በመረዳት ንግግራቸውን እያስተካከሉ የመጡ ይመስላል። በዉጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አቶ ኦስማን ሣሌ በኩል ለተባበሩት መንግስታት የሰብአዊ መብት ጉባዬ በላኩት ደብዳቤ፣ አገራቸው በሰብዓዊ መብት መከበር ዙሪያ ለመወያየት ዝግጁ እንደሆነች ነው የገለጹት። “ I wish to assure the Council that Eritrea shall remain open and committed to constructive engagement to promote and protect human rights and fundamental freedoms and Eritrea will lend its hands to make this body more credible and relevant to all stakeholders.” ነበር ባለስልጣኑ ያሉት። ይሄ በሻእቢያ ታሪክ ተሰምቶ የማያወቅ፣ ሻእቢያ አፍንጫው ተይዞ ፣ ተገዶ የደረሰበት አቋም ነው።

ይሄ ማለት ምን ማለት ነው ? ሻእቢያ ከተባበሩት መንግስታት የሰብአዊ መብት ጉብዬ ጋር አብሮ ለመስራት ከወሰነ፣ እንደፈለገ ሊሆን አይችልም ማለት ነው። በተለይም በተባበሩት መንግስታት፣ በአፍሪካ ሕብረት በመሳሰሉት የማይወደዱና የሚያስነቅፉ ተግባራቱን ማቆም ይኖርበታል።

የጸጥታው ምክር ቤት እንደ ፈረንጆች አቆጣጠር በ2009 ያወጣው ፣ ” ሕግ 1907″ የተባለው፣ በኤርትራና በሶማሊያ ዙሪያ ያስቀመጣቸው ነጥቦች አሉ። አንዱ ኤርትራ በአካባቢዋ ያሉ አገራት መንግስታትን የሚቃወሙ የትጠቅ ትግል የሚያደርጉ ድርጅቶችን መደገፍና መርዳት እንድታቆም የሚጠይቅ ነው። ከዚህም የተነሳ ሻእቢያ፣ ፈልጎ ሳይሆን ተገዶ በኤርትራ ያሉ የትጥቅ ትግል የሚያደረጉ ተቃዋሚዎችን ሊያግድ ይችላል።

በመሆኑም በነ አቶ ኢሳያስ ላይ የተወሰነው ዉሳኔ፣ ተቀለበሰም፣ አልተቀለበሰም፣ ግንቦት ሰባትና ሌሎች አስመራ ያሉ ደርጅቶች፣ አስቸጋሪ ሁኔታ ላይ ነው የወደቁት። በኤርትራ በኩል እናደርገዋለን የሚሉት ትግል መጨረሻም ሊሆን ይችላል። ወይም አቶ ኢሳያስ ለፍርድ ቀርቦ ፣ ግንቦት ሰባቶች ወዳጃችን ያሉትን በማጣት ዜሮ ይገባሉ፤ አሊያም ኢሳያስ ለራሱ ሲል፣ ከአለም አቀፍ ማህበረሰብ ጋር መስማማት ስላለበት ይሽጣቸዋል። በዚህም በዚያ ኤርትራ ያሉ ተቃዋሚዎች ቀለጡ ማለት ነው።

ለዚህም ነው በኢትዮጵያ ለዉጥ ለማምጣት የሚደረገው ትግል፣ በምን አይነት ሁኔታ ከሻእቢያ ጋር መያያዝ የለበትም አይሉ ብዙ ሲከራከሩ የነበሩት። ሻእቢያ ለኢትዮጵያ ህዝብ ደንታ የለውም። በማናቸዉም ጊዜ የኢትዮጵያ ተቃዋሚዎች ከገደል ላይ ለጥቁሙ ሲል የሚፈጠፍጥ ነው። ታማኝነት ብሎ ነገር በታሪኩ አያውቅም።የኢሕዓፓ ወዳጅ ነበር፤ ወዲያው ተገልብጦ ወደ ወያኔ ሄደ። ብዙም ሳይቆይ ደግሞ ከወያኔ ጋር ደመኛ ሆነ። ነገርም ግንቦት ሰባቶች እንደ ቁሻሻ ይወረወራቸዋል።

በተለይም በዳያስፖራ ብዙ ወገኖች ለግንቦት ሰባት ድጋፍ እንዳላቸው ይታወቃል። አብዛኛው የግንቦት ሰባት ደጋፊ ድጋፍ የሚሰጠው በኤርትራ በኩል ያለው ሁኔታ ጥሩ ሁኔታ ላይ እንዳለ ተደረጎ ስለተነገረው ነው። አገሩን ከመዉደዱ፣ ለወያኔ ካለው ጥላቻ የተነሳ ነው።

ሆኖም ሕዝቡ የተነገረው ነገር ዉሸት ነው። የግንቦት ሰባት ንቅናቄ እንኳን አገር ዉስጥ እንቅስቃሴ ሊያደርግ ቀርቶ፣ ከላይ ለመገልጽ እንደሞከርኩት፣ በኤርትራ መኖሩና አለመኖሩ ራሱ በትልቁ አጠያያቂ ነው የሆነው። ምናልባትም ጅማናስቲክ ሰርተው፣ አንድ ምክንያት ፈጥረው፣ “ሰራዊታችን ወደ ኢትዮጵያ ገብቷል። በኤርትራ ያለንን ስራ ጨርሰናል” በሚል በዚያ ያሉ በርካታ ወጣቶችን ትተው ወደ አሜሪካ ኑሯቸው ሊመለሱና በዳያስፖራ ባሉ ከተሞች “የሌለ ነገር አለ፣ ያልተደረገ ነገር ተደረገ” እያሉ ማጭበርበራቸዉን ቢቀጥሉ ብዙ መደነቅ የለብንም።

ብዙዎች እንደሚሉት ኢትዮጵያ ዉስጥ ለዉጥ የሚመጣው በኢትዮጵያዉያን ነው። መመካት እና ማደራጀት የሚያስፈለገው የኢትዮጵያን ህዝብ ነው። እኛዉ ኢትዮጵያዉያን በቂ ነን።

( አቶ አበበ ከአቶ ንአምን ጋር ያደረጉትን ለመስማት 36 ደቂቃ ወደ ፊት ይሂዱ)

Leave a Reply