ያልተዘመረላት፣ ያልተነገረላት ጀግና ኢትዮጵያዊት ሴት ናት። እንደሌሎች “እኔ ምን አገባኝ? አርፌ ልቀመጥ” ብላ፣ ባርነትንና ዉርደትን አሜን ብላ ተቀብላ፣ ሕሊናዋን ሸጣ፣ የገዢው ፓርቲ አዉደልዳይ ሆዳም ካድሬና አገልጋይ ሆና፣ በዘረኝንትና በጠባብነት በሽታ ተለክፋ መኖር ትችል ነበር። ግን አላደረገችውም።
ከደቡብ ክልል ከወላይታ ሶዶ ናት። የወያኔ ቡችላው ሃይለማሪያም ደሳለኝ መጣሁበት ካለው። እንደ ሃይለማሪያም ደሳለኝ የሌሎች አሽከር አልሆነችም። እንደ ኃይለማሪያም ደሳለኝ አልተንቦቀቦቀችም። እንደ ኃይለማሪያም ደሳለኝ ሕሊናዋን አልሸጠችም። የወላይታ ጀግና የሆነውን የንጉስ ጦናን ወኔ ተላብሳ፣ ለእዉነት፣ ለፍትህ፣ ለነጻነት፣ ለዲሞክራሲና ለኢትዮጵያ አንድነት ቆመች። የወላይታ ሕዝብበባህሉ፣ በቋንቋም በኢትዮጵያዊነቱ የሚኮራ፣ መብቱ ሲደፈር የማይወድ፣ ታታሪ ሕዝብ ነው። ይች ሴት በትክክል የወላይታ ሕዝብን አቋም አንጸባረቀች። ሕገ መንግስቱ በሚፈቅደው የመደራጀት መብት መሰረት፣ መብቷን ለማስከበር፣ የአንድነት ፓርቲን ተቀላቀለች። የወላይታ ዞን የአንድነት አመራር አባል ሆነች።
የአንድነት ፓርቲ፣ የሚሊዮኖች ድምጽ ለነጻነት በሚል መርህ በወላይታ ዞን ሕዝባዊ ስብሰባ ባደረገበት ወቅት፣ የቅስቀሳ ወረቀቶችን ለሕዝቡ ሳትፈራ ታድል ነበር። ያኔ ገዢዎች አሰሯት። ብዙ ጊዜ በፍርድ ቤት ካንገላቷትና ካሰቃይዋት በኋላ፣ ያለ አንዳች መረጃ፣ በአካባቢ የደህንነት ሃላፊ መመሪያ “አመጽ ቀስቃሽ” ተብላ ተፈረደባት። ወደ ወህኒ ተወረወረች። ያልተዘመረላት የነጻነት ታጋይ ጀግናዋ ሃዲያ ሞሃመድ!!!!
ኢትዮጵያዉያን በየቦታው በአእምሯችን ላለፉት 20 አመታት፣ ወያኔዎች የቀረቀሩትን፣ ስለነርሱ ያለንን የዉሸት ምስል፣ ከአእምሯችን አውጥተን፣ ምንም ጉልበትና አቅም የሌላቸው ደካሞችና የበሰበሱ መሆናቸውን ተገንዝበን፣ እንደ ሃዲያ ሞሃመድ፣ እንደ ርዮት አለሙ፣ እንደ ንግስት ወንዳፍራ፣ እንደ ሜሮን አለማየሁ . . . ብንነሳ የአገራችንን ትንሳኤ እናፋጥነው ነበር። ሰቆቃችን እንዳይራዘም፣ ዉርደታችን እንዳይቀጥል፣ ዛሬ፣ አሁን እንነሳ። ሁላችንም የድርሻችንን ለማበርከት እንዘጋጅ። ነጻነት በጥቂቶች መስዋትነት ብቻ አይገኝም። ለነጻነት ሁሉም የድርሻዉን ይወጣ ዘንድ የግድ ነው!! ትግሉን እንቀላቀል። ከሚሊዮኖች አንዱ እንሁን። (የሚሊዮኖች ድምጽ ፌስቡክ ገጽ)