አርበኞች ግንቦት ሰባት በ”ነፍጠኛነት” (በአማራነት) ሲከሰስ እንዳልሰማ አልፎ የ”ደቡብ ድርጅት” ነው መባሉ ምነው አስቆጣው??

 የሰኔ ወር ለ“አርበኛ” ነአምን ዘለቀና ለጅርጅቱ አርበኞች ግንቦት ሰባት በጣም ፈታኝ ወር ነበር።ምናልባትም ድርጅቱ ከተቋቋመበት ቀን ጀምሮ እዲህ አይነት የፖለቲካ ኪሳራ አጋጥሞት የሚያውቅ አይመስለኝም። ከሁለት አመት በፊት የዋና ፀሐፊው መታገት የጅርጅቱን ዝርክርክነት ከመጠቆም ባለፈ የሞራል እንጅ  የፖለቲካ ኪሳራ አላስከተልም ነበር።እንደውም በብዙሀኑ ኢትዮጵያዊ ዘንድ ቁጭት ፈጥሮ ስለነበር ለጅርጅቱ አወንታዊ ሚና ነበረው  ።  የአሁኑ ክስተት ግን ለየት ያለ ነው። የበላይና ወሳኝ የሚባሉት አመራር ብቃት የተለካበት፣ ግለሰቡ የድርጅቱ ልሳን እንደመሆኑ አመራሩ የሕዝብ መብትና ነፃነት በሚሉት  ፅንሰ ሀሳቦች ላይ የሚከተውን መስመር ለሕዝብ  ይፋ ያደረገበት አጋጣሚ ነው።“እኛ በረሀ የወረድነው፤ እኛን አገር አልባ ያደረገንን ፣ የመላው የኢትዮጵያ ሕዝቦች ተፈጥሮአዊ መብቶች የነጠቀውን ፤ ዘራፊውንና አምባነኑን ህውሃትን ለመታገል ነው”።  እያለ ቱልቱላውን ሲነፋ የነበረው ድርጅት ከኢትዮጵያ ቅኝ ግዛት ነፃ አወጣዎት በሚላትን ሀገርና ሕዝብ ላይ ከህውሃት ተቀራራቢ ወንጀል እየፈፀመ ላለና ድርጊቱም በአለም አቀፍ ማህበረሰብ ዘንድ ተወግዞ ለእርድ እየተዘጋጀ ያለውን ሻብያ መደገፉ ሳያንስ ሌሎቻችንን የምልጃ ፊርም እንድንፈርም መጠየቁ በፖለቲከኛ አገላለፅ እራስን ማጥፋት እንደማለት ይቆጠራልና ግለሰቡም ሆነ ድርጅታቸው ማኖ ነክተዋል።

እንግዲህ ይህ ጉዳዩ “ወደሽ ከተደፋሽ” ሆነና የፊርማ ማሰባሰብ አጀንዳውን ያልተቸ “የማሪያም ጠላት”  የተባለ እስኪመስል ድረስ በጉዳዩ ላይ ብዕሩን ያልቀሰረ ሰዉ ማግኘት ይከብዳል። በውጢቱም የተደናገጠው “አርበኛ” ንአምንም  ለማስተባበልና የማሳመን ስራ ለመስራት ያልተጠቀመው ሚዲያ፣ ያልወተወተው ምክንያት የለም። ስለዚህ በጉዳዩ አስመልክቶ ምንም ያልተነሳ ነገር ባይኖርም እኔም “የማሪያም ጠላት” ላለመባል ብቻ የበኩሌን አንድ ሁለት ነጥቦችን አንስቸ ወደ ዋናው ሀሳብ ልመለስ።

ነአምን ለመከራከሪያነት ካቀረባችው ሀሳቦች አንዱ “የኤርትራው መንግስ የሞራል ልህልና ከህውሃቶች የተሻለ ነው” የሚል ነው ። “የኤርትራ መሪዎች ሌቦች አይደሉም፣ዘራፊዎች አይደሉም” ይላል ደፋሩ ነአምን።ስለዚህ ህውሃትን ያልነካ አለም አቀፍ ማሕበረሰብ ሻብያን ላይ ጫና እየፈጠረ  ያለው “ኢሳያስ (ኤርትራ)  ለምህራባዊያኑ ጫና  የማያጎበድና ሎሌ ስላልሆነ ነው” ብሎ ይከራከራል ።መችም ይህን አሳፋሪ የመከራከሪ ሀሳብ ታጥቆ መድረክ ከመድረክ መራወጡ እጅግ የሚገርም ነው።በቀላሉ የክርክሩ ጭብጥ ሻብያ ለምራባዊያን በመወገን ለምን የአረብ ሀገር አባላት በሆኑ እንደ ሱማሊያ በመሳሰሉ ሀገራት እንደ ወዳጁ ህውሃት ጦር አላዘመተም ነው።እንዴት ነው ጉዳዩ ጎበዝ?? ኤርትራ እኮ ሀገር የሆነችው በአረብ ሀገራት ሙሉ የትጥቅም ፣ የስልጠናና የሎጅስቲክ እርዳታ ነው። በአርቡ አለም እንደ አንድ አባል ሀገር ነው የምትታየው።የአረብ ሊግም ታዛቢ አባል ሀገር ናት። አረብኛን እንደ ብሔራዊ ቋንቋ ያስቀመጠች እጩ አረብ ሀገር። እና እንዴት ተደርጎ ነው?? ለምራቢያኑ ወግና አረቦችን ለመግደል ወታደር የምታዘምተው።ሌላው በአረቦች መካከል ባለው ጦርነት  ሀብቱ ያመዘነውንና ጥሩ ይከፍላል ብላ ለገመተችው ለሰውዲ አረብያ ወግናና ዶላሯን እንደ ህውሃት ዘግና ወታደሮቾን ወደ የመን ልካ እየተዋጋች አይደለም ወይ?? የደሀ ሕዝብ ልጆችን ለባለሀብት ሀገራት እየቸረቸሩ ገንዘብ የሚቀበሉበትን የየራሳቸውን መስመር ከመምረጣቸው ውጪ ምኑ ላይ ነው ልዩነታቸው??

