22 JULY 2015 ተጻፈ በ ታምሩ ጽጌ
በመከላከያ ምስክርነት የተቆጠሩት አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ፣ ዛሬ ፍርድ ቤት እንዲቀርቡ ከትናንት በስቲያ የተሰጠው ትዕዛዝ ተግባራዊ ባለመሆኑ፣ ሦስተኛ ትዕዛዝ ተሰጠ፡፡
በሽብርተኝነት ተጠርጥረው በእስር ላይ በሚገኙት በእነዘመኑ ካሴ (ዘመኑ ካሴ በሌለበት የተከሰሰ ነው) መዝገብ ተጨማሪ መከላከያ ምስክር ሆነው የተቆጠሩትና ፍርድ ቤት በተደጋጋሚ ትዕዛዝ እየጠራቸው የሚገኙት አቶ አንዳርጋቸው፣ ዛሬ ያልቀረቡት በመጥሪያ ስህተት መሆኑ ተገልጿል፡፡ ለምን ዛሬ እንዳልቀረቡ ፍርድ ቤት ሲጠይቅ፣ የማቅረቢያው ትዕዛዝ ከፍርድ ቤት ወጥቶ ለማረሚያ ቤት የተላከ ቢሆንም፣ ‹‹ለአዲስ አበባ ማረሚያ ቤት›› በሚል የተሳሳተ አድራሻ የተላከ በመሆኑ እንደሆነ የማረሚያ ቤቱ ተወካይ አስረድተዋል፡፡ ፍርድ ቤቱም የተላከውን ማዘዣ ሰነድ ግልባጭ ተመልክቶ፣ የተሳሳተ አድራሻ መሆኑን በማረጋገጥ ‹‹ለቃሊቲ ማረሚያ ቤት›› ተብሎ እንዲጻፍ በማስታወቅ፣ ለሐምሌ 29 ቀን 2007 ዓ.ም. እንዲቀርቡ ለሦስተኛ ጊዜ ትዕዛዝ አስተላልፏል፡፡