September 6, 2016

* በጣም ያሳዝናል   #ጥቁርሳምንት
* የእኔስ ሃገሬ የት ነው ? የት ልሂድ  ?

ካንዱ የሳውዲ ጫፍ ተነስቸ ወደ አንዱ ጫፍ ስጓዝ ሰላም ፣ ደህንነቴ   በአንድዬ የተጠበቀ ቢሆንም በሀገሬና በወገኔ ላይ እየሆነ ያለው ግን ያሳስበኛል ፣  ያመኛል ።   ትናንት በሰሜናዊው የሳውዲ ጫፍ ሆኘ እናቴን ስልክ ደውዬ ሳነጋግራት እንዲህ አለችኝ …  ” ልጄ ከእንግዲህ እናትህ ሞተች ቢሉህ እንዳታለቅስ ፣ ሞት ረክሷል ፣ በዚህ ጊዜ ሞት ለእኔ  ጌጥ ነው ፣ አደራህን ሞተች ብለህ እንዳታለቅስ  ! ” ነበር ያለችኝ  ! እርግጥ ነው ፣ በሀገር ቤት ለለውጥ የተጋ  ወጣቱ  “መብቴ  ይከበር !”  ያለ ጎልማሳውና አዋቂው በአደጋ ተከቦ ነው ያለው ፣ እየሞተም ነው ፣ ዛሬም የእኛ እናቶች እንደቀድሞው በአደጋ ተከበው በሚኖሩ ልጆቻቸው ተሳቀው እየኖሩ ነው !

ማምሻውን የሰማሁት ዘገባ ግን ፣ ከመንገድ ደክሞኝ ላርፍ ብፈልግ አላሳርፍህ አለኝ  ። መረጃውን ያገኘሁት ከአሜሪካ ድምጽ ራዲዮ ነው  ! መረጃው በቂሊንጦ እስር ቤት የደረሰውን ቃጠሎ ተከትሎ የተጨነቁ ቤተሰቦችን በሚመለከት የቀረበ ዘገባ ነው  !  የሰማያዊ ፖርቲ አባል የሆነው የወጣቱ ፖለቲከኛ የዮናታል እናት የወ/ሮ ሙጪት ተካን ቃለ ምልልስ ሰምቸው ውስጤ ታወከ ..  ።

… ዘጠኝ ወር አምጠው የወለዱ ፣ ተቸግረው ያሳደጉ ያስተማሩና ልጃቸውን ለሀገር ወገኑ ባለ ብሩህ ራዕይ ያደረጉ ፣ ለወግ ማዕረግ ያበቁ እናት በመጦሪያቸው ጊዜያቸው ቤታቸው በሀዘን ድባብ አጥልቶበታል … ” ለወገኔና ለህዝቤ መስዋዕት እሆናለሁ  !” ያለ አንድ ወንድ  ልጃቸው ዮናታን ታስሮባቸዋል ፣ ተጨንቀው ተጠበዋል  ! አስቡት  ! ደካማዋ እናት  ከታሰረበት እስር ቤት ስክ ምግብ አብስለው መመላለስ እጣ ፈንታቸው ሆኗል  …ከቀናት በፊት ደግሞ ” ደረሰ ”  በተባለው የእሳት ቃጠሎ ስጋቱ አላስተኛ አላስቀምጥ ብሏቸዋል  !  የልጃቸው ዮናታን መኖር አለመኖር ለማወቅ እየተንገላቱ ነው ። በህዝብ ግፊት መንግሥት ከቀናት በኋላ በሰጠው መረጃ  በቃጠሎ ው የሞቱት ሰዎች ቁጠር ከአንድ ወደ ሃያ ሶስት ከፍ ብሏል፣ ብዙው የሀገሬ ሰው ” በመንግሥት የተነገረው የሟች ተጎጅ ቁጥሩ የተለመደ የማይታመን መረጃ ነው!” በማለት ከእሳት ተረፈው  በባሩድ ያለቁት  የሟች ዜጎች ቁጥር  ከፍ እንደሚል የአይን እማኝ ሳይቀር እየጠቀሱ ምሬት ስጋታቸውን ብሎም ሀገር መንግሥት አልባ ያደረጋቸውን ክፉ የተጎጅ ስሜት በመግለጽ ላይ ናቸው   …  ይህ ሁሉ ሲሆን ወደ 3000 ከሚገመተው ታሳሪ ”  ማን ሞተ ማን ቆሰለ? ”  ለሚለው ለዮናታን እናትና ለቀሩት ተገፊ ታሳሪ ቤተሰቦች ጥያቄ  ”  እዚህ ነው ፣ እንዲህ ሆኗል! ” መልስ የሚሰጥ ሁነኛ ሰው ግን አላገኘም !  ክፉ ቀን ፣ ከረፉ መንግሥት  ። አሳዛኝ ዜጎች  ።

