(በፍሬስብሀት ስዩም ተዘግቦ ቻላቸው ታደሰ ለዋዜማ ሬዲዮ እንዳዘጋጀው)መነሻ አንድ

የኢትዮጵያ ጦር ሃይል በአፍሪካ ከግብፅ ቀጥሎ ሁለተኛው ጠንካራ ሃይል ሲሆን በዓለም ደግሞ 29ኛ ደረጃ ላይ እንደሚገኝ መረጃዎች ያሳያሉ፡፡ የተለያዩ ዓለም አቀፍ ሪፖርቶች እንደሚያሳዩት ከሆነ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ካሉት አምስት ሃያላን ሀገራት አንዷ ነች፡፡ ለዚህ ደረጃ ያበቃት አንዱና ዋኛው አላባ ወታደራዊ ሃይሏ ነው፡፡ ጦር ሰራዊቱ ከአሜሪካ መንግስትም ወታደራዊ እርዳታ ሲቸረው እንደኖረ ይታወቃል፡፡ ለሀገሪቱ በአፍሪካ ቀንድ ልዕለ ሃያል ሀገር (Regional hegemony) መሆን መንግስትና አንዳንድ ታዛቢዎች አስረጂ አድርገው የሚያቀርቡትም ወታደራዊ ሃይሏ ነው፡፡

መንግስትም ሰራዊቱ የሀገሪቱ ሉዓላዊነት ጠባቂ ብቻ ሳይሆን ሀገሪቱ ከውጭ የምታስገባቸውን የውጭ ምርቶች በሀገር ውስጥ በማምረት የቴክኖሎጂ ሽግግር ዋልታ፣ የኢትዮጵያ ትንሳዔ አብሳሪና የኢኮኖሚ ዕድገቱ ምሰሶ መሆኑን ደጋግሞ ይገልፃል፡፡

በኢትዮጵያ ውስጥ እስካሁንም ቢሆን ወታደራዊ-ነክ ጉዳዮች በህዝቡም ሆነ በተቃዋሚዎች ዘንድ በአደባባይ ውይይት የማይደረግባቸው አይነኬ ጉዳዮች በመሆናቸው ህዝቡ በቂ ግንዛቤ የለውም፡፡ የመከላከያ ኢንዱስትሪው ግዙፍ ሃብትና ምርቶች በከፊልም ቢሆን ለህዝቡ ይፋ የሆኑት በከቅርብ ጊዜ ወዲህ በየዓመቱ በሚከበሩት የሰራዊቱ ቀኖች ወቅት በተዘጋጁት ኤግዚብሽኖች አማካኝነት ነው ማለት ይቻላል፡፡ ስለሆነም ከግዙፉ ወታደራዊ ኢንዱስትሪ ጀርባ የሚያንዣብበው ፖለቲካዊ አደጋ ገና በደንብ የተጤነ አይመስልም፡፡ በመከላከያ ሚንስቴር ሚስጢራዊነት ሳቢያም በወታደራዊ ኢንዱስትሪው ባጀት አጠቃቀምም ሆነ የሰራ ሂደቱ ላይ ፓርላማው ያለው ቁጥጥር በጣም አነስተኛ እንደሆነ የሚካድ አይደለም፡፡

ባለፉት ጥቂት ዓመታት መንግስት ለጦር ሰራዊቱ የኢኮኖሚ አቅም መጎልበት የሰጠው ትኩረት በማደጉ በህግ ማዕቀፍ ረገድ የጦር ሰራዊቱ ኢኮኖሚያዊ ይዞታ እንዲፈረጥም የሚያስችሉ ደንቦችንና አዋጆችን በማውጣት በስራ ላይ አውሏል፡፡ ከእነዚህም ውስጥ በመንግስት ልማት ድርጅትነት የተመዘገቡት የመከላከያ ኮንስትራክሽን ኢንተርፕራይዝ፣ የመከላከያ ግንባታ ግብዓቶች ማምረቻ ድርጅት እንዲሁም የብረታ ብረት እና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን ማቋቋሚያ ደንቦች ተጠቃሽ ናቸው፡፡ የሰራዊቱን ሞራልና ኑሮ ለማሻሻል ያስችላል የተባለው የመከላከያ ሰራዊት ፋውንዴሽንም በህግ ተፈቅዶ ሰራ ላይ ውሏል፡፡

በተለይ ከአምስት ዓመት በፊት በ10 ቢሊዮን ብር (ወይም ግማሽ ሚሊዮን ዶላር) መነሻ ካፒታል የተቋቋመው የብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን ከፕራይቬታይዜሽን ኤጀንሲ የተላለፉለትን የልማት ድርጅቶች ጨምሮ የ15 ግዙፍ ኢንዱስትሪዎችና የ100 ፋብሪካዎች ባለቤት ሆኗል፡፡ የተሽከርካሪ መገጣጠሚያና ኢንጂነሪንግ ኢንዱስትሪዎች ብቻ በዓመት ከአንድ ቢሊዮን ዶላር በላይ እንደሚያስገቡ የቅርብ ጊዜ ሪፖርቶች ይጠቅሳሉ፡፡

በአሁኑ ጊዜ የመከላከያ ወታደራዊ ኢንዱስትሪ ያልገባበት ትርፋማ የኢንቨስትመንት ዘርፍ ማግኘት አዳጋች እየሆነ ነው፡፡ በወታደራዊ ፍጆታዎች በኩልም አውቶማቲክ መሳሪያዎች፣ የታንክ መለዋወጫዎች፣ ሞርታርና ላውንቸር የሚያመርት ሲሆን ተዋጊ ሄሊኮፕተሮችንና አውሮፕላኖችንም የመጠገን አቅም አዳብሯል፡፡

የመከላከያ ኢንዱስትሪዎች “ተልዕኳቸውን ለማሳካት በሚያስችሉ ዘርፎች” ሁሉ እንዲሰማሩ መንግስት ስለፈቀደላቸው እምብዛም ገደብ የለባቸውም፡፡ ስለሆነም ድርጅቶቹ ለሲቪል አገልግሎት የሚውል ብረታ ብረት፣ ጀነሬትርና ትራንስፎርመር፣ ከባድ ማሽነሪዎች እንዲሁም የከተማ አውቶብስ፣ የባቡር ፉርጎ፣ ትራክተር፣ ቡል ዶዘርና ተሽከርካሪዎችን የመገጣጠምና ለገበያ ማቅረብም ዋነኛ ስራዎቻቸቸው ሁነዋል፡፡ ከሶስት ዓመት በፊትም መከላከያ ሚንስቴር “የሰራዊት ባንክ” (Army Bank) በማቋቋም ወደ ፋይናንስ ኢንዱስትሪው ለመግባት እያቆበቆበ ስለመሆኑ ለፓርላማው ማሳወቁ ይታወሳል፡፡

መንግስትም አሁንም በርካታ ግዙፍ የግንባታ ፕሮጄክቶችንና ምርት አቅርቦቶችን ያለ ጨረታ ለመከላከያ ተቋማት በኮንትራት እየሰጠ ይገኛል፡፡ የተቋሙ ኢንዱስትሪዎች የታላቁ ህዳሴ ግድብን ኤሌክትሮ ሜካኒካል ስራዎች ከመረከባቸውም በላይ በአምስት ዓመቱ የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ የተያዙትን በርካታ የስኳር ልማትና ማዳበሪያ ፕሮጄከቶችንም እየገነቡ ይገኛሉ፡፡

