መንግሥት የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ወላጆችን ሊያነጋግር ነው

በአገሪቱ በተለያዩ አካባቢዎች በተፈጠረው ተቃውሞና አለመረጋጋት በርካታ ወላጆች የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችን የመላክ ፍርኃት እንዳደረባቸውና እነዚህ ወላጆች ልጆቻቸውን ወደሚማሩበት ዩኒቨርሲቲ እንዲልኩ መንግሥት እንዴት ሊያሳምን ይችላል የሚል ጥያቄም ለሚኒስትሩ ቀርቦ ነበር፡፡ የኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦች ለልጆቻቸው ደኅንነት ኃላፊነት እንደሚወስዱና መንግሥት ደግሞ ሥርዓት እንደሚያስከብር ወላጆች ማመን እንዳለባቸው በመግለጽ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡

መንግሥት በየዓመቱ የሚያወያየው በውይይት፣ በምክንያትና በሐሳብ ልዩነት የሚያምን የዩኒቨርሲቲ ማኅበረሰብ ለመፍጠር ሲሆን፣ በተለይም ባለፉት ሁለት ዓመታት ውይይቱ ውጤታማ ነበር ብለዋል፡፡ ‹‹ዘንድሮ በሚካሄደው ውይይት ደግሞ ከወላጆች ጋር የሚደረገው ይበልጥ እንደሚሳካ ይታመናል፡፡ ትምህርት ከተጀመረ በኋላም ቢሆን ተማሪዎች የሚያነሷቸው ጥያቄዎች የሚኖሩ ከሆነ ተመሳሳይ መድረክ ለመፍጠር መንግሥት ዝግጁ ነው፤›› ሲሉ አስረድተዋል፡፡

በቀጣዩ ሳምንት የአዳዲስ ተማሪዎች የዩኒቨርሲቲ ምደባ ይፋ የሚደረግ መሆኑን፣ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማትን የሚቀላቀሉ አዳዲስ ተማሪዎችም ሥልጠና ወስደው በመስከረም መጨረሻ በትምህርት ገበታቸው እንዲገኙ እንደሚደረግ ሚኒስትሩ ገልጸዋል፡፡ ነባር ተማሪዎች ደግሞ ከመስከረም 18 ቀን 2009 ዓ.ም. ጀምሮ እንደሚጀምሩ ተገልጿል፡፡

መንግሥት የውይይት አጀንዳ ይሆናሉ ካላቸው መካከል የፌደራሊዝም ሥርዓት አንዱ ነው፡፡ ከዚህ ሥርዓት ጋር በተያያዘ በቅርቡ የወልቃይትና የቅማንት ጥያቄዎች መነሳታቸው፣ ጥያቄዎቹን ተከትሎ ግጭቶች መፈጠራቸው አይዘነጋም፡፡ ይህንና በአጠቃላይ በአገሪቱ በተፈጠረው አለመረጋጋት ምክንያት መንግሥት ጥልቅ ተሃድሶ እንደሚያደርግና የሚያደርጋቸውን ለውጦችም በመስከረም መጨረሻ ለፓርላማ እንደሚያቀርብ መግለጹ ይታወሳል፡፡

Source       –       Ethiopian Reporter

 

Leave a Reply