ከጋዜጠኛ ደምስ በለጠ

ኢትዮጵያ ውስጥ አዲሱን የ2008 ዓ.ም አመት ለመቀበል ሁሉም በየቤቱ እንደአቅሙ ሽር ጉድ እያለ ነው ። በመላ ሃገሪቷ ሜዳና ሸንተረር ፤ ሸለቆና ሜዳ ፤ አደይ አበባው ፈንድቷል ። ለጥቅምት የሚሆነውን ማር ንቦች ለመቅሰም በነፃነት ካንዱ አደይ አበባ ወደሌላው ውር ውር ይላሉ ። አገር ምድሩ እንዳቅሙና እንደተለመደው በአሉን ለማክበር በየቤቱ ተዘጋጅቷል ። የጠላው ፤ የጠጁ ፤ የዳቦውና አንባሻው መአዛ የአገር ምድሩን አየር አጥኖታል ። በዚህ አውደ-አመት ዋዜማ ላይ ሻእቢያም የራሱን የአዲስ አመት ስጦታ ለአገራችን አዘጋጅቷል ።

ኤርትራ ውስጥ ተቋቋመ የተባለው “አገር አድን ንቅናቄ” ምስረታ ዜና ከተናኘ በኋላ ፤ ሞላ አስገዶም በሻእቢያ ተልእኮ ጠሰጥቶታል ። ተልእኮው ስድስት መቶ የሚደርሱ የዴምሕት ወታደሮቹን ይዞ ኢትዮጵያ ወስጥ በመግባት የአዲሱ አመት ዋዜማ ላይ አደጋ መጣል ነው ። በውጊያ ላይ እነሞላ አስገዶምን ሊከዱ ከሞከሩ በቅርብ የጥይት ርቀት ላይ የሚጠብቁ የሻእቢያ አልሞ ተኳሾች (Snaipers) እንደተለመደው አብረዋቸው እንዲገቡ ተዘጋጅተዋል ።

ወደ ኢትዮጵያ ገብቶ አደጋ ለመጣል አመቺው ስፍራ ደግሞ በኦምሃጀር በኩል ወደ ሱዳን ግዛት በመግባት ፤ በፍጥነት ወደ ግራ በመታጠፍ ኢትዮጵያ ግዛት ላይ መዝለቅ ነው ። የነፍስ ወከፍ መሳሪያ ከነመሰል ጥይቶቹ ፤ ለእያንዳንዱ የዴምሕት ተዋጊ ታድሎታል ። መትረየስ ተሸካሚዎች ከነዝናራቸውና ከነረዳቶቻቸው ቦታ ቦታቸውን ይዘዋል ከጥቂት ደቂቃዎች በኋላ ፤ በሞላ አስገዶም የሚመራው ስድስት መቶ ጦር በሱዳን ድንበር በኩል ገብቶ በፍጥነት ወደኢትዮጵያ ግዛት እጥፍ ይልና አስፈላጊውን ጥቃት ይፈፅማል ። ይህ ለኢትዮጵያ የአዲሱ አመት ስጦታ ተብሎ በሻእቢያ ታስቦ ነበር ።

እንደማንኛውም ኢትዮጵያዊ ፤ ሞላ አስገዶምም የራሱን የአዲስ አመት ምኞት ፤ በተግባር ላይ ለማዋል ሃሳቡን በልቡ ቋጥሮ ተዘጋጅቷል ። ከተዋጊዎቹም ውስጥ እንዲሁ የአዲስ አመት ህልማቸውን እውን ለማድረግ የተዘጋጁና ሚስጥሩ የተነገራቸው ተዋጊዎች ፤ ከሻእቢያ ነፃ የሚወጡበትን ደቂቃዎች ጭምር እየቆጠሩ ናቸው ። ይህ እቅድ ደግሞ የሞት የሽረት ጉዳይ ነውና በሁሉም ተዋጊዎች ደረት ውስጥ ልባቸው ክፉኛ ይመታል ። እቅዱ ሌላ አማራጭ የለውም ። ነጻነት ብቻ ።