እዚህ ላይ አሳዛኙ ነገር የሀገሪቱ የግል ዘርፍ ከወታደራዊ ኢንዱስትሪው ጋር ሽርክና የሌለው መሆኑ ነው፡፡ በአንፃሩ የመከላከያው ኢንዱስትሪ ተቋማት ዋነኛ ሸሪኮች መሰል የአሜሪካ፣ አውሮፓና ቻይና ድርጅቶች ብቻ እንደሆኑ መረጃዎች ያሳያሉ፡፡ ኢንዱስትሪዎቹ ከሃያላን ሀገሮች ጦር መሳሪያ አምራች ድርጅቶች ጋር ብቻ ሳይሆን በተባበሩት መንግስታት የጦር መሳሪያ ማዕቅብ ከተጣለባት ሰሜን ኮሪያ ጋር ሳይቀር የስራ ግንኙነት እንዳላቸው ሪፖርቶች ይጠቁማሉ፡፡

ገና በማቆጠቆጥ ላይ ካለው የሀገሪቱ ኢንዱስትሪ አንፃር ሲታይ የሀገሪቱን ኢኮኖሚ በበላይነትና ምናልባትም በብቸኝነት ለመቆጣጠር በመንደርደር ላይ መሆኑን ያሳያል፡፡ በዚህ ላይ የህወሃት ኢንዶውመንቶች ሲታከሉበት በነፃ ገበያ ላይ የተመሰረተው የሀገሪቱ ኢኮኖሚ ከሁለት አቅጣጫ ከባድ አደጋ እንደተደቀነበት ያረጋግጣል፡፡ ስለሆነም የመከላከያ ኢንዱስትሪ ኢምፓዬር በግዙፎቹ የህወሃት ኢንዶውመንቶች ተደቁሰው በመቀጨጭ ላይ ያሉትን የግል ድርጅቶች ጭራሹን ከገበያ እንዳያሳወጣቸው ያሰጋል፡፡ ምናልባት ህወሃት ኢንዶውመንቶቹ ከመከላከያ ኢንዱስትሪዎች ጋር የሚዋሃዱበት ወይም በጋራ የሚሰሩበትን ዕድል ያመቻች ይሆናል እንጂ የመከላከያ ኢንዱስትሪዎች ወደፊት ከኢንዶውመንቶች ጋርም ፉክክር ውስጥ ሊገቡ ይችላሉ፡፡

ሁኔታውን በቅርብ የሚከታተሉ ታዛቢዎች እንደሚሉት የጦር ሰራዊቱ ኢኮኖሚያዊ ጡንቻ መፈርጠም በሀገሪቱ ፖለቲካ ላይ ቁልፍ ሚና እንዲኖረው መገፋፋታቸው አይቀሬ ይሆናል ይላሉ፡፡ እንዲያውም የአንዳንድ ታዛቢዎች ስጋት በጦር ሰራዊቱ የሚቀነባበር ወታደራዊ መፈንቅለ መንግስትንም የሚጨምር ሁኗል፡፡

አሁን ዋናው ጥያቄ ይህ የወታደራዊ ኢኮኖሚያዊ ጡንቻ መፈርጠም ምን ዓይነት ፖለቲካዊና ወታደራዊ ውጤት ያስከትላል? የሚለው ይሆናል፡፡ በሀገሪቱ ውስጥ ሁለት ተፎካካሪ የስልጣን ማዕከሎች (contending power centers) ይፈጠሩ ይሆን? እውነት አንዳንድ ታዛቢዎች እንደሚሰጉት ሁኔታው አንፃራዊ ነፃነት በመጎናፀፍ ላይ ያለው የጦር ሰራዊቱ አመራር ለሲቪሉ መንግስት ያለው ተጠያቂነት ላልቶ ጦር ሰራዊቱ ራሱ የፖለቲካ ተዋናይ እንዲሆንና ስልጣን እንዲይዝ ያደርገው ይሆን? የሚሉትን ጥያቄዎች መፈተሽ ተገቢ ነው፡፡

ኢትዮጵያን የእጅ መዳፋቸውን ያህል ያውቋታል የሚባልላቸው ታዋቂው አሜሪካዊ ምሁር ሬኒ ሌፎርት አምና ባስነበቡት አንድ መጣጥፍ “የፀጥታ ሃይሎችና ጦር ሰራዊቱ በመንግስት ውስጥ ያለ ሌላ መንግስት (a state within a state)” ሁነዋል እስከማለት ደርሰዋል፡፡ ተጠሪነታቸውም ለሲቪሉ መንግስት ሳይሆን ለራሳቸውና ለተወሰኑ የህወሃት አመራሮች ብቻ መሆኑንም በመጠቆም፡፡ “በኢትዮጵያ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ፖለቲካ በጠመንጃ ላይ የነበረውን የበላይነት አጥቷል” ሲሉ መደምደማቸውም የሀገራችን ሁኔታ ምን ያህል አሳሳቢ ደረጃ ላይ መድረሱን ይጠቁማል፡፡

የምሁሩ ከባድ ድምዳሜዎች ሀገሪቱ ለወታደራዊ አገዛዝ ወይም መፈንቅለ መንግስት የተመቻቸ ሁኔታ ላይ እንደሆነች የሚያረጋግጡ ናቸው፡፡ በአንፃሩ ግን በህገ-መንግስቱ መሰረት ጠቅላይ ሚንስትሩ የጦር ሃይሎች ጠቅላይ አዛዥ መሆናቸውን ለሚያውቀው ተራው የኢትዮጰያ ህዝብ አስደንጋጭ መርዶ መሆናቸው እሙን ነው፡፡
በእርግጥ እስካሁን ያለው ሁኔታ ምሁሩ ሬኒ ሌፎርት የገለጡትን ያህል ስለመሆኑ ሊያጠራጥር ይችል ይሆናል፡፡ ሆኖም ሁኔታዎች በዚሁ ከቀጠሉ ዜጎች አንድ ቀን ከእንቅልፋቸው ሲነቁ ሀገራቸውን በይፋዊ ወታደራዊ መዳፍ ስር ላለማግኘታቸው ዋስትና የለም፡፡ እንደሚታወቀው በአፍሪካ የግዙፍ ወታደራዊና ሲቪል ኢንዱስትሪዎች ባለቤት በመሆን ረገድ ዋነኛ ተጠቃሽ የሆነው የግብፅ ጦር ሰራዊት የዕለት ተለት ምግብ ፍጆታ የሆነውን ዳቦ የሚያመርቱ ፋብሪካዎች ሳይቀር ባለቤት መሆኑ ምን ያህል ዋነኛ የፖለቲካ ተዋናይ እንዳደረገው ባለፉት አራት ዓመታት በገሃድ እየታየ ነው፡፡

የኢትዮጵያ ጦር ሃይል በፖለቲካው ላይ ስለሚኖረው ሚና ሶስት ዋና ዋና የ“ቢሆን መላ ምቶች”ን (possible scenarios) ማስቀመጥ ይቻላል፡፡

አንደኛው መላ ምት ሲቪሉ መንግስት ህገ መንግስቱን በመጣስ ጦር ሰራዊቱ የሀገር ውስጥ ፖለቲካው የጀርባ አጥንት እንዲሆን ሁኔታዎችን ሊያመቻች ይችላል የሚለው ነው፡፡ ሰራዊቱም የቢዘነስ ኢምፓዬር እንዲገነባ የፈቀደለት የፖለቲካ ስርዓት በማናቸውም መልኩ እንዲቀጥል ጥብቅና በመቆም የሁለትዮሽ እከክልኝ ልከክልህ አሰራር እንዲሰፍን ሊያደርግ ይችላል፡፡ በሌላ አነጋገር ሲቪሉ መንግስት ሲቪላዊ ማንነቱንና አደረጃጀቱን ይዞ እንዲቀጥል ለማስቻል ጦር ሰራዊቱ ሃይል እስከመጠቀም ሊደርስ ይችላል፡፡ ወይም መፈንቅለ መንግስትን እንደ ማስፈራሪያ በመጠቀም በስልጣን ላይ ያለው ስርዓት እንዲቀጥል ተፅዕኖ ያደርጋል፡፡ በግብፅ ከዓመታት በፊት ሆስኒ ሙባረክ በህዝባዊ ተቃውሞና በራሱ በጦር ሰራዊቱ የመጨረሻ ሰዓት ግፊት ከስልጣን እስኪወርዱ ድረስ ጦር ሃይሉ ምንጊዜም የሲቪሉ መንግስት ጠበቃ እንደነበር አይዘነጋም፡፡