ሌላው ሻብያ ሀገር ውስጥ የሚያደርገውን ዝርፊያ በተመለከተ ኤርትራዊኒያኑ ቢያወሩ ይሻላል። የሻበያ አመራሮች እጅግ አስቀያሚና ኢሰባዊ በሆነና ምናልባትም አረመኔው ህውሃት እንኮ ሲታማበት ያልሰማነው ኩላሊት ንግድ ላይ ተሰማርተዋል የሚለውን ሀሜት ልተወዉና በመላው ኢትዮጵያዊያን ዘንድ የሚታወቀውን ሀሳብ ብቻ እናንሳ።ከ1983 እስከ 1990ዓ.ም. መካከል በነበሩት ወደ ስምንት ለሚጠጉ አመታት የነበረውንና “ኤርትራ የግላችን የኢትዮጵያ ሃብት ደግሞ የጋራችን” በሚል ስሌት ሻዕቢያና ወያኔ የኢትዮጵያን ሕዝብ ጥሬ ሃብት መዓድኗን እና ሃገሪቱ ያፈራችውን የተለያዩ ፋብሪካዎቸ እና ባንኮችን አብረው ተባብረው ሲዘርፉ፣ማሰር የፈለጉትን ሲያስሩ፣ መግደል የፈለጉትን ሲገሉ እንደነበር   መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ የሚያስታውሰው ሀቅ ነው። የተለወጠ ነገር ቢኖር አንደኛው ዘራፊ ሌላውን ዘራፊ አባሮ  መዝረፍና መግደሉን ለብቻው መቆጣጠሩ ብቻ ነው። የኤርትራው መንግስት ሌባ አይደለም ብሎ እንዴት ሕዝብ ፊት በድፍረት ይቆማል?? አንድ እግር ቡና የሌላት ኤርትራ ቡና ወደ ውጪ በመላክ በደረጃ ከኢዮጵያ የቀደመችበት እነዚህ ሌቦች አይደሉም፣ዘራፊዎች አይደሉም በማለት ባህታዊ አድርጎ ሊስልልን የፈለጋቸው ሰዎች እየመሮት በነበረበት ወቅት እኮ ነው። ለማንኛውም በነዚህ ሁለት ሌባዎች መካከል የተፈጠረው ጠብ ምንም እንኮ በርካታ ዜጎቻችንን ያጣንበት ቢሆንም ለሌላው ኢትዮጵያዊ በተለይ ለአማራ ሕዝብ የገዳይ ፣ ያሳሪ ፣የሌባና የዘራፊ ቁጥር እንደ ቀነሰለት ነው የምንወስደው።

ሌላው አስቂኝ ነገር ደግሞ ነአምን ይህንን ግልብ መከራከሪያው አሳማኝ ለማድረግ የተጠቀመበት መንገድ ነው። ደጋግሞ “ይህንን ደግሞ የምለው እኜ ሳልሆን ፕ/ር መስፍን ወልደማሪያም ናቸው”  ይላል። እንደ እግዚያብሔር ቃል መጠቀሙ ነው። ይታያችሁ ይህ ሰው የድርጅቱ የምክር ቤት አባል፣የውጭ የስራ አመራር የዲፕሎማሲና የትብብር ጉዳዮች ሀላፊ ነው። የአንድን ግለሰብ አስተያየት እንደ ወረደ ተቀብሎ እናንተም ተቀበሉ ይለናል ። የሚገርመው ደግሞ በዚህ ቃለመጠይቅ ላይ እናቴ ሙሉ አማራ ናት ፣አባቴ ደግሞ በዛ በኩል አማራ ነው እያለ ሲያወራ በሌላኛው ቃለመጠይቅ ላይ  በምስክርነት የጠራቸውና እንደሚያምናቸው የጠቆመን  ግለሰብ  ከጂኦግራፊ ድግሪያቸው በላይ “አማራ የሚባል ዘር የለም”  በሚለው ግልብ ቲኦሪያቸው እንደሚታወቁ እርስቶታል።

ለማንኛውም ኢሳያስም ሆነ ድርጅቱ ሻብያ የኢትዮጵያዊነትን የኩራት መገለጫ ናቸው የሚለ የ ፕ/ር ሀሳብ በጣም ጅል የሆነ ሀሳብ ነው።ሻብያ ማለት በግብጽ ጀማል አብድል ናስር ኢትዮጵያን ለማጥፋት የተፈጠረውን ጀብሀ የተባለ አክራሪ እስላማዊ ፓርቲ እንዲመታ በንጉሰ ነገስቱ የመረጃና ደህንነት ተቋም ሀሳብ አመንጭነት የተቋቋመ፣ በኋላም የኢትዮጵያ የምንግዜም ጠላት በሆኑት በአረብ ሀራት ተጠልፎ  ክህደት የፈፀመ ድርጅት ነውና የኩራት ሳይሆን የክህደት አዋሪያ ነው። ኢሳያስና ድርጅቱ። “ኤርትራ በጣም ኋላ ቀር በሆነችው ኢትዮጵያ ቅኝ እየተገዛች ነው”  ብሎ ትውልድ ቀርፆ ለ30  አመት የወጋንን፣ በርካታ ንብረታችንን ያወደመ፣ ወደ 100 ሺህ ሕዝባችንን ያረገፈ፣ኢትዮጵያን ከተፈጥሮአዊ የባሕር በሯ እንድትነጠል ያደረገ  ነው ኢሳያስና ድርጅቱ። ምንም አይነት የፈጠራ ድርሳት ብታነቡ ሀቁ ይኸው ነው። ኢትይጵያን አምርሮ የሚጠላና እድሜውን በሙሉ ለዚሁ ስራ ያዋለን ሰው የኢትዮጵያ የሞራል መገለጫ ነው ብሎ አፍን መክፈት ፀያፍ ነው።