እናቴን ተመስለው ከህሊናዬ አልጠፋ ያሉት የዮናታን እናት ወ/ሮ ሙጪት ተካ በአሜሪካ ሬድዮ ትንታግ ጋዜጠኛ በጽዮን ግርማ ስለፈረሰባቸው እንግልት ተጠይቀው እንዲህ አሉ  ” ልጄ በምን ሁኔታ ውስጥ እንዳለ አላውቅም በእሳት ተቃጥሎ ይሙት ወይም በጥይት ተመቶ ይሙት አላውቅም፣ በየማረሚያ ቤቱ ዞርኩኝ ፣ ሆስፒታልም ሄድኩ ልጄን ግን ማግኘት አልቻልኩም….እኔ ሃገሬ የት ነው ?  የት እንሂድ  ? ለማን አቤት እንበል ? ልጄ የታሰረው ለህዝብ ሲል ነው !  የኢትዮጵያ ህዝብ ይፍረደኝ። የአዲስ አበሻ ህዝብስ ለምን ዝም ብሎ ያያል ?  ”

የእድሜ ባለጸጋዋን የዮናታን እናት እንግልት ሳስበው ዘመኑ አለመቀየሩ አበሳጨኝ ፣ ያኔ መከራውን በሀዘን ሙሾ  ሲተነፍሱት የነበረው እንዲህ ተብሎ ነበር …

መላኩ ተፈራ የእግዜር ታናሽ ወንድም ፣
የዛሬን ተውልኝ  ፣ የነገን አልዎልድም !

አዎጨካኝ በሚባሉት በእነ መላኩ ተፈራ ዘመን  የነበረው የእናቶች መከራ ዛሬም አለ !  ከእነ መላኩ ቅልቦች የከፉ ፣ በእሳት እየለበለቡ በጥይት የሚቆሉ አራዊቶች ዛሬም አሉ  ! …እናት ለልጇ ስጋት ላይ ነው ፣ መንግሥት ፍትህ አላሰፈነም ፣ አድልኦ ተንሰራፍቷል ፣ ዜጋ ያለ ተጨባጭ ወንጄል በፖለቲካ አመለካከቱ ተጠልፎ ይሳደዳል ፣ ከሀገር እንዳይገባ ይሰጋል ፣ በሀገር ስጋት ራዕዩን ደፍሮ የተነፈሰ፣ ይታሰራል ፣ በቁም ይታገታል ፣ ይገረፋል ፣ በድብቅና በአደባባይ ይገደላልም …! ያን መከራ አልፈን ፣ እዚህ ላይ ደርሰናል  ።

በዚህ መካከል መነኩሴዋን የእኔን እናት  አሰብኳት ፣ በስደት የሚደርሰኝ የከበደ ማስፈራሪያና ማስጠንቀቂያ እውነት ሆኖ ታየኝ  … ብዙ ርቄ ሄድኩ በምናብ …እኔ በምለቀው መረጃ ” ጸረ ህዝብና መንግስት አሸባሪ  !” ተብዬ ታስሬ መነኩሴዋ ደካማ እናቴ ለምትወደ ው ልጇ ምግብ ልታቀብል ሔዳ ፣ እስር ቤቱ ተቃጥሎ ፣ ልጇ ያለሁበትን ሳታውቅ ቀናት ስትገፋ ፣  መዳረሻዬ ጠፍቷት ፣ ልጄን ስጡኝ ስትል ፣ በጀብራሬ ቅልብ ወታደሮች ግልምጫ ስታስተናግድ … እንደ ዮናታን እናት የእኔም እናት የምትሆነውን ሳስበው ልቤ በሐዘን ቆሰለ  : (  በእርግጥ ወደራስ አምጥተው ሲያስቡት ደግሞ ጠልቆ ያማል  ።

ማሰሩ ማሰቃዬቱ አንሶ በእሳት እየለበለቡ መግደል ፍጹም ከሰብአዊነት የወጣ ተግባር ነው ። ልብ ይሰብራል ፣ በጣም ያሳዝናል  ! የእኔስ ሃገሬ የት ነው ? የት ልሂድ  ?

በድምጽ ለመደመጥ ይህን ይጫኑ ⇓

“ልጅን ያህል ነገር ያለበትን ሳላውቅ እንዴት ዝም ልበል?” የዮናታን ተስፋዬ እናት (10:56)

አንድዬ በቃችሁ ይበለን  !
#ጥቁርሳምንት
ነቢዩ ሲራክ
ጳግሜ  1 ቀን 2008 ዓም

Leave a Reply