ከጅምሩም የሀገራችን ጦር ሰራዊት ፖለቲካዊ ገለልተኛነት አስተማማኝ ባይሆንም ሲቪሉ መንግስታዊ አመራር የጦር ሰራዊቱ መኮንኖች በፖለቲካ ውስጥ እንዲገቡ ጥርጊያ መንገዱን ያመቻቸላቸው ግን እኤአ ከ2001 የህወሃት ክፍፍል ጀምሮ ነው እንደነበር ይታወሳል፡፡ ስለሆነም የጦር ሰራዊቱ አመራርና የሲቪሉ ፖለቲካዊ አመራር እጅና ጓንት መሆን ይህን የ“ቢሆን መላ ምት” ከመላ ምትነት አልፎ ወደ ተጨባጭነት የተጠጋ ነው ለማለት ይቻላል፡፡ በእርግጥ እስካሁንም ከሞላ ጎደል በተግባር ሲታይ የኖረው ይህንኑ የሚያጠናክር ነው ማለት ይቻላል፡፡

ሁለተኛው የ“ቢሆን መላ ምት” ደግሞ በሲቪሉ አመራርና ወታደሩ የስልጣን ሽኩቻ ተነስቶ ሰራዊቱ ሲቪሉን መንግስት ሙሉ ለሙሉ ወይም በከፊል ገልብጦ ስልጣን ሊይዝ ይችላል የሚለው ነው፡፡ ልክ ከዓመት በፊት ታይላንድ በፖለቲካዊ ችግር ውስጥ ስትዘፈቅ ጦር ሰራዊቱ እንዳደረገው መፈንቅለ መንግስት ወይም ከዓመት በፊት የግብፅ ጦር ሰራዊት በዴሞክራሲያዊ መንገድ ፕሬዝዳንት ሆነው በተመረጡት የሙስሊም ወንድማማቾቹ ሙሃመድ ሙርሲ ላይ እንዳደረገው መፈንቅለ መንግስት ዓይነት ማለት ሊሆን ይችላል፡፡ ሆኖም ይኸኛው የ“ቢሆን መላ ምት” በኢትዮጵያ ተጨባጭ ሁኔታ በአጭርና መካከለኛ ጊዜ ውስጥ የመሞከሩም ሆነ የመሳካት ዕድሉ እምብዛም ይመስላል፡፡

በሶሰተኛ ደረጃ ሊጠቀስ የሚችለው የ“ቢሆን መላ ምት” ጦር ሰራዊቱ በሲቭሉ መንግስት ጋባዥነት (coup with civilian consent) በብቸኝነት ወይም ከራሱ ከሲቪሉ ጋር ተዳብሎ ስልጣን ሊይዝ ይችላል የሚለው ነው፡፡ በእርግጥም እስካሁን የሚታየው የህወሃት-ኢህአዴግ መራሹ መንግስት ሁኔታ እንደ የመጀመሪያው መላ ምት ሁሉ ይህንንም መላ ምት የሚያጠናክር ይመስላል፡፡ ስለሆነም ከመፈንቅለ መንግስት አንፃር ከታየ ለእውነታ የሚቀርበው ይኸኛው ነው፡፡

በጠቅላላው እንዲህ ዓይነቶቹ ሁኔታዎች እንዲፈጠሩ ገፊ ምክንያቶች ሊሆኑ ከሚችሉት ውስጥ ዋነኛው መጠነ-ሰፊ ሀገራዊ ፖለቲካዊ ቀውስ መከሰት እንደሚሆን ይገመታል፡፡ ለምሳሌ እንደ 1997ቱ ምርጫ-አመጣሽ ቀውስ ዓይነት፡፡ ፖለቲካዊ ቀውስ የሚፈጠረው ደግሞ ኢህአዴግ-መራሹ መንግስት ለሀገሪቱ ፖለቲካዊ ችግሮች ዘላቂ የፖለቲካ መፍትሄ መስጠት ካቻለ ወይም ካፈለገ ይሆናል፡፡ መላ ምቱ ለእውነታ ያለውን ቅርበት የሚያሳየው ደግሞ መንግስት ለሀገሪቱ ችግሮች ፖለቲካዊ መፍትሄ ለመስጠት ያለው ፖለቲካዊ ፍላጎትና ተቋማዊ ብቃት እየተኮላሽ መሄዱ ነው፡፡

ክፍል ሁለት

የሀገራችን ጦር ሰራዊት ለራሱ ፍጆታም ሆነ ለሽያጭ የሚውሉ ዘመናዊ ጦር መሳሪያዎችን ማምረቱ ተገቢና የሚደገፍ ነው፡፡ መቼም ሀገራችን በተስፋፊዋ ሱማሊያ በ1960ዎቹ መጨረሻ በተወረረችበት ጊዜ ከአሜሪካ የተገዛው ጦር መሳሪያ ታግዶ ህልውናችን አደጋ ውስጥ መግባቱ አይረሳም፡፡

በዓለም ዓቀፍ ደረጃ የሚታወቀው ለጦር ሰራዊት የሚመደብ በጀት ከአንድ ሀገር አጠቃላይ ምርት ሁለት ፐርሰንት በላይ እንዳይበልጥ በመሆኑ ጦር ሰራዊቱ የራሱን ወታደራዊ ምርቶች እያመረተ የመንግስትን ባጀት ጠባቂ ባይሆን የሚያስወቅስ ተግባር አይደለም፡፡ በሌሎች ሀገራትም የተለመደ ነው። ሆኖም ዋናው ጥያቄ ወታደራዊ ኢንዲስትሪዎቹ ለሲቪሉ ህዝብ ፍጆታ የሚውሉ ሸቀጦችና አገልግሎቶችን ሳይቀር የሚያቀርቡ ነጋዴዎች መሆናቸው ጦር ሰራዊቱን የጥቅም ግጭት ውስጥ በማስገባት የማይገባው ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ አጀንዳ እንዲኖረው አይገፋፉትም ወይ? የሚለው ነው፡፡ መልሱ ቢያንስ በመርህ ደረጃ “አዎ ይገፋፉታል” ይሆናል፡፡

አሜሪካን ጨምሮ ባደጉት ሀገሮች የግል ፋብሪካዎች ሳይቀሩ ከወታደራዊ ኢንዱስትሪዎች ጋር ሽርክና መስርተው ጦር መሳሪያ እያመረቱ ለጦር ሰራዊቱ እንደሚያቀርቡ ይታወቃል፡፡ በእኛ ሀገር ግን በተቃራኒው ወታደራዊ መሳሪያዎችንም ሆነ ለሲቪሉ ህዝብ ፍጆታ የሚውሉት ሸቀጦችንና አገልግሎቶችን በወታደራዊ ሞኖፖሊ ስር የመጠቅለል አዛማሚያ መታየቱ የኋላ ኋላ እጅግ ከባድ አደጋ ያስከትላል የሚለውን ስጋት የሚጋሩ ብዙ ናቸው። ድርጊቱ ነፃ ገበያን መፃረሩ ብቻ ሳይሆን ጦር ሰራዊቱ በቀጥታ በወገንተኛ ፖለቲካ ውስጥ ያገባኛል እንዲል ያደርገዋልና፡፡ ዴሞክራሲና ህገመንግስታዊነት ባለሰፈነባት ሀገር መሆኑ ደግሞ አደጋውን ያጎላዋል፡፡