ለማንኛውም ይህንን አጀንዳ ኢሳያስን በተሻለ በሚያውቁት  ሰዎችና የትግል አጋሮቹ እንዴት እንደሚገለፅ ፣ ኢሳያስ እንደ ግለሰብም ሆነ ሻብያ እንደ ድርጅት ያለውን አረመኔዊ ባሕሪይ፣ ለኢትዮጵያ እንደ ሀገር ያለውን ጥላቻና ምኞት፣ ለአማራ ሕዝብ በተለይ ደግሞ ያለውን አመለካከት ከመላምት ይልቅ ቀርበው ከሚያውቁት ሰዎች የተሰጠ ምስክርነት ጠቆም ጠቆም ላድርግና ልዝጋ።

የመጀመሪያው  የራሱ ድርጅት ነባር አባል የነበረና “ትልሚ ንዘርኢ ክርዳድ”  በአማርኛው ሲተረጎም ደግሞ  (እቅድ ለአረም እርሻ) በሚል በአቶ ረድኢ መሓሪ   ከተፃፈ  የኢሳያስ አፈወርቂ ማንንትን የሚገልጽ  የትግረኛ መፀሀፍ ላይ የኢትዮጵያ ሰማይ ድህረ ገፅ ባለቤት ዶ/ር ጌታቸው ረዳ ተርጉሞ ያስነበበው ነው ።እንዲህ ይላል፦

“ኢሳያስ ስታሊናዊ ባሕሪ ስለነበረው ነፃነት እና መብት አስገኛለሁ ብሎ ትግሉን በተቀላቀለ ታጋይ ላይ በኢሳያስ የመነፅር ክትትል ውስጥ ነበር። በሰዎች ላይ ቅጣት ሲፈጸም የጭካኔው ብዛት “የጀርመን ናዚዎች ሲደርጉት እንደነበር ሁሉ ሰዎች ዳቦ መጋገርያ፨ፎረኖ ውስጥ  ይጠበሱ ነበር፤ እንደ ዶሮ የፈላ ውሃ በሰውነታቸው ላይ ተደፍቶባቸው ይገሸላለጡ ነበር፤ ሰዎች ከዛፍ ግንድ ጋር ታስረው ወተት በላያቸው ላይ እንዲፈስባቸው ይደረግ ነበር (በትንኝ እና ዝምብ እንዲወረር)።”ይህ ድርጊት በዓይኑ ያላየ ሰው ለማመን የስቸግረው ይሆናል፤ ነገር ግን ተደርጓል።”ሙሉው እዚህ ሊንክ ውስጥ ይገኛል።https://ethiopiansemay.blogspot.it/2012_05_07_archive.html

ይህ እንግዲህ በገዛ ወገኖቹ ላይ የፈፀመው አረመኒያዊ ድርጊት ነው።ይህ ግለሰብ በእጁ የወደቁትን አማራዎች ምን ሊያደርግ እንደሚችል አስቡት። አማራን እጅግ አድርጎ የሚጠላ አረመኔ ሰው ነው ኢሳያስ። ለማንኛውም ህውሃት አማራ ላይ በሚፈፅመው ግፍ ተማራችሁና በነዚህ ግልብ ሰዎች ተታላችሁ እዛ በረሀ ውስጥ ያላችሁ አማራ ወገኖቸ ከዚህ እብድ የአማራ ጠላት የየምታምኑበት እምነት ይታደጋችሁ።

ሁለተኛው ደግሞ የእስከመቼ አዘጋጁ አንዱዓለም ተፈራ “ለፕሬዘዳንት ኢሳያስ አፈወርቅ ምስክር”  በሚል ከጦመረው ጦማር ውስጥ ስለ ኢሳያስ የሰጠው ምስክርነት ነው። አንዱዓለም ተፈራ  ከጀበሀ ተባረው እና የሻብያ አካሄድ አላምራቸው ብሎ የራሳቸውን አዲስ ድርጅት ለመፍጠር የሞከሩትንና በኋላም በሻብያ ዳቦ መጋገሪያ ውስጥ እየተከተቱ የከሰሉትን ወጣቶች የድርጅት ሰነድ እንዲያዘጋጅላቸው በቀረቡት ግዜ ስለ ኢሳያስ ምንነት እንደተረዳ ነው የሚገልፀ። ኢሳያስን እንዲህ ይገልፀዋል ፦