የመጨረሻው ሰአት ደርሶ ሻእቢያ ትእዛዝ ሰጠ ። ትእዛዝ የተሰጠው ጦር ውስጥ ከየአቅጣጫው ግርግር ተፈጠረ ። ከዚህም ከዚያም ጥይት ተተኮሰ ። እነሞላ አስገዶምን በጥይት ርቀት እንዲጠብቁ ፤ ትእዛዝ የተሰጣቸው የሻእቢያ አልሞ ተኳሾች (Snipers) ፤ ከተዋጊዎቹ በሚተኮሱት ጥይቶች ሬሳቸው እዚህም እዚያም ጠብ ጠብ ማለት ጀመረ ።

በዚህ አይነት ፤ በአዲሱ አመት ፤ በኤርትራ ሱዳን ድንበር ላይ ፤ የሻእቢያን የአዲስ አመት ስጦታ ፤ ተዋጊዎቹ ዘፍ አደረጉት ። በዚህም የነጻነታቸውን ብስራትና የአዲሱን አመት ችቦ ኤርትራና ሱዳን ድንበር ላይ ፤ ተዋጊዎቹ በጥይት ለኮሱ ። ይህ በሞላ አስገዶም የሚመራ ጦር ቀደም ብሎ በሁኔታው ተዘጋጅቶበት ነበርና ሻእቢያዎቹን እዚያው አስቀራቸው ። ጦሩ መሳሪያውን እንደታጠቀም ወደ ሱዳን ገባ ። ይህን እቅድ ፤ ሞላ አስገዶምና ጥቂት የሻእቢያ ጠባቂዎችን ወሳኙ ሰአት ላይ እንዲጥሉ ፤ በሚስጥር ከተዘጋጁ ሰዎች በስተቀር ፤ ማንም የሚያውቅ አልነበረም ። ሆኖም አጋጣሚው ከተገኘ ከሻእቢያ ለማምለጥ ይማይመኝ ተዋጊ ኤርትራ ውስጥ የት ይገኛል ? ይህ ካልሆነ እንዴት ስድስት መቶ ተዋጊ ወታደር በአንድ ልብ ሆኖ ለማምለጥ ሊተባበር ቻለ ?

ሞላ አስገዶም በመራው በዚህ ዘመቻ ላይ ያልተመደቡና ሃሬና ካምፕ የቀሩ ተዋጊዎች ፤ ለዘመቻ በተላኩት ወንድሞቻቸው እድል እንዴት እንደሚቀኑ መገመትም ይቻላል ።

ከዚህ በፊት “ዴምህት የሻእቢያ የትሮ ፈረስ” በሚለው ጽሁፌ ላይ ድርጅቱ ውስጥ ያለውን መንፈስ እንዲህ ብዬ ገልጬው ነበር ።

“…… ያም ሆኖ ታዲያ በደንብ ላስተዋለ በ“ዴምሕት” ሰራዊት ወስጥ ያለ ሰብአዊ ስሜት-አልባነትና የዝምታ ድባብ እጅግ ጠንካራ ነው ። ይህ ሁኔታ በአርበኞች ግንባርም ወስጥ ያለ ቢሆንም እንደ “ዴምሕት” ግን ጎልቶ አይታይም ። የ “ዴምሕትን” ወታደሮች አይናቸውን አትኩረህ ስትመለከት፤ በተለይ የትግራይ ተወላጆቹ በአብዛኛው አንድ ስውር ጥቁር ጥላ ይከተላቸው ይመስል ባስቸኳይ አይናቸውን ይሰብራሉ ።…ለእርሻ ፤ለከብት ጥበቃ ፤ ውሃ ለመቅዳት ወይም ለገበያ በጠዋት ወይም አመሻሽ ላይ የወጡ ወጣቶችን እንደባሪያ እየፈነገሉ በፍጥነት ድንበር እንዲሻገሩ ያደርጓቸዋል ። ተፈንጋዮቹ እነማን እንዳፈኗቸው ወዴትስ እንደሚወስዷቸው ምንም አትነይ ግምት የላቸውም ።….ከአመት ላላነሰ ጊዜ በዚህ አይነት እንዲሰሩ ተደርገው ፤ ቅስማቸው ፤ ማንነታቸውና ሰብዕናቸው ተሰብሮ ተስፋ ቆርጠው ሳለ ለነዚህም ሻእቢያ አዲስ አማራጭ ይሰጣቸዋል ፤ የዴምሕት ወታደር መሆን ። ሌላ ተስፋም ስለሌላቸው የዴምሕት ወታደር መሆን ይገደዳሉ——-።