ምዕራባዊያን በኢትዮጵያ የዴሞክራሲ ጅማሮ ተሰፋቸው ባይሟጠጥም፤ በህገመንግስቱ መሰረትም የጦር ሃይሉ ሙሉ ታዛዥነት ለሲቪሉ መንግስት ቢሆንም የሀገሪቱ ፖለቲካ አሁንም ለጦር ሰራዊት ጣልቃ ገብነት የተጋለጠ ስለመሆኑ ምሁራን በስፋት የመወያያ አጀንዳ ያደረጉት ከአቶ መለስ ህልፈት ጀምሮ ነው፡፡

በዚህ ረገድ ተጠቃሽ ኢትዮጵያዊ ምሁራን ፕሮፌሰር ተኮላ ሃጎስና የኢትዮጵያን ፖለቲካ በመተንተን የሚታወቁት ፕሮፌሰር መሳይ ከበደ ናቸው፡፡ በተለይ ፕሮፌሰር ተኮላ ለሀገሪቱ ፖለቲካዊ ችግር ብቸኛው መፍትሄ ወታደራዊ መፈንቅለ-መንግስት መሆኑን እስከመጠቆም ደርሰዋል፡፡ እንደ ፕሮፌሰር ተኮላ የመፈንቅለ መንግስት አቀንቃኝ ባይሆኑም ፕሮፌሰር መሳይም በቅርቡ ባስነበቡት አንድ መጣጥፍ “መንግስት አሁን እያደረገ ያለው ነገር በሙሉ መፈንቅለ-መንግስትን የሚጋብዝ ነው” ይላሉ፡፡

ታዋቂውን ምሁር ሬኒ ሌፎርትን ጨምሮ ሌሎችም የቅርብ ታዛቢዎች የጦር ሰራዊቱ አንፃራዊ ነፃነት ስለመጎናፀፉ የሚናገሩት በአቶ መለስ ህልፈት ማግስት የህወሃት የፖለቲካ የበላይነት ቀንሷል ብለው በማመናቸው ነው፡፡ ይህን መካድ ባይቻልም በሌላ በኩል ግን ጦር ሰራዊቱ ራሱ ፖለቲካዊ ሚና ለመጫወት ምን ዓይነት ጥንካሬዎችና ውስንነቶች እንዳሉበት መፈተሽ ያስፈልጋል፡፡

እንደሚታወቀው ማንኛውም ጦር ሰራዊት የፖለቲካ ማህበራዊ መሰረት (social base) ስለሌለው የከባድ ሚዛን ፖለቲካ ተዋናይ ለመሆን ቢያንስ ሶስት መሰረታዊ ነገሮችን ማሟላት ያስፈልገዋል፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ ጦር ሰራዊቱ የኢኮኖሚያዊ ኢምፓዬር ባለቤት መሆን ያስፈልገዋል፡፡ በኢኮኖሚያዊ አቅሙ የተራቆተ ማንኛውም ጦር ሰራዊት ከባድ ሚዛን ፖለቲካዊ ተዋናይ ለመሆን ይቸግረዋል፡፡

በሁለተኛ ደረጃ የካበተ ወታደራዊ ተቋማዊ ልምድና ባህል ያስፈልገዋል፡፡ ልክ እንደ ታይላንድ፣ ግብፅ፣ ናይጀሪይ፣ ቱርክ ወይም በርማ ጦር ሰራዊት ዓይነት፡፡

ሆኖም በዚህ በኩል የኢትዮጵያ ጦር ሰራዊት እዚህ ግባ የሚባል ልምድ የለውም፡፡ ኢህአዴግ በ1983 ዓመተ ምህረት አዲስ አበባን በተቆጣጠረ ማግስት ነባሩን ግዙፍ ጦር ሰራዊት ሙሉ በሙሉ ስለበተነው የአሁኑ ጦር ሰራዊት ከድሮው የወረሰው ተቋማዊ እሴትም ሆነ ፖለቲካዊና ወታደራዊ ልምድ እንደሌለውም ይታወቃል፡፡ መቼም አቶ መለስ ሙሉ ለሙሉ ሊቆጣጠሯቸው የሚችሏቸውን መኮንኖች በአመራር ላይ አስቀምጠው መሄዳቸው እሙን ነው፡፡ በኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ማግስት ጄኔራል ፃድቃን ገብረ ተንሳይን ከጠቅላይ ኤታማዦርነት ያነሱበት ሁኔታም ይህንኑ ያስታውሰናል፡፡

በሶሰተኛ ደረጃ ደግሞ ጠንካራ ሀገራዊና ዓለም ዓቀፋዊ ፖለቲካዊ ንቃተ ህሊና (domestic and regional Geo-political consciousness) ያስፈልገዋል፡፡ የሀገራችን ጦር ሰራዊት አመራር ግን ሀገራዊ፣ አካባቢያዊና ዓለም ዓቀፋዊ ጅኦ-ፖለቲካዊ ፍላጎት ለማራመድ የሚያስችለው ብቃት ያለው ስለመሆኑ መናገር ያዳግታል፡፡ የሀገሪቱ ጦር ሰራዊት በዓለም ዓቀፍ ሰላም ማስከበር ተልዕኮዎች መልካም ዝና ቢኖረውም ይህ ዓለም ዓቀፍ ልምድ ግን የአመራሩን ፖለቲካዊና ወታደራዊ ብቃትና ንቃተ ህሊና ስለማዳበሩም ሆነ በጠቅላላው ጦር ሰራዊት ላይ እሴት ለመጨመር በሚያስችል ደረጃ ተቋማዊ (institutionalized) ስለመደረጉ አስተማማኝ ማስረጃ ማየት አልተቻለም፡፡

በአራተኛ ደረጃ ጠንካራ ተቋማዊ አንድነት (institutional cohesion)፣ ዴሞክራሲያዊ ህገመንግስትን መሰረት ያደረገ ወታደራዊ ኢንዶክትሪኔሽን (military indoctrination) ሊኖረው ይገባል፡፡ ሆኖም የሀገራችን ጦር ሰራዊት ተቋማዊ አንድነቱን የሚጎዱ በሰራዊት ምልመላ፣ በማዕረግ ዕድገት አሰጣጥ፣ በአመራሩ ተዋፅኦ፣ ጥራትና ብቃት ዙሪያ የሚታዩ ድክመቶች እንዳሉበት በተደጋጋሚ ሲነሳ ይደመጣል፡፡ የተጠቃኘበት ኢንዶክትሪኔሽንስ ሰራዊቱን ለህገመንግስቱ ብቻ ወገንተኛ እንዲሆን የሚያበቃው ነው? ወይንስ ስልጣን ላይ ያለውን መንግስት የሚያስጠብቅ ነው? የሚለው አጠራጣሪ ሆኖ ቀጥሏል፡፡ በነገራችን ላይ አቶ መለስ በህወሃት ክፍፍል ወቅት የጦር ሰራዊቱ ከፍተኛ መኮንኖች በፓርቲው ግምገማ እንዲሳተፉ ማድረጋቸው ምን ያህል አደገኛ እንደሆነ ማስታወስ ያስፈልጋል፡፡
ወታደራዊ ኢንዱስትሪዎቹ ግዙፍ ሃብት እያካበቱ ቢሆንም የጠቅላላው ወታደር ኑሮ ስለመሻሻሉ ግን ምንም የሚታይ ነገር የለም፡፡ ይህ ደግሞ ውሎ አድሮ በአመራሩና በተራው ወታደር መካከል ቅራኔ መፍጠሩ አይቀሬ ነው፡፡ ከዓመታት በፊት ከዓለም ዓቀፍ ሰላም ማስጠበቅ ተልዕኮ የተመለሱ ወታደሮች ተገቢው ክፍያ አልተፈፀመልንም ብለው ለአጭር ጊዜም ቢሆን ማመፃቸው ይህንኑ ስጋት ያጠናክራል፡፡ በተለይ ቅራኔዎች ብሄረሰባዊ ይዘት ከያዙ የሰራዊቱን መፈረካከስም ሊያስከትሉ ይችላሉ፡፡