“ኢሳያስ የሰው ደም የሚጠማውና የሚያረካው ሰው ነው። ይህ ሰው የሚከተለው የራሱን ፍላጎት ሊያሟላላት የሚችለውን ሕግ ብቻ ነው። ከዚህ ሰው ጋር ድርድር ወይንም ምንም ዓይነት ስምምነት ማድረግ አይቻልም። የሚሠራው፤ ለሱ አገልጋይ ሆኖ እስከተገኘ ድረስ ብቻ ነው። ለኢትዮጵያዊያን ያለው ጥላቻ፤ ከሥልጣን ጥማቱ በላይ ነው። በትግሉ ዙሪያ ለነበሩት ሕፃናት፤ አውሮፕላን በሰማይ ጽምጿ ሲሰማ፤ ኢትዮጵያ መጣች! እያለ ነበር ወደዛፍ ሥር እንዲከለሉ ያስተማራቸው። ለኢትዮጵያ ያለው ጠላትነት ልክ የለውም። ኢትዮጵያ የኤርትራ አገልጋይ መሆን አለባት የሚል ጽኑ እምነት አለው። ይህ ነው የኔ ምስክርነት።……… ለኢትዮጵያ ያለው ጠንካራ ጥላቻ፤ ጊዜ የማይሽረው፣ ምንም ዓይነት ድርድር የማያረግበው፣ እና በደም ሥሩ የተተከለ ስለሆነ፤ ከዚህ ግለሰብ ጋር የሚደረግ ቃለ መጠየቅም ሆነ ከሱ የሚደመጥ በጎ ንግግር ዋጋ የለውም።”ሙሉው እዚህ ሊንክ ውስጥ ይገኛል። http://www.goolgule.com/personal-testimony-about-isayas-afewerk/

ሶስተኛ ደራሰ መቶ አለቃ ታደለ ቴሌ አልቫኖ የተባሉ የደርግ ወታደር  አዲስ መፀሀፋቸውን አስመልክቶ በSBS ራዲዮ ቀርበው በነበረበት ወቅት ኤርትራ በምርኮ በነበሩበት ግዜ ሻብያ አማራ የሆኑ የደርግ ወታደሮችን እንዴት ይይዝ እንደነበረ ሲገልፁ

“እስረኞችን በማንኛውም ከባድ ስራ ድንጋይ ፍንቀላ፣ መንገድ ስራ የትኛውንም የሻብያ ታጋይ ያልቻለውን ስራ ያሰራሉ። እስከ ምሽቱ ሶስት ሰሀት እንዲሰሩ ይገደዳሉ። ደም ባፍንጫቸው መጥቶ የሚሞቱም ነበሩ። እዛ ቦታ ላይ መብት መጠየቅ ወይንም አልሰራም ማለት በሞት ያስቀጣል። ምርኮኛው እጁ ፈንድቶ እየመገለ በዛው በመገለ እጁ እንዲሰራ ይደረጋል። ኦሮሞዎቹን ሌንጮ እየመጣ እየመለመለና እያስታጠቀ ይወስድ ነበር። ደቡቦችንና ትግሬዎች ከሆኑ ደግሞ ፍቃዳቸው እየተጠየቀ በወያኔ እየመለመሉና እንዲታጠቁ ተደርገው ይሄዳሉ።<<በተለይ ደግሞ የአማራ ብሔረሰብ የሆኑትን ለብቻ ለይተው ድንጋይ ፍንቀላና መንገድ ስራ ያሰሯቸዋል።አማረኛ ተናጋሪ ከሆንክ ለብቻ ያደርጉና እናንተ ናችሁ ለኤርትራ ጦርነት ምክንያት የሆናችሁ ይሎቸዋል።ሁሉም ሰው አማራ ላይ ይበረታል ።አማራ ብሔረሰብ ሲመዘገብ አማራ ነኝ ብሎ ስለሚመዘገብ አማራ የሚባለው ዘር ፋይል ለብቻ አለው። ፋይሉን ለብቻ አውጥተው ነበር የሚጠቀሙበት። በአማራ ላይ ያላቸው ጥላቻ እጅግ በጣም የከረረ ፣አንድ ቃል በመናገሩ አንድ ጥይት የሚሰጡበት ሁኔታ ነው የነበረው”>>።ሙሉው እዚህ ሊንክ ውስጥ ይገኛል።  http://www.ethiofreedom.com/a-must-listen-interview-with-tadesse-tele-salvano-sbs-radioo/

*****************************

ወደ ተነሳሁበት ዋናው ሀሳቤ ልመለስ።አርበኞች ግንቦት ሰባት በነፍጠኛነት (በአማራነት) ሲከሰስ የተቃውሞ ድምፅ አሰምቶ እንደማያውቅ  ሁሉም የሚገነዘበው ነገር ይመስለኛል።  መችም ድርጅተ ከተቋቋመበት ቀን ጀምሮ  በብሔር ፖለቲከኞችም ይሁን ገዢው መንግስ በነፍጠኝነት ወይም በአማራነት ነው ሲታማ የቆየው።የኦሮሞ ፖለቲከኞች አርበኞች ግንቦት ሰባት  በአማራነት ያልከሰሱበት ወቅት የለም ብሎ ደፍሮ መናገር ይቻላል። ኢሳያስ አፈወርቂ ኢሳቶች ኤርትራ ድረስ ሄደው መወድስ ያሰሙለት ሰሞን እነ ጅዋር አርበኞች ግንቦት ሰባትና ኢሳትን የአማራ ድርጅት አድርገው አቦራ ሲያጨሱ ነበር።ጀዋር መሐመድ በዛን ወቅት facebook  ገፁ ላይ እንዲህ ነበር ያለው።  “When it comes to dealing with the right wing Amhara political camp, you have to give it to isaias afewerki . … The man who one was once portrayed as devil in Amhara political consciousness is now being re- branded as a messiah. He has effectively exploited their political desperation to force them not only acknowledge Eritrea’s sovereignty but also drop the single legitimate political agenda, the right to access and ownership of the Asab port . Febrewary 13, 2015” አርበኞች ግንቦት ሰባት ግን ለዚህ በጣም አሰልቺና ተደጋጋሚ ክስ “ዝቃጮች” ብሎ መሳደቡ ቀርቶ  አግባብ ያለው መልስ ሲሰጥ ተሰምቶ አይታዎቅም። እንደውም  በማስተር ፕላን ስም የኦሮሞን አንድነት በማስጠበቁ ኢደት ዋና አጋር ሲሆን ነው የታዘብነው።