ይህን የመሰለ የሻእቢያ ጭቆና እንዴት የሰዎችን ልብ በአንድነት አያስር ? የሰው ልጅ በእግዚአብሄር የተሰጠው ፤ማንነቱና ሰብእናውና ተደፍሮ ቅስሙ ተሰብሮ መኖሩ ፤ እንዴት በአንድነት አያስተባብረው ?

ሞላ አስገዶም ኤርትራ ውስጥ በየትኛውም ስፍራ በነፃነት መንቀሳቀስ የሚችል ሰው ነው ። ገንዘብም ሆነ የግል ፍላጎቱን ሊያሟላ የሚችልባቸው አጋጣሚዎች ሁሉ ያለው ሰው ነው ። መኪናም ተሰጥቶት የሚንቀሳቀስ ሰው ነው ። ሆኖም ግን ኤርትራ ውስጥ አሻንጉሊት ሆኖ በሻእቢያ ትእዛዝ መንቀሳቀስና የመንፈስ ነጻነት ማጣት ከሁሉ የከፋ እንደሆነ ፤ ከዚህ ከሞላ አስገዶም ሁኔታ መገመት ይቻላል ።

ያለፈው የ2ሽህ 7 ዓ.ም የመጨረሻ ሳምንት ፤ የዜናውን አየር በሙሉ ሰበር ዜና በሰበር ዜና አድርጎት አልፏል ። በኢሳት ቴሌቪዥን እንደሰማነው ፤ ከሶስት ቀን በፊት ፤ የአራቱ ድርጅቶችን “አገር አድን ንቅናቄ” “ሰበር ዜና” ምሥረታ ተነገረን ። ሞላ አስገዶም ምክትል ሊቀ መንበር ሆኖ መመረጡንም አብሮ ተወሳ ።

በማግስቱ የአዲሱ አገር አድን ንቅናቄ አዲሱ ሊቀመንበር ዶ/ር ብርሐኑ ነጋ ፤ ካለፉት ጥምረቶች ሁሉ በተሻለ ሁኔታ ፤ እንዳይፈርስና ዘለቂ እንዲሆንም አስፈላጊው መጠበቂያ ተደርጎለት አገር አድኑ ንቅናቄ ተቋቁሟል ሲሉ በቃለ መጠይቅ ላይ ገለፁ ። የዛኑ እለት ዶክተሩ ድምፃቸው በአየር ላይ ገና እየተንሳፈፈ እያለ ፤ ለመጀመሪያ ጊዜ እውነተኛ ሰበር ዜና ሰማን ። የአዲሱ “የኢትዮጵያን አገር አድን የጋራ ንቅናቄ” ምክትል ሊቀመንበር ፤ አቶ ሞላ አስገዶም ስድስት መቶ ሰራዊት ይዘው መክዳታቸው ተሰማ ።

ስለ ኢትዮጵያ ዜናዎች በየቀኑ የሚከታተለው አገር ወዳድ ኢትዮጵያዊ ሁሉ ፤ ከተለያዩ ሚዲያዎች ዜናውን ቀድሞ ሰማው ። ከዚህ በኋላ የኢሳት ቴሌቪዥንም ዜናውን በራሱ መንገድ አሰራጨው ። ለመሆኑ ኢሳት ከዚህ ሌላ ምን አማራጭ ነበረው ? ኢሳት ቴሌቪዥን ልሸፍነው ቢልስ በምንስ ሊሸፍነው ይችል ነበር ? እኛም ሆንን ሌሎች ታዛቢዎች እንዳስተዋሉት ፤ የአዲሱ “አገር አድን የጋራ ንቅናቄ” እውነተኛ ገፅታ በሞላ አስገዶም ፍንትው ብሎ ወጣ ።

