25 JUNE 2015

የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ አንድነት መድረክ (መድረክ) ግንቦት 16 ቀን 2007 ከተካሄደው አምስተኛውን ዙር ጠቅላላ ምርጫ በኋላ፣ ለሞት የተዳረጉ አባላቱ ቁጥር አራት መድረሱን አስታወቀ፡፡

በዚህም መሠረት ቀደም ሲል መሞታቸው ከተነገረው ሦስት የመድረክ አባላት በተጨማሪ፣ በደቡብ ክልል በሐድያ ዞን ሶሮ ወረዳ በዳና ቶራ ቀበሌ ነዋሪና የመድረክ አባል ድርጅት የሆነው የኢትዮጵያ ማኅበረ ዴሞክራሲ ደቡብ ሕዝቦች አንድነት ፓርቲ (ኢማዴ-ደሕአፓ) መሠረታዊ ኮሚቴ አባል የነበሩት አቶ ብርሃኑ ኤረቦ መገደላቸውን አስታውቋል፡፡

‹‹በ2007 ጠቅላላ ምርጫ በቅስቀሳ ላይ ተሰማርተው ከፍተኛ አስተዋጽኦ ሲያበረክቱ የቆዩት አቶ ብርሃኑ ኤረቦ፣ ሰኔ 11 ቀን 2007 ዓ.ም. ከምሽቱ ሁለት ሰዓት ላይ በመኖሪያ መንደራቸው በተፈጸመባቸው ድብደባ ከተገደሉ በኋላ ወንዝ ውስጥ ተጥለው ተገኝተዋል፤›› ሲሉ የመድረክ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ጥላሁን እንደሻው ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

በሥፍራው ካሉ የፓርቲው አደረጃጀቶች መረጃ እንደሚሰባሰብ የገለጹት አቶ ጥላሁን፣ ‹‹መጀመርያ ቀን ላይ በአካባቢው ያሉ ፖሊሶችንና ሌሎች ካድሬዎችን ያካተተ አካል እየተንቀሳቀሱ፣ ሟችንና ሌሎች ለመድረክ የምርጫ እንቅስቃሴ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያበረከቱ አባላትና ወጣቶችን ‹የማዳበሪያ ሒሳብ እንዳይከፈል ሕዝቡም በመንግሥት ላይ እንዲያምጽ ቅስቀሳ እያደረጋችሁ ነው፤› በማለት ሟችንና ወጣቶችን ለማስፈራራትና ለማሰር ሲንቀሳቀሱ ነበር፤›› በማለት፣ አጋጠመ ያሉትን አስረድተዋል፡፡

‹‹በተለይ ‹ማዳበሪያን በሚመለከት ዕዳው እንዳይከፈል ያደረጋችሁት እናንተ ናችሁ› ተብለው ፖሊስ ሊይዛቸው ሲል ሸሽተው ነበር፤›› ያሉት አቶ ጥላሁን፣ ‹‹ሟች ሸሽቶ ከቆየበት ሥፍራ ምሽት ላይ ወደ ቤቱ በሚያመራበት ወቅት ነው ግድያው የተፈጸመበት፤›› በማለት የፓርቲውን አባል የአሟሟት ሁኔታ አስረድተዋል፡፡

ከጉዳዩ ጋር በተያያዘ በሥፍራው የመድረክ ተወካይና የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ዕጩ ተወዳዳሪ የነበሩት ግለሰብ ስለሁኔታው ለማጣራት ፖሊስ ጣቢያ ቢሄዱም፣ በፖሊስ ጣቢያው የዕለት ሁኔታ መመዝገቢያ ላይ የተመዘገበው ‹‹ሰክሮ ውኃ ውስጥ ወድቆ›› የሚል እንደሆነ መመልከታቸውን፣ አቶ ጥላሁን ከደረሳቸው ሪፖርት ለመረዳት መቻላቸውን ገልጸዋል፡፡

‹‹የምናካሂደው ሰላማዊ ትግል ብዙ መስዋዕነት እንደሚያስከፍለን እናውቃለን፤›› ያሉት አቶ ጥላሁን፣ ‹‹ቢሆንም ግን ሰላማዊውን ትግል አጠናክረን እንቀጥላለን፤›› በማለት አስተያየታቸውን አጠቃለዋል፡፡

ሟች አቶ ብርሃኑ ኤረቦ የ40 ዓመት ጎልማሳና የአምስት ልጆች አባት እንደሆኑ መድረክ ሰሞኑን ባወጣው መግለጫ ላይ አስታውቋል፡፡

መድረክ ከምርጫው ዕለት ጀምሮ በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ ዞን ሚዳ ቀኝ ወረዳ አቶ ጊዲሳ ጨመዳ፣ በምዕራብ  አርሲ ዞን ቆራ ወረዳ አቶ ገቢ ጥቤ፣ እንዲሁም በትግራይ ክልል ምዕራብ ትግራይ ዞን በማይካድራ ከተማ አቶ ታደሰ አብርሃ የተባሉ ዕጩዎቹ መገደላቸውን ቀደም ብሎ ማስታወቁ ይታወሳል፡፡

Leave a Reply