ሀሜቱንና መላምቱን ትተን   ድርጅቱ እኮ በአለማቀፍ  ደረጃ ሳይቀር የሚታዎቀውም የአማራ ድርጅት ተብሎ ነው። ይህንን ጉዳይ በአንድ ወቅት መጥቀሴን አስታውሳለሁ።  የተባበሩት መንግስታት የሴኩሪቲ ካውንስል እኤእ 2014 ባወጣው እሪፖርት ግንቦት ሰባትን የሚያስቀምጠው እንዲህ ብሎ ነው።  <<78. “Ginbot Sebat is a banned opposition group formed in 2005 by Amhara political elites committed to regime change in Ethiopia through armed struggle.” United Nations Security Council, 13 October 2014, page 30>>. እንግዲህ ልብ በሉ ይህ ሕጋዊ ሰነድ ነው። አርበኞች ግንቦት ሰባት ግን  እንዲህ  በግላጭ በአለም አቀፍ ተቋም ላዛውም በሰነድ ተደግፍ ለመላው አለም ለተሰራጨ  መረጃ  በመግለጫም መልኩም ይሁን በሌላ መልኩ አንዳች ያለው ነገር የለም። ስለዚህ የደቡቦች ነው መባሉ አቦራ ያስነሳው ለምንድን ነው ??  ብሎ መጠየቅ አግባብ ነው።

ለቀጣይ ሙግት እንዲረዳ ሶስት ጥያቄዎችን  ልጠይቅና የኔን ግምት አስቀምጣለሁ።

የመጀመልያው ድርጅቱ በደቡብ ሰዎች እንደሚመራ መረጃ የወጣው ሰሞኑን አይደለም። እኔ እንደግለሰብ የአመራሩን ዝርዝር በማሕበራዊ ሚዲያዎች ተበትኖ ያየሁት ምናልባት ከስድስት ወር በፊት ይመስለኛል።  ስለዚህ ዛሬ ምን ተገኝቶ ነው እንደ አዲስ ማስተጋባትና በአማራነት የተደራጁ ቡድኖችን የወረዱ፣ ህውሃትን መረዳት ያልቻሉ ደደቦች፣ ዝቃጮችና መሰል ስድ ስድቦችን በመጠቀም ለመስደቢያነት ያገለገለው?

ሁለተኛ አቶ ነአምን ጅርጅቱን የሚመሩት ደቡቦች ናቸው ለሚለው ጥያቄ መልስ ሲሰጥ “ጅርጅቱ የህቡዕ ድርጅት እንደመሆኑ ዝርዝሩ ላይ የተጠቀሱት ከአመራሩ አንድ አራተኛ የሚሆኑ ናቸው” ብለውናል። ቅኔዉ አማራዎችም አሉ በህቡዕ እየተንቀሳቀሱ ነው ለማለት ይመስላል። መችም ኤርትራ ውስጥ ወይንም አውሮፖና አሜሪካ ውስጥ ተሆኖ በሚስጥር መንቀሳቀሱ ፋይዳ የለውምና ሀገር ቤት አማራ የሆኑ የድርጅቱ አመራር አሉ እንደማለት ነው። ይህ ደግሞ ግንቦት ሰባትን በተመለከተ የህውሃት ትኩረት አማራ ወደሆኑ ኢትዮጵያዊያን እንዲያደርግ አማራን ሆን ተብሎ ለማስጠቃት የተሰነዘረ ቃል አመስልም ትላላችሁ??

ሶስተኛው  ከላይ የተባበሩት መንግስታት የሴኩሪቲ ካውንስል ያወጣው መረጃ ላይ  Amhara political elites  በሚለው ቦታ  “political elites from Southern Nations Nationalities region state” በሚል  ቢተካ ኖሮስ ድርጅቱ በቀላሉ ያልፈው ነበር ወይ?? የሚል ነው።

የመጀመሪያውን መልስ ከላይ ያተትኩት ነው።የነፃነት ታጋይ ነኝ የሚል ድርጅት አስተዳድራቸዋለሁ የሚላቸውን ሕዝቦች ነፃነት ጨፍልቆ ፣ ድርጊቱ በአሳማኝ መረጃ ተረጋግጦ በአለም አቀፍ ማሕበረሰብ ዘንድ አይንህን ላፈር ከተባለን አምባገነን ጎን ተሰለፈና ወሳኝ የሆነ የፖለቲካ ስህተት  ሰራ። በዚህም ይደግፉት በነበሩት ወገኖች ሳይቀር ከፍተኛ የሆነ ዉርጅብኝ አስተናገደ። እና ለምን ዛሬ ለሚለው በፖለቲካ የደረሰበትንና እየደረሰበት ያለውን ጫና ለማርገብ ነው። ለዚህ ደግሞ ከህውሃት ባልተናነሰ መልኩ የሚታገሉት አማራ እንዳይሰባሰብና የራሱን ድርጅት እንዳይፈጥር እንደመሆኑ አፈሙዙን አማራን ለማሰባሰብና ለማደራጀት እየሰሩ ወዳሉት ቡድኖች አዞረ። በአንድ ድንጋይ ሁለት ወፍ እንደማለት ነው።