በእርግጥ ጦር ሰራዊቱ የተመሰረተበት ወታደራዊ ፍልስፍና “ተከላካይነት” (defensive) እንደሆነ ይነገራል፡፡ ሀኖም ከኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ወዲህ “የአጥቂነት” (aggressive) ባህሪ መላበስ ጀምሯል፡፡ በሱማሊያ የሚያደርገው ድንበር-ዘለል የአጥቂነት ዘመቻም በሀገሪቱ ታሪክ የመጀመሪያ ነው፡፡ በሉዓላዊቷ ኤርትራ ላይ መንግስት የሚከተለው ፖሊሲም በሃይል የመንግስት ለውጥ (regime change) ማምጣትን የሚጨምር እንደሆነ ይታወቃል፡፡ ይህ ደግሞ የሚተገበረው በጦር ሃይሉ ነው፡፡

እንግዲህ ጦር ሰራዊቱ ይህን በመሰሉ ውስጣዊ ሁኔታዎች ውስጥ ይገኛል፡፡ በአንፃሩ ደግሞ ጦር ሰራዊቱን ወደ ፖለቲካ ጎትተው ሊያስገቡት የሚችሉ ሶስት ውጫዊ ምክንያቶችን መጥቀስ ይቻላል፡፡ አንደኛ መጠነ-ሰፊ ሀገራዊ ፖለቲካዊ ቀውስ፣ ሁለተኛ በኢህአዴግ ውስጥ የሚፈጠር ድርጅታዊ ቀውስ እና በሶስተኛ ደረጃም በኢትዮጵያና ኤርትራ መካከል በድጋሚ የሚቀሰቀስ ጦርነትን ማንሳት ይቻላል፡፡

በድርጅት ደረጃ ሲታይ አቶ መለስ እንዳሰቡት ኢህአዴግን ውህድ ፓርቲ ሳያደርጉት በመቅረታቸው ድርጅቱ ለውስጣዊና ዉጫዊ ቀውስ እንደተጋለጠ እሙን ነው፡፡ ድርጅቱ በባህሪው ውስጠ-ዴሞከራሲ ስለሌለውና በአወቃቀሩም የብሄር-ተኮር ድርጅቶች ግንባር በመሆኑ በተለይም ደግሞ የድርጅቱ የጡት አባት አቶ መለስ በሌሉበት ሁኔታ ራሱን ለማደስና የፖሊሲ ማሻሻያ ለማድረግ ያለው ዕድል የተሟጠጠ ይመስላል፡፡ በግንባሩም ውስጥ የስልጣንና ሃብት ክፍፍልን ማዕከል ያደረጉ ፖለቲካዊ ቀውሶች የመነሳት ዕድላቸው ከፍተኛ ነው፡፡ ድርጅቱም እስካሁን የሀገሪቱን ሁለንተናዊ ህይወት ስለተቆጣጠረ ውስጣዊ ቀውሶቹ በቀጥታ ለሀገራዊ መጠነ-ሰፊ ቀውስ ምክንያት የመሆን ዕድላቸው ሰፊ ነው፡፡ እንዲህ ዓይነት ቀውሶች ደግሞ ጦር ሰራዊቱን ወደ ፖለቲካ የመሳብ አቅም ይኖራቸዋል፡፡

የኢህአዴግ-መራሹ መንግስት ሁኔታ በአምባገነኖችና ወታደራዊ ገዥዎች የተጠነሰሱትን የምስራቅ እስያ ልማታዊ መንግስታት ፈለግ መከተል እንደሆነ ምሁሩ ሬኒ ሌፎርትና ፕሮፌሰር መሳይ ከበደ ያስረዳሉ፡፡ በእርግጥ ልማታዊ መንግስት ወታደራዊ መልክ ያለው ጠንካራና ጥብቅ ተዋረዳዊ አደረጃጀትን ይጠይቃል፡፡ መሰረታዊው ጥያቄ ግን ኢህአዴግ ወደ ወታደራዊ አገዛዝ የሚያዘነብለው እውነተኛ ልማታዊ መንግስትን መስርቶ የሀገሪቱን ልማት ለማፋጠን ነው? ወይስ ስልጣን ለማራዘም ነው? የሚለው ነው፡፡ ሆኖም የትኛውም ዓላማ ቢኖረው እስካሁን ባለው ሁኔታ በኢትዮጵያ ልማታዊ መንግስትን የሚያስተናግድ ድርጅታዊ፣ መንግስታዊ፣ ሀገራዊ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ነባራዊ ሁኔታዎች እንደሌሉ ብዙ ታዛቢዎች ይገልፃሉ፡፡

መንግስት የፖለቲካ ምህዳሩን በከፍተኛ ሁኔታ በማጥበብ ብቻ ሳይወሰን በዘንድሮው ብሄራዊ ምርጫ እንኳ የፌደራሉን ፓርላማና የክልል ምክር ቤቶችን መቀመጫዎች ሙሉ በሙሉ ለመቆጣጠር መድፈሩ ስልጣንን በብቸኝነትና በማናቸውም መንገድ ተቆጣጥሮ የመቆየት ፍላጎቱን ያሳያል፡፡ የሰብዓዊ መብቶች ይዞታም ስለማሽቆልቆሉ ዓለም ዓቀፍ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች በተደጋጋሚ የሚገልፁት ነው፡፡

ሁኔታውም አሁን ካሉትም በላይ በሰላማዊ ትግል ተስፋ የቆረጡ በርካታ ነፍጥ ያነገቡ አማፂያን እንዲፈጠሩ ሊያደርግ ይችላል፡፡ ያኔ ደግሞ ሲቪሉ አመራር ከምንጊዜውም በበለጠ ወታደራዊ መዋቅሩንና ወታደራዊ መፍትሄዎችን የሙጥኝ ማለቱ አይቀርም፡፡

በአንፃሩ ግን ቀደም ብለው ከተነሱት ነጥቦች አንፃር ሲታይ ድርጅታዊና ሀገራዊ ቀውሶች ቢከሰቱም ጦር ሰራዊቱ ራሱ ከቀውሱ ነፃ የመሆን ዕድሉ አናሳ ነው፡፡ ስለሆነም ቀውሶችን ተቋቁሞ የስርዓቱ መድህን ላይሆን ይችላል ማለት ነው፡፡ ለዚህም ይሆናል መጠነ-ሰፊ ድርጅታዊና ሀገራዊ ቀውሶች ከመፈጠራቸው በፊት ለወታደሩ ፖለቲካዊ መደላድሉን ማጠናከር የተፈለገው፡፡