ከላይ በገለፅኩት ዴምህት የሻእቢያ የትሮይ ፈረስ ፅሁፌም ላይ የዚህን “አገር አድን የጋራ ንቅናቄ” መቋቋም አስመልክቶ ፤ የሚከተለውን ትንበያ አድርጌ ነበር ።

“የአዲሱ ትብብር ሊቀ-መንበርነት ስልጣን ለቀድሞው ግንቦት 7 መሪ ይሰጣል ። የወታደራዊ አዛዥነት ስልጣኑን ደግሞ ዴምህት የ(ሻእቢያ የትሮይ ፈረስ) መሪ እንዲይዘው ይደረጋል ።…… የትብብሩ ፀሃፊነትም ለቀድሞዎቹ አርበኞች ግንባር አንድ አባል ሊጨመር ይችላል ። የውጪ ጉዳይ ሃላፊነቱ ስልጣን ደግሞ አዲስ ከአሜሪካ ከሄዱት እንግዶች ላንዱ ለቀድሞው ግንቦት 7 አመራር ሰው ይታከልለታል ።”

“የአገር አድኑ የጋራ ንቅናቄ” ከሊቀ-መንበሩና ከምክትል ሊቀ-መንበሩ ስልጣን በስተቀር ፤ የሌሎች ስልጣን ተዋረድ ባይገለፅም፤ ከሞላ ጎደል የሆነውም ይኸው ነው ። (ይህን “የጋራ አገር አድን ንቅናቄ” በተመለከት ተመልሼ ሰሞኑን በሌላ ጽሁፍ የምመጣበት ጉዳይ ይሆናል ።)

የኢሳት ቴሌቪዥን ሞላ አስገዶምን አስመልክቶ በበተነው ዜና ላይ ፣ ሞላ አስገዶም የከዳው በጋራ ንቅናቄው ላይ ልዩነት ነበረው የምትል ዜናም አብራ ተሰንቅራ ተነግራለች ።

ጥያቄዎች ልጠይቅ !

ጥያቄ አንድ፦ ሞላ አስገዶም በጋራ ንቅናቄው ላይ ፤ ልዩነት ከነበረው እንዴት ተደርጎ የንቅናቄው ም/ሊቀመንበር ሆኖ ሊመረጥ ቻለ ? ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ ቃለ-መጠይቃቸው ላይ ፤ በመርህ ላይ የተመሰረተና ፤ እንዳይፈርስ ሆኖ የተዋቀረ ነው ያሉት ፤ ይህን በልዩነት ላይ የተገነባ ካብ ነው እንዴ ?

ጥያቄ ሁለት፦የተዋጊ ድርጅቶችን ባህርይ በሚገባ የሚያውቁና በውጊያ ልምድም ያለፉ ታዛቢዎች እንደሚሉት ፤ “የዴምሕት” መሪና ተዋጊዎቹ ፤ የነጻነት ትግል ያደርጉ ከነበረ ፤ትግላቸው በመርህ ፤ በአላማና በእምነት ላይ የተመሰረተ አልነበረም ማለት ነው ? ወይስ የሚታገሉት በእምነት ሳይሆን ከኋላ ለሚገፋቸው ልዩ ሃይል ነበር ማለት ነው ?