“አማራ አመራሮች አሉን በህቡዕ አገር ቤት እየተንቀሳቀሱ ነው” የሚለው ደግሞ ያው የቋሚ ጠላታችን የሻብያ መርዘኛ አካሄድ ነው። የአማራ አሳር ጥልቀቱንና ስፋቱን ወገኖቻችን አልተረዱትም የምንለው ለዚህ ነው።አገር ቤት በአንድነት ስም በተቋቋሙ የፖለቲካ ፖርቲዎች ውስጥ ሲንቀሳቀሱ የነበሩ የአማራ ወጣቶች ግንቦት ሰባት ናችሁ  ተብለው እድሜ ልክ ተፈርዶባቸዋል። ስርሀቱን በማገልገል ላይ የነበሩ አማራ መኮንኖች ሳይቀር ግንቦት ሰባት ናችሁ ተብለው “አማራ ሽንታም ነው”  ተብለው እየተሰደቡ አይናቸው እስኪጠፍ ተደብድበው ዛሬም እስር ቤቱን እንዳጨናነቁ ነው።የሀገር ውስጥ ግፉ ከአቅማቸው በላይ የሆነባቸውና የነዚህን ከንቱ ፖለቲከኞች ስብከት ሰምተው ኤርትራን በረሀ የገቡ ደግሞ በጦርነቱ ሰሀት ከፊት ሆነው ፈንጅ ይጠርጋሉ፣  በሰላም ወቅት ደግሞ አቅምና ችሎታቸው እተመዘነ ልቀው የተገኙትና ምናልባት ነገ ችግር ሊፈጥሩ ይችላሉ ተብለው በነ ኮረኔል ፍፁም የተጠረጠሩ እንዲወገዱና ደመ ከልብ እንዲሆኑ ይደረጋል።

የሶስተኛው ነጥብ መልሱን ነአምን እንዴት ተደርጎ ብሎ መልሶልናልእና ብዙም ምርምር የሚያስፈልገው አይሆንም። እልቅ መመርመር ያለበት ጉዳይ  ይህ ድርጅት በአንድ በሆነ ምክንያት በአማራነት እንዲታማ ፈልጓል ማለት ነው።  ስለዚህ  ከላይ ባሉ ሁለት መልሶች ላይ እንደጠቋቆምኩት የአማራ መሰባሰብና መደራጀት የሚያስፈራው፣  በወሰደው የተሳሳተ አቋም የጎበጠ ፖለቲካውን በአማራ መሰዋትነት ሊጠግን የሚቃጣው ድርጅት ፣ አማራ ጠል በሆነ ጎረቤት አገር መሽጌአለሁ የሚል ድረጅት፣ በመመሪያ ደረጃ አመራሩን ከአማራነት ውጭ አድርጎ የሚንቀሳቀስ ድርጅት (እዚህጋ ግልፅ ለማረግ በአርበኞች ግንቦት ሰባት ድርጅት ውስጥ የምክር ቤት እጩ ለመሆን ከአማርኛ ቋንቋ በተጨማሪ ሌላ ቋንቋ መናገርን ደንባቸው በግዴታነት ያስቀምጣል)  ፣ልሳኑ በሆነው ኢሳት  የአማራን እንደ ዘር የመኖርና ያለመኖርን ሀሳብ የሚሞግት ድርጅት፣ በአጠቃላይ አማራን መሰዋት አድርጌ ኢትዮጵያን አድናለሁ፣ አማራን እንደ እርካብ እረግጬ ስልጣን እጨብጣለሁ ብሎ የተነሳ ድርጅት  የአለም ማሕበረሰብ የአማራ ድርጅት አድርጎ እንዲያስበው ለምን ፈቀደ??  ለምን ደቡብስ መባሉ እንዲህ አንገበገበው??

አርበኞች ግንቦት ሰባት በአማራ ድርጅትነት መታማቱን የወደደውና ተቃውሞ ሳያሰማ የዘለቀው በደቡቦችም ሆነ በሻቢያዎችም ዘንድ ጠቀሜታው ታምኖበት ነው።በደቡቦቹ ልብ ውስ ያለው ሶስት ነገር ነው። የመጀመሪያው (መችም ሻብያ ፈቅዶ አንድ ቀን ከህዋት ጋር እንዋጋለን የሚል ተስፋው አይጠፋም አይደል) እናም ከህውሃት ጋር ለሚኖረን ትግል የአማራን ይሁንታ ካላገኘን መረብን ሻብያ ቢያሳልፈን እንኮ  ተከዜን መሻገሩ የማይሞከር ነው የሚል ስሌት ነው።  ከትግራይ ከታለፈ አማራም አይደል ያለው እና የአማራን ወጣት በጓሮ የአንተ ድርጅት ነው እያስባሉ ከአሁኑ ማማለል ካልተቻለ ከጦረኛውን አማራ ተራምዶ እንዲት ይታለፋል በማለት ነው።ህውሃት ከበሮዋን ተሸክሞ መንገድ እየመራ አራት ኪሎ ያደረሰ አማራ ዳግም ተመሳሳይ ስህተት ይሰራል ተብሎ አይጠበቅምና። ሁለተኛው በስርሀቱ በጠላትነት የተፈረጀዉና አሳሩን እያየ ያለው አማራው እንደመሆኑ የአማራ ድርጅት ነው እያል በጓሮ ብናሶራ ግልብጥ ብሎ ይቀላቀለናል የሚል ነው። በቀላል አማርኛ የታጋይ ቅጥር ማስታወቂያ መሆኖ ነው።መቸም በኦሮሚያ ፍቅር እየነደደ ያለው የዘመኑ የኦሮሞ ወጣት በአለቆቹ በነፍጠኛነት ስሙ የሚብጠለጠለውን የ”ድሮ ስርሀት ናፋቂ” ለሆነ ድርጅት ትርፍ ነፍስ ቢኖረውም እንኮን ያዋጣል ተብሎ አይታሰብም።ሶስተኛው የዲያስፖራውን የገንዘብም የሞራልም ድጋፍ ላለማጣት ነው። በአለም እንደ ባሕር አሸዋ ተበትኖ የሚባዝነው የአማራ ዲያስፖራ የአማራ ድርጅት ነው ወያኔን ልናራውጠው ነው ካልነው ወደደሀ ቤተሰቦቹ ከሚልከው ፍራንክ እየገመሰ ይወረውርልናል በማለት።