ከዚህ በኋላ ሲቪሉ መንግስት የጦር ሰራዊቱን ኢኮኖሚያዊ ኢምፓዬርና ፖለቲካዊ ሚና ለመገደብ ፍላጎትም አቅምም አይኖረውም፡፡ ሆኖም ግን ጦር ሰራዊቱ ራሱ ካሉበት ውስጣዊ ውስንነቶችና ከኢህአዴግ-መራሹ መንግስት ጋር ካለው ጥብቅ ቁርኝት አንፃር ሲቪል መንግስቱን በሃይል ገልብጦ ስልጣን ሊይዝ ይችላል ብሎ ማሰብ የዋህነት ይሆናል፡፡ ይልቁንስ ሀገራዊና ድርጅታዊ ቀውሶች ባንዣበቡ ቁጥር የኢህአዴግ-መራሹ መንግስት በመልካም ፍቃዱና በልማታዊ መንግስት ሽፋን ሰራዊቱን ወደ ፖለቲካ በመሳብና ጥምር የሲቪልና ወታደራዊ አገዛዝ (civilian-cum-military) በማስፈን ስልጣኑን ለማራዘም ሊሞክር ይችላል፡፡ ምዕራባዊያን አጋሮችም ቢሆኑ በዋናንት የሚፈልጉት የኢትዮጵያን መረጋጋት (stability) ስለሆነ ግብፅ ላይ እንዳደረጉት ሁሉ ተቃውሞ ላይኖራቸው ይችላል፡፡

መቼም ከኢትዮ-ኤርትራ ጦርነትና የህወሃት ክፍፍል በፊት ለጦር ሰራዊት ግንባታ እምብዛም ትኩረት ያልሰጡት የቀድሞው ጠቅላይ ሚንስትር አቶ መለስ ዜናዊ ከህልፈታቸው በፊት ጦር ሰራዊቱ የኢኮኖሚ ኢምፓዬር እንዲገነባ መሰረቱን ሲጥሉለትም ሆነ ፖለቲካዊ ፍላጎቱ እንዲነቃቃ ሲያደርጉት ይህን ሁሉ ታሳቢ አድርገው ይሆናል፡፡

ክፍል ሶስት

በቅርብ እናውቀዋቸዋልን የሚሉ ወገኖች ‹‹ክንፈ ደፋር ነው፤ ምንም የማይሞክረው ነገር የለም›› ሲሉ ሰውዬው አዲስ ነገርን ለማወቅ ያላቸውን ጉጉትና ለፈጠራ ስራዎች ያላቸውን ፅኑ ፍላጎት ሲመሰክሩ ይደመጣሉ፡፡ በአንጻሩ ደግሞ የሰውዬውን ቁጡነትና ኃይለኛነት በመጥቀስ ‹‹ቆራጥ›› እና ‹‹ጀግና›› እያሉ የውዳሴ ካባዎችን ሲደርቡላቸው ይሰማል፡፡ እነዚህ ሁለት የተቃራኑ ባህሪያቸውን ደግሞ ከልጅነት ዕድሜያቸው ጀምሮ እስከ ህወሃት ታጋይነት ዘመናቸው ያዳበሯቸው ባህሪያት ሳይሆኑ እንዳልቀረ የሚናገሩ አሉ፡፡ የዚህ ድርብ ባህርያት ባለቤት ደግሞ በሀገሪቱ ውስጥ በግዙፈነቱና በሃብቱ ጡንቻ ተወዳዳሪ የሌለውን በእንግሊዘኛው ምህጻረ ቃል “ሜቴክ” (Metal Engineering Corporation/METEC) በመባል የሚታወቀውን የመከላከያ ብረታብረት ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን ከምስረታው ዘመን ጀምሮ እየመሩ ያሉት ሜጀር ጄኔራል ክንፈ ዳኘው ናቸው፡፡

ጄነራል ክንፈ ዳኘው

ተቋሙ በመከላከያ ሚንስቴር ስር ሆኖ የጦሩ ጠቅላይ አዛዥ የሆኑት ጠቅላይ ሚንስትሩ በበላይነት እንደሚመሩት የተቋቋመበት አዋጅ ቢገልጥም አዋጁ ለጠቅላይ ሚንስትሩ ከሰጠው ‹‹የበላይ ተቆጣጣሪነት›› ስልጣን ይልቅ የሜጀር ጀኔራል ክንፈ ተፅዕኖ እንደሚያይል የተቋሙን አሰራር በቅርብ የሚያውቁ ሰዎች ይናገራሉ፡፡

ይህ ድርጅት በመከላከያ ሚንስቴር ስር የብረታብረት ምህንድስና ይሰሩ የነበሩትንና ሌሎች ከፕራይቬታይዜሽን ኤጀንሲ የተላለፉለትን የልማት ድርጅቶች በአንድ ተቋም ስር ለማስተዳደርና ሀገራዊ አቅምን ለመፍጠር ተፈልጎ ነበር በ2002 ዓ.ም. በአዋጅ የተቋቋመው፡፡ በመንግስት በተመደበለት 10 ቢሊዮን ብር መነሻ ካፒታል የተመሰረተው ኮርፖሬሽኑ የካፒታል አቅሙንና የሚያስተዳድራቸውን አምራች ድርጅቶች ብዛት እየጨመረና ዓመታዊ ትርፉም ከጊዜ ወደ ጊዜ እያሻቀበ ስለመምጣቱም ከድርጅቱ የሚወጡ መረጃዎች ያሳያሉ፡፡ ለአብነትም ያህልም ከሁለት ዓመት በፊት ዓመታዊ ትርፉ 17 ሚሊዮን ብር ያህል የነበርው ድርጅት በዓመቱ ማለትም በ2006 ዓ.ም ትርፉን ወደ 300 ሚሊዮን ብር ማሳደጉን ስራ አስኪያጁ ለፓርላማው ባቀረቡት ሪፖርት አስታውቀው ነበር፡፡ በአሁኑ ወቅት ጠቅላላ የካፒታል አቅሙም 30 ቢሊዮን ብር እንደደረሰም ይነገራል፡፡ ሲመሰርት አካባቢ ከ20 የማይበልጡ ንዑሥ ድርጅቶችን ያስተዳድር የነበረው ኮርፖሬሽን በአሁኑ ወቅት 100 ያህል አምራች ድርጅቶችን ያስተዳድራል፡፡

ሜቴክ በቅርቡ በተጠናቀቀው የመጀመሪያው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ቁልፍ ማስፈፀሚያ እንዲሆንና የሀገሪቱን ኢኮኖሚ በግንባር ቀደምትነት በመምራት ከግብርና ወደ ኢንዱስትሪ ኢኮኖሚ እንዲያሸጋግር ተስፋ ተጥሎበት ነበር፡፡ ሆኖም በመጀመሪያው የአምስት ዓመት ዕቅድ ግን የኢንዱስትሪው ዘርፍ ዋና አካል የሆነው የማኑፋክቸሪንግ ንዑስ ዘርፍ ቀድሞ የታለመለትን ግቦች ካላሳኩት ውስጥ ቀዳሚውን ስፍራ ስለመያዙ በመንግስት እየተነገረ ነው፡፡ የማኑፋክቸሪንግ ዘርፉን እንዲመራ ሃላፊነት የተሰጠው ሜቴክ የንዑስ ዘርፉን በማጎልበት ሀገሪቱን ተጠቃሚ ከማድረግ ይልቅ ራሱን ከሚገባው በላይ እየለጠጠና እያገዘፈ ስለመሄዱ ግልፅ እየሆነ መጥቷል፡፡