ጥያቄ ሶስት፦ኢሳት ስለ ሞላ አስገዶም የነዛው ዜና አቢይ አላማ ፤ የሞላ አስገዶምን ሰብእና በማጠልሸት የእስፖንሰርን (ሻእቢያን) ሞራል ለመጠበቅ? ይህን ያሰኘኝ ጥያቄ ደግሞ የሚከተለው ነው ።

ጥያቄ አራት፦ የሞላ አስገዶም እናት ድርጅት “ዴምሕትም” ሆነ ፤አዲስ የተቋቋመው “አገር አድን ንቅናቄ” ምንም አይነት መግለጫ ሳያወጣ ፤ኢሳት የልዩነቱን ዜና ከየትና ከማን አገኘው ?

ጥያቄ አምስት፦ኢሳት በየጊዜው የሚያወጣቸው “ሰበር ዜናዎች” ገና ከመውጣታቸው ቀናት እንኳ ሳያስቆጥሩ ፤ለምንድነው ደጋግመው ፍርስርስ የሚሉት ?

ጥያቄ ስድስት፦ግንቦት ሰባት ንቅናቄ ፤ የነካቸው ወይም የተጠጋቸው ሁኔታዎች ሁሉ ፤ ለምንድነው በየጊዜው አደጋ የሚያገጥማቸው ?

ከነዚህ ጥያቄዎች በኋላ ወደዜናው ልለፍ ።

ይህን ዜና በማጠናቅርበት ወቅት ሞላ አስገዶም የኢሳት ቴሌቪዥን ዜና እንዳለው ሳይሆን ፤የሚገኘው ሱዳን ግዛት ውስጥ ነው ። ወደ ሱዳን ከመግባታቸው በፊት የኤርትራን አልሞ ተኳሾች (Snipers) እዚያው ኤርትራ ውስጥ አደጋ ጥለው ገድለዋቸዋል ። ሞላ አስገዶም ስድስት መቶ የታጠቁ ወታደሮችን ይዞ ነው ወደ ሱዳን ግዛት የገባው ። ሱዳን በግዛቱ ውስጥ ያለፈቃድ የታጠቀ ጦር ይዞ የገባን ግለሰብ ሁኔታ በራሱ ህግ የሚያይበት ሁኔታውች አሉት ። የሱዳን መንግስትም እንደ መንግስት ማሟላት የሚገባው ፎርማሊቲዎች ስላሉት ያን ካሟላ በኋላ ነው ፤ በሞላ አስገዶምና በቀሩት ተዋጊዎች ላይ ፤ ህጋዊም ሆነ ፖለቲካዊ ውሳኔ ሊሰጥባቸው የሚችለው ። ስለዚህ ሞላ አስገዶም ፤ ይህን ጽሁፍ እስከማዘጋጅበት ጊዜ ድረስ የሚገኘው ሱዳን ውስጥ ነው ። ከዚህ በተጨማሪ ፤ ከስድስት መቶዎቹ ተዋጊዎች ውስጥ ፤ የተወሰኑ ተዋጊዎች ነፃነታቸውን ከሻእቢያ እንዳገኙ ካረጋገጡ በኋላ ፤ በተፈጠረ የደስታ ስሜት ምክንያት ጊዜ ሳያጠፉ በተዘበራረቀ መልኩ ገስግሰው ወደ ኢትዮጵያ ገብተዋል ።

ከሻእቢያ ያመለጡት የዴምህት ተዋጊዎች። ሱዳን ድንበር ላይ በትራክተር ተጓጉዘው ከነትጥቃቸው ከሱዳን ወታደር ጋር ።

ወንድሜ ሞላ አስገዶም አንተም ሆንክ አብረውህ ያሉ ተዋጊዎች ፤ እንኳን ከሻእቢያ ገሃነም ወጥታችሁ ለነፃነት በቃችሁ !!
አዲሱ አመት የሰላም እንዲሆንላችሁ ምኞቴ ነው ። እግዚአብሄርም የምታስቡትን ሁሉ ያሟላላችሁ ዘንድ እፀልያለሁ !!

ውድ አንባቢዎቼ እናንተንም እንኳን ለአዲሱ አመት አደረሳችሁ እላለሁ!!

ሰፕቴምበር 12 ቀን 2015 እ.ኤ.አ.
ላስ ቬጋስ ኒባዳ ።

Leave a Reply