የዚህ ሀሳብ ሁለተኛው ባለድርሻ ሻብያ ነው።  በመሰሪው ኢሳያስ የሚጠነሰስና የኤርትራን ዘላቂ ጥቅም ለማስጠበቅ የሚሰራ ደባ። ሻብያዎች የኢትዮጵያን ጥንካሬና አንድነት ሁሌኔም የሚያስተሳስሩት ከአማራ ሕዝብ ጋር ነው። በኢትዮጵያ ታሪክ እንደሚታወቀው አማራ ጠንክሮ በወጣ ቁጥር በደከመበት ሰሀሳ የተነጠቁ የአባቶቹን እርስት ሲያስመልስና ግዛቱን ሲያስፋፋ ነው። የኦሮሞ ሕዝብን የሚመሩት ፖለቲከኞች  የሻብያ  ፍጥረቶች እንደመሆናቸው ለግዜውም ቢሆን ኦሮሞ ለህውሃት እንጅ ለኤርትራ ችግሯ አይደለም። የኦሮሚያ ፅንሰ ሀሳብ ባብዛኛው የሻብያ ሀሳብ ነው። ስለዚህ ለኤርትራ የአርበኞች ግንቦት ሰባት በአማራ ድርጅትነት መታማት በርካታ ጥቅሞችን የያዘ ነው። አንደኛው ከላይ ጀዋር መሐመድ እንዳስቀመጠው የኤርትራን ሉዋላዊነትና የአሰብ ወደብ ባለቤትነት በአማራ ወጣት ልብ ውስጥ እንዲሰርፅ ያደርጋል።ለምን ቢሉ አንድም ድርጅቱ የአማራ ተደርጎ ስለተፈረጀ የአማራ ትውልዱ በአጠቃላይ ኤርትራን በተመለከም ሆነ  መሪውዋን ኢሳያስ አፈወርቂን በተመለከተ በመሪዎቹ በኢሳት አማካኝነት የሚስተጋባውን አወንታዊ የፕሮፖጋንዳ እየጠጣ እንዲያድግ ይረዳል።አሁን አሁን እኮ  አርበኞች ግንቦት ሰባትና ኢሳት እየፈጠሩት ባለው ጫና ስለ ባሕር በር፣ ስለ አሰብ ወደብ ማውራት የሚያስተች እንደ ድርቁርና የፖለቲካ አላዋቂነት ሆኖ እየተቆጠረ ነው። ኢትዮጵያ ለኤርትራ የተፈረደላትን ባድሜንና አካባቢውን በሀይል ይዛለች ብሎ መናገር እንደ ጀግንነትና ወያኔን እንደመታገል ተደርጎ መቆጠር ተጀምሮል። አንድም በፖለቲካ የበሰሉና ከስርሀቱ ጋር ጥርስ የተናከሱ የአማራ ወጣቶች መጠጊያ የሚሆነን የአማራ ድርጅት አገኘን በማለት በፍቃዳቸው ወደ መታረጃቸው ይተማሉ።በዚህም የአማራ ምርጥ ልጆቹን እየተነጠቀ ኢትዮጵያ ጨርሳ እስክትበታተንና ሁኔታዎች ጨርሰው ወደማይመለሱበት ደረጃ እስኪደርሱ ሻብያ ግዜ ይሸምትበታል።አንድም ከላይ ለመጠቆም እንደተሞከረው በነ ነአምን በኩል “አማራ አመራሮች አሉን በዕቡህ እየተንቀሳቀሱ ስለሆነ ነው የማታውቋቸው” አይነት መረጃ ወደ ህውሃት ደህንነት ጆሮ እንዲደርስ በማድረግ ኤርትራ በረሀ መምጣት ያልቻለውን የአማራ ወጣት አራት ኪሎ ባለው ወኪሉ በሰበብ አስባቡ እንዲያሳስር፣ እንዲያስገርፍ እና እንዲያስገድም ሁኔታውን ያቻችለታል።

ስለዚህ አርበኞች ግንቦት ሰባት የደቡቦች ፖርቲ ነው መባሉ ብዙ ነገር ያበላሻልና የነአምን ጨርቁን ጥሎ ማበድ ሊገርመን አይገባም።ጠያቂዎ ሙያዬ ምስክር (ሙሉ ወንድም አገኘሁ) “ያ ሁሉ አርበኛ ጉራጌ፣ከምባታና ሀድያ ነው ወይ” ብላ ትጠይቃለች። ይህንን ማን አላት ። ግምባሩ ካሉተ 100 ይሁን 1000 ታጋይ አርበኞት ከ 80%እስከ90% የሚሆኑት አማራዎች መሆናቸውን መች አጣነው።ህውሃት ሰራዊት ውስጥም እኮ አንጋቹ አማራና ኦሮሞ ነው። ጥያቄው አመራሩን፣ ፀሀይና ብርድ የማያገኘውን፣አውሮፖና አሜሪካ እየዞረ አሸሸ ገዳሜ የሚለውን ፣”ዝቃጭ”፣ “ ደደብ” ፣ “ውራጅ” እያለ የሚዘልፈንን እኮ ነው። ይሄ ደግሞ እንደፈለጉ ቢያነሱና ቢጥሉት የደቡቦች መሆኑማ ፀሀይ የሞቀውና አገር ያወቀው ጉዳይ ነው።አቶ ነአምን እንደ ግለሰብ አማራነቱ እንደሚያመዝን ነግሮናል።ያለውን ሙሉ ለሙሉ ተቀብለን እንመነው። ይህ ማለት ግን የድርጅቱን አገልጋይነት አይለውጠውም። በነ ኮረኔል ፍፁም በሚመራ ድርጅት ውስጥ የአንድ አማራ መኖርና አለመኖር ትርጉም የለውም።እንኮን እንደ ነአምን በአባቱ ከኦሮሞ የሚወለድና በእድገቱ የአማራ ስነልቦና የሌለው   ጎንደር ገጠር ውስጥ  ተወልዶ ያደገውና  በናቱም በአባቱም አማራ ሆኖ የተፈጠረዉ አብተው ታከለን ‹‹በትግራይ ህዝብ ላይ እየደረሠ ያለው የአማራ ጭቆናን እና ቅኝ አገዛዝን ከዚህ በላይ መሸከም አንችልም›› ብለው ደደቢት ከሸመቁት ትግሬዎች ጋር አብሮ  ወገኖቹን በመውጋት ታሪክ ሰርቷል እኮ።