በተጨማሪም ለአገር ውስጥ ባለሙያዎች እንደ ‹‹ልህቀት ማዕከል›› (Center of Excellence) እና የቴክኖሎጂ ሽግግር ማዕከል ለማድረግ ታሰቦ እንደተቋቋመ ይታወቃል፡፡ በኢኮኖሚው ረገድም ከውጪ አገር በብዙ ዶላር እየተገዙ የሚገቡ ዕቃዎችን በአገር ውስጥ በማምረት የውጪ ምንዛሬን ማስቀረትና የአገር ውስጥ የማምረት አቅምን ለማጎልበት ታስቦ የተቋቋመ ነው፡፡ መንግስትም በሀገሪቱ ባለ ሁለት አኃዝ ኢኮኖሚ ዕድገት ውስጥም የሜቴክን ሚና እንዳለበትና ለብዙ ዜጎችም የሥራ ዕድል ፈጥሯል በማለት ይኩራራበታል፡፡

በሀገር ገጽታ ግንባታ ረገድም መንግስት ሜቴክን እንደ ቱሪዝም መዳረሻ ወስዶ በተደጋጋሚ ሲያስጎበኝ ይስተዋላል፡፡ ባለፈው አንድ ዓመት ብቻ የኡጋንዳውን ፕሬዝዳንት ዩዌሪ ሙሴቬኒን፣ የሩዋንዳው ፕሬዚዳንት ፖል ካጋሜን የጨምሮ የተለያዩ አገሮች ዲፕሎማቶችን፣ የፓርላማ አባላትን እንዲሁም የውጭ ሀገራት ጋዜጠኞችን በቢሸፍቱና በተለያዩ ቦታዎች የሚገኙ ኢንዲስትሪዎቹንና ፋብሪካዎቹን በተደጋጋሚ ሲያስጎበኝ ታይቷል፡፡

በአንፃሩ ደግሞ በመንግሥት ውዳሴና አድናቆት የሚጎርፍለት ኮርፖሬሽኑ በምርቶቹ ጥራት፣ በሕጋዊ አመሠራረቱና ተጠያቂነቱዙሪያ ብዙ ትችቶችና ወቀሳዎችም ይሰነዘሩበታል፡፡ ለመንግስት አወንታዊ አመለካከት ያላቸው አስተያየት ሰጭዎች ሳይቀሩ ሜቴክ ከአቅሙ በላይ ውጦ እያኘከ መሆኑን ስመሆኑ የሚከራከሩት ታላላቅ የመንግስት ፕሮጀክቶችን ለመስራት ከተረከበ በኋላ በጊዜ ገደብ ማስረከብ ያለመቻሉንና የስራዎቹም ጥራት መጓደሎችንም በማንሳት ነው፡፡

በተጠናቀቀው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ ለመንግሥት አስር የስኳር ፋብሪካ ልማት ፕሮጀክቶችን ለመገንባት ቢዋዋልም አንዳቸውንም ሳያጠናቅቅ የዕቅዱ ዘመን ተጠናቋል፡፡ በእርግጥ መንግሥት ለእነዚህ ፕሮጀክቶች መገንቢያ የውጭ ብድሮችን ባሰበው መጠን አለማግኘቱ አንዱ ችግር ቢሆንም ሜቴክ ብድር የተገኘላቸውንም ፕሮጄክቶች ማጠናቀቅ ሳይችል ቀርቷል፡፡ በደቡብ ኢትዮጵያ ኦሞ ሸለቆ ሊገነቡ ከታሰቡት አምስት የኩራዝ ስኳር ፕሮጀክቶች መካከል ሜቴክ አንዱን ብቻ ለማጠናቀቅ መቃረቡን የገለጻው ገና በቅርቡ ነው፡፡ የገጠመውን የአቅም ውስንነትም ግምት ውስጥ በማስገባት ‹‹ኩራዝ ሁለት›› እና ‹‹ኩራዝ ሦስት›› የተባሉት ሁለት ፋብሪካዎች በቅርቡ ከሜቴክ ተነጥቀው ለቻይና ኩባንያዎች ተሰጥተዋል፡፡

በተመሳሳይም በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ከአሥር ቢሊዮን ብር በላይ በሆነ ካፒታል የድንጋይ ከሰልና ማዳበሪያ ፋብሪካዎችን ለመገንባት ቢረከብም በተዋዋለበት የጊዜ ገደብ ሳያጠናቅቃቸው በርካታ ወራት ነጉደዋል፡፡

በሌላ በኩልም ሜቴክ ለአዲስ አበባ ከተማ መስተዳድር ለሕዝብ ትራንስፖርት የሚያገለግሉ ከ500 በላይ አውቶብሶችን ገጣምሞ ለማቅረብ ቢዋዋልም በተፈለገው ፍጥነት አጠናቆ ማቅረብ ባለመቻሉ አስተዳድሩ በቅርቡ ከውጭ ሀገር ተሽከርካሪዎችን ለማስገባት ውሳኔ ላይ መድረሱን ለማወቅ ተችሏል፡፡ በምርት ጥራት በኩልም የሚታዩ ችግሮች ኮርፖሬሽኑን ከመስተዳድሩ ጋር ውዝግብ ውስጥ ስገባው ሲሆን በተለይ ለአንበሳ አውቶብስ ድርጅት የገጣጠማቸው ተሽከርካሪዎች የፍሬን ችግሮች ያሉባቸው መሆናቸውን መስተዳድሩ ይወቅሳል፡፡ ሆኖም ግን የሜቴክ ሥራ አስኪያጅ ስለ ጉዳዩ ፓርላማው ውስጥ ሲጠየቁ በሰጡት መልስ ‹‹እኛ የገጣጠምናቸው አውቶብሶች የፍሬን ችግር የላቸውም፡፡ ችግሩ የእኛ አውቶብሶች አሽከርካሪዎቹ ቀድሞ ሲያሽከረክሯቸው ከነበሩት የተለየ ቴክኖሎጂ ስላላቸው ብቻ የተከሰተ ችግር ነው›› በማለት አስተባብለዋል፡፡

ይኼው ኮርፖሬሽን ከሚያከናውናቸው ትላልቅ ፕሮጀክቶች አንዱ የታላቁ ህዳሴ ግድብ የኤሌክትሮ ሜካኒካል ሥራዎች ተጠቃሽ ነው፡፡ ነገር ግን የግድቡን ግንባታ የሚያከናውነው የኢጣልያኑ ሳሊኒ ኮንስትራክሽን በሜቴክ የሥራ ፍጥነት ደስተኛ አለመሆኑን የዋዜማ ምንጮች ይገልፃሉ፡፡ ግድቡ በአሁኑ ወቅት ቢያንስ 700 ሜጋ ዋት ኃይል ማመንጨት እንደነበረበት በእቅዱ ቢቀመጥም ዕቅዱ ላለመሳካቱ ሳሊኒ ሜቴክን ተጠያቂ እንደሚያደርግ ምንጮቻችን ይጠቁማሉ፡፡

የጥራት ችግር ኮርፖሬሽኑን ከኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ኮርፖሬሽን ጋርም ውዝግብ ውስጥ ከቶት እንደነበር አይዘነጋም፡፡ ኤሌክትክ ሃይል ሜቴክ ባመረታቸው ትራንስፎርመሮች ላይ ከፍተኛ የጥራት ችግሮች እንዳባቸው ቢያነሳም ሜቴክ በበኩሉ ደንበኛዬ ‹‹ያመረትኩትን ትራንስፎርመር ጥራት የመመርመር ብቃት የለውም›› በማለት ተከራክረዋል፡፡ ደንበኛዬ ለምርቱ ያወጣሁትን 380 ሚሊዮን ብር ይክፈለኝ ሲልም ክስ መስርቶ ጉዳዩ እስከ ፓርላማው አፈጉባዔና ጠቅላይ ሚንስትር ፅ/ቤት ድረስ ደርሶ የነበረ ሲሆን መንግስትም ገንዘቡ ለሜቴክ እንዲከፈል ትዕዛዝ በመስጠቱ ተከፍሎታል፡፡