ሌላው መነሳት ያለበት ነጥብ ድርጅቱ በአማራ ሲታማ አንዳች ቃል ሳይተነፍሱ የባጁት ደጋፊዎቹ ዛሬ በደቡብነት ስሙ ሲነሳ ጉዳዩ ከዘረኝነት ጋር እያያያዙ ሲፈላሰፉ የመደመጣቸው ጉዳይ ነው።። እነዚህ ግልብ ደጋፊዎች ትላንት ህውሃትን አናሳዎችን ከፊት አስቀድሞ ከጀርባ ይዘርፋል ፣  ሀገር ያፈርሳል ብለው ይከሱት የነበረው ሀይለማሪያምንና ብጤዎቹን በመጥቀስ ነው። ዛሬ በሻብያ ተመሳሳይ ስራ ሲሰራ ፍልስፍናቸው መልኩን ይቀይራል። በመሰረቱ ህውሃትና ሻብያ እኮ ከአንድ አይነት ማሕበረሰብ ውስጥ የወጡ ቡድኖች ናቸው።ቋንቋቸው፣አመጋገባቸ፣ ስነልቦናቸው፣ይሉንታ ቢስነቸው፣ መሰሪነታቸው ከአንድ እናት መሀፀን የተፈጠሩ መትያዎች።ሁለት የተለያየ መርዘኛ ጭንቅላት ያላቸው ነገር ግን በአንድ ሳምባ የሚተነፍሱ እርጉም ቡድኖች። የትግል ታሪካቸና የወሰዶቸው አቋሞችም እንዲሁ አንድ አይነት ናቸው።ኢትዮጵያን በተለይ ደግሞ አማራ ሕዝብን ላይ አንድ አይነት ጥላቻ ያለቸው።ኢትዮጵያን  ለማፈራረስ ለአረብ ሀገራ ቅጥረኛ በመሆን ሲታጩ በአንድ ድምፅ ግዳጃቸውን አሜን ብለው የተቀበሉ። የንጉሱ ስርሀት መስረሱን ተከትሎ አጋጣሚውን በመጠቀም ኢቲዮጵያን ለመውረር ከመጣው ከዚያድባሬ ለማበርና ቃታቸውን ኢትዮጵያዊያን ላይ የሳቡ ወራዳ ቡድኖች ናቸው።የነገው ህልማቸውም ተመሳሳይ ነው። ኢትዮጵያን በዘና በቋንቋ አቦድነውና በመሀከላቸው ጥላቻን ተክለው እያጋደሉ ያኛው እንደ ሲንጋፖር የመሆን ህልሙን ሊያሳካ፣ይሄኛው ደግሞ የተቀረውን ሕዝብ ንብረትና ሀብት ዘርፎ የኩታ ገጠም ሀገሮችን ደግሞ እርስታቸውን ቀምቶና ዘራቸውን አጥፍቶ ታላቋን ትግራይ ለመመስረት እንደ ትል ያለ እንቅልፍ የሚተጉ መሰሪዎች ናቸው።

ስለዚህ የትግል ስልታቸውም አንድነው።ህውሃት ሀይለማሪያምንና መሰል ከአናሳ ብሔር የሚወጡ ምሁራንን ከፊት አሰልፎ አይደል እንዴ ያሻውን የሚያደርገው። በራሱ ሀሳብ ሊንቀሳቀስና ውሳኔ ሊያሳልፍ የሚችል አማራ ወይም ኦሮሞ የሆነ ሰው ህውሃት እያለ ወደ ፊት ሊመጣ አይችልም ብለን ስንተነትን አልነበር።ስለዚህ ህውሃት ደቡብን እንሚጠቀም ሻብያ ደብቦችን ይጠቀማል።ይህ ደቡቦች በኢትዮጵያዊነታቸው ላይ ችግር ስላለባቸው አይደለም ።ወይንም ደግሞ እንደ ህውሃቶችና ሻብያዎች መሰሪ ስብዕና ስላላቸውም አይደለም። ለሌሎች ብሔሮች የተለየ ጥላቻም ስላላቸው አይደለም። ጉዳዩ ደቡቦቹ በነዚህ መሰሪ ቡድኖች አገልግሎታቸውን ሲጨርሱ አውልቆ ለመጣልና ቀላል ናቸው ተብለው በመመረጣቸው ብቻ ነው።ስለዚህ ዝም ብላችሁ አትወራጩ ።አርበኞች ግንቦት ሰባት በአመራር ደረጃ የደቡብ ድርጅት ነው።ከዚህ ውጭ እንዲሆን ሻብያ ሊፈቅድ ፈፅሞ አይችልም። አርባ አራት ነጥብ።

ግዜነው ደም መላሽ

አማራነት በልጆቹ ይለመልማል

ምንጭ  ሳተናዉ