በሌላ በኩል መንግሥት ለሜቴክ ከገደብ ያለፈ ድጋፍ ስለሚያደርግለት ብቻ ከምርት በፊት የቅድመ ገበያ አዋጭነት ጥናት፣ የምርት ተጠቃሚዎችን የመግዛት አቅምና ፍላጎት እንዲሁም በአመራረት በኩል ያሉበትን ችግሮች እንዳይቀርፍ እንቅፋት ሆኖበታል፡፡ ለምሳሌም ያህል ሜቴክ ባለፉት ሁለት ዓመታት የአርሶ አደሮችን የማምረት አቅም ለመሳደግ ታስቦ በገፍ ብዙ ሺሕ ትራክተሮችንና ባለሁለት ተሽከርካሪ ጎማ ያላቸውን የማረሻ መሣሪያዎችን አምርቶ ነበር፡፡ ነገር ግን የአብዛኛው አርሶ አደር አቅም አነስተኛ በመሆኑ ምርቶቹን ገዝቶ ለመጠቀም ውድ ስለሆነበት ኮርፖሬሽኑ ያመረታቸውን ወደ 20 ሺሕ የሚጠጉ ትራክተሮችና የማረሻ መሣሪያዎች በመጋዘን ለማቆየት መገደዱን ሃላፊዎቹ ሲገልፁ ይሰማሉ፡፡

የሜቴክ ዘርፎች በመለጠጣቸው በግሉ ዘርፍ ላይም ጡንቻውን ማሳረፉን የሚጠቅሱ በርካቶች ናቸው፡፡ በተለይ በተሽከርካሪ መገጣጠምና መለዋወጫ ዕቃዎች ምርት ላይ ተሰማርተው የነበሩ የግል ኩባንያዎች ተጎጂዎች ሆነዋል፡፡ በተለይ በአገሪቱ በፌዴራልም ሆነ በክልል ደረጃ ያሉ የመንግሥት ድርጅቶች የሜቴክን ተሽከርካሪዎች ብቻ እንዲገዙ በቀጥታና በተዘዋዋሪ እያስገደደ በመሆኑ የነጻ ገበያ ውድድሩን እየጎዳው እንደሆነ ታዛቢዎች በአስረጂነት ያነሳሉ፡፡ ‹‹ድርጅቱ ተሽከርካሪ ወይም ማሽነሪ ማምረቱ ቢበረታታም አነስተኛዋን ቡሎን ሳይቀር በማምረት የጉልበት ሽሚያ ውስጥ ገብቷል›› በማለት ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ አንድ ባለሃብት ሰሞኑን ለዋዜማ ሬዲዮ ገልጸዋል፡፡

በተጨማሪም የውጭ ምንዛሬን ለመቆጠብ እንዲያስችል ተብሎ ቢመሰረትም ሜቴክ ስር የሰደደ የእውቀት ውስንነት ስለሚታይበት ከፍተኛ ገንዘብ በመክፈል ከውጪ አገራት ባለሙያዎችን ማስገባቱ ከሚነሱበት ትችቶች ውስጥ አንዱ ነው፡፡ ከክፍያውም በላይ ሙያተኞቹ ቆይታቸውን አጠናቀው እስኪሄዱ ድረስ የሚያወጣው የሆቴልና ተያያዥ ወጪዎች አሳሳቢ ሆኖበታል፡፡ ለዚህም ነበር ታላላቆቹን ኢምፔሪያልና ሪቬራ ሆቴሎችን ለእንግዳ ማረፊያ እንዲሆኑ ከ200 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጭ የገዛው፡፡ ሆኖ ግን ሆቴሎቹ ከሁለት ዓመት በላይ ስራ ፈትተው ተቀምጠዋል፡፡

የኮርፖሬሽኑን ‹‹የልማት ድርጅትነት›› ጥያቄ ውስጥ የሚከቱና የወታደራዊ ተቋሙነቱን ብቻ የሚያሳዩ እውነታዎች ፈጠው እየወጡ ነው፡፡ ለምሳሌ የሜቴክ ሰራተኞች ከጦር ሰራዊቱ የተውጣጡና በመከላከያ ሚንስቴር ህግ ብቻ የሚታዳደሩ በመሆናቸው ከልማት ድርጅትነት ይልቅ ወታደራዊ ኢንዱስትሪነቱ እንደገዝፍ ያሳያል፡፡ በጉዳዩ ላይ በቅርቡ በፓርላማውም ሳይቀር ‹‹የኮርፖሬሽኑ ሰራተኞች በሀገሪቱ የሰራተኛ ህግ መሰረት ካልተዳደሩ የልማት ድርጅትነቱ ምኑ ላይ ነው?›› የሚል ጥያቄ ለጄኔራል ክንፈ ቀርቦላቸው ነበር፡፡ እሳቸውም በሰጡት መልስ ‹‹ተቋሙ የጦር መሳሪያን ጨምሮ ለሀገር ደህንነት መጠበቂያ አጋዥ መሳሪየዎችን የሚያመርት ተቋም ስለሆነ ሠራተኞችም ወታደሮች ናቸው፡፡ ስራው ደግሞ በባህሪው ከሀገር ደህንነት ጋር በቀጥታ የተያያዘ በመሆኑ፣ ሰራቶኞቹን ከሰራተኛ አዋጁ ይልቅ በወታደራዊ ዲስፕሊን መመራት ስላለበት ነው›› በማለት ተከራክረዋል፡፡

የሜቴክን የ‹‹ልማት ድርጅትነት›› ጥያቄ ውስጥ የሚያስገባው ሌላው ጉዳይ የቁጥጥርና ተጠያቂነት ስርዓቱ እንደሆነ የሚከራከሩ ወገኖችም አሉ፡፡ ለምሳሌ ማንኛውም ከመንግስት በጀት የሚመደብለት መስሪያ ቤት በሀገሪቱ ህግ መሰረት በኦዲት፣ በስነ-ምግባርና ፀረ-ሙስና ህግ እንዲሁም በመንግስት ንብረት አስተዳደር አዋጅ ቁጥጥርና ክትትል እንደሚደረግበት ቢደነገግም ሜቴክ ግን ከዚህ ነፃ ነው፡፡

ሌላው አነጋጋሪ ጉዳይ ሜቴክ በየዓመቱ ከሚያስገባው ትርፍ ምንም ዓይነት ገንዘብ ወደ መንግስት ግምጃ ቤት አለማስገባቱ ነው፡፡ ሆኖም ግን በማንኛውም ጊዜ ሜቴክ ተጨማሪ በጀት ካስፈለገው በፓርላማ ተፈቅዶ ማግኘት እንዲችል በህግ ተፈቅዶለታል፡፡ በትርፋማ ስራ ለተሰማራ ድርጅት ይህንን መብት መፍቀድ ተቋማዊና ህጋዊ ተጠያቂነትን አደጋ እንደጣለው የሚያነሱ ባለሙያዎች በርካታ ናቸው፡፡ ለዚህም ይሆናል ሜቴክ በፈለገው ዘርፍ ሁሉ ለመሰማራት ያስቻለው፡፡ ከላይ በተነሱት አንገብጋቢ ጉዳዮች ዙሪያም ጠንከር ያለ ጥያቄ ሳይነሳበት እነሆ የ30 ቢሊዮን ብር ካፒታል ባለቤት መሆኑን በቅርቡ ይፋ አድርጓል፡፡ መንግስትም ሜቴክ ‹‹የአገር አለኝታ›› ስለመሆኑ ለህዝቡ መለፈፉን የሚያቋርጥ አይመስልም፡፡

Leave